family law

  • ጋብቻ በባህላዊ መንገድ ተመስርቷል ለማለት የሚቻልበት አግባብና መመስረቱን ማስረዳት የሚቻልበት ሁኔታ የተሻሻለው የቤተሰብ ህግ አንቀፅ 4 እና 97(2)

    Cassation Decision no. 33875

  • የአንድ ሰው አባት ነኝ በሚል የሚቀርብ ሰው አባትነቱን በህግ አግባብ በማስረጃ ማስረዳትና ማረጋገጥ ያለበት ስለመሆኑ የአማራ ክልል የቤተሰብ ህግ አንቀፅ 147(1) 97(2)

    Cassation Decision no. 34149

  • የጡረታ አበል እንደማንኛውም ገቢ የባልና ሚስት የጋራ ንብረት ተደርጐ የሚወሰድ ስላለመሆኑ

    Cassation Decision no. 34387

  • ከጋብቻ በፊት የተፈራ ንብረት ላይ ያለን ዕዳ ለመወጣት ከጋብቻ በኃላ ከባልና ሚስት የጋራ ገንዘብ መከፈሉ ንብረቱን የጋራ ንብረት የማያደርገው ስለመሆኑ የተሻሻለው የቤተሰብ ህግ አንቀፅ 62(1) እና 7ዐ(1)

    Cassation Decision no. 35376

  • የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፍ/ቤቶች ጋብቻን በተመለከተ የባልነት ወይም የሚስትነት የምስክር ወረቀት ከመስጠት ባለፈ በማስረጃው ላይ ክርክር ከተነሳበት ወይም የጋብቻ መኖር አለመኖርን ለመወሠን የስረ ነገር ሥልጣን ያልተሠጣቸው ሥለመሆኑ፣

     

    አዋጅ ቁጥር 408/1996 አንቀፅ 2

     

    አዋጅ ቁጥር 361/1995 አንቀጽ 41/1/ /ሸ/

    የሰ/መ/ቁ. 75560

    ሐምሌ 26 ቀን 2004 ዓ.ም.

     

    ዳኞች፡-ተሻገር ገ/ስላሴ

    አልማው ወሌ ዓሊ መሐመድ ነጋ ዱፊሳ

    አዳነ  ንጉሴ

     

    አመልካች፡- ወ/ሮ ኪሮስ ገ/ማሪያም - ጠበቃ ዮሴፍ  አእምሮ ቀረቡ ተጠሪ፡-አቶ ገብረ ስላሴ ሃይሌ- ወኪል ወርቅነሽ መንግስቱ ቀረቡ

    መዝገቡ ተመርምሮ ተከታዩ ፍርድ ተሰጥቷል፡፡

     

                 

     

    ጉዳዩ የባልነት ማስረጃን መሰረት ያደረገ ክርክርን የሚመለከት ሲሆን ክርክሩ የተጀመረው በአዲስ አበባ ከተማ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የአሁኑ አመልካች ባቀረቡት የመቃወም አቤቱታ መነሻ ነው፡፡አመልካች የመቃወም አቤቱታ ሊያቀርቡ የቻሉት የአሁኑ ተጠሪ በስር ፍርድ ቤት የሟች ወ/ሮ ኪሮስ ውቤ ባል ነኝ በማለት በሐሰት የወሰዱት ማስረጃ ያላግባብ ነው በማለት የተወሰደው ማስረጃ እንዲሰረዝላቸው ዳኝነት ጠይቀዋል፡፡ የስር ፍርድ ቤትም ግራ ቀኙን ከአከራከረና የምስክሮች ቃል ከሰማ በኋላ በተጠሪና በሟች ወ/ሮ ኪሮስ ውቤ መካከል ጋብቻ ስለመፈፀሙ በትዳር ሁኔታ ተረጋግጧል በሚል ምክንያት የአመልካችን አቤቱታ ባለመቀበል ቀድሞ ተጠሪ የሟች ወ/ሮ ኪሮስ ውቤ ናቸው በማለት የሰጠውን ውሳኔ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 360(2) መሰረት በማጽናት ወስኗል፡፡ከዚህም በኋላ አመልካች የይግባኝ ቅሬታቸውን ለአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤት ቢያቀርቡም ተቀባይነት  አላገኙም፡፡ ጉዳዩን ለከተማው ሰበር ሰሚ ችሎት አቅርበውም ተቀባይነት አላገኙም፡፡የአሁኑ የሰበር አቤቱታ የቀረበውም ይህንኑ ውሳኔ በመቃወም ለማስለወጥ ነው፡፡የአመልካች ሰበር አቤቱታ መሰረታዊ ይዘትም የባልነት ጉዳይ አከራካሪ በሆነበት ሁኔታ ጉዳዩ በበታች ፍርድ ቤቶች የታየው ያለስልጣናቸው መሆኑንና የተጠሪ የባልነት ማስረጃ ከመጀመሪያውም የተሰጠው ተገቢ ያልሆነ አቤቱታ ቀርቦና በሕግ አግባብ መቅረብ ያለበት ማስረጃ ሳይቀርብ ነው የሚል ሲሆን አቤቱታው ተመርምሮም ጉዳዩን የአዲስ አበባ ከተማ ፍርድ ቤቶች ለማየት ስልጣን ያላቸው መሆን ያለመሆኑን ለመመርመር ሲባል ለሰበር ችሎቱ እንዲቀርብ የተደረገ ሲሆን ለተጠሪም ጥሪተደርጎላቸው ቀርበው በጉዳዩ ላይ የተሰጠው ውሳኔ ተገቢ ነው በማለት ተከራክረዋል፡፡አመልካች በበኩላቸው የሰበር አቤቱታቸውን በማጠናከር የመልስ መልሳቸውን ሰጥተዋል፡፡

    የጉዳዩ አመጣጥ አጠር አጠር ባለመልኩ ከላይ የተገለፀው ሲሆን ይህ ችሎትም የግራ ቀኙን ክርክር ለሰበር አቤቱታው መነሻ ከሆነው ውሳኔ እና አግባብነት ካላቸው ድንጋጌዎች ጋር በማገናዘብ በሚከተለው መልኩ መርምሮታል፡፡እንደመረመረውም የአዲስ አበባ ከተማ ፍርድ


    ቤቶች ጉዳዩን የማየት የስረ ነገር ዳኝነት ሥልጣን አላቸው? ወይስ የላቸውም? የሚለው ነጥብ በጭብጥነት ሊመረመር የሚገባው ሁኖ አግኝቶታል፡፡

    የአዲስ አበባ ከተማ ፍርድ ቤቶች የዳኝነት ሥረ ነገር ሥልጣን በአዋጅ ቁጥር 361/1995 እና 408/1996 ስር ተመልክቷል፡፡በዚህም መሰረት በአዋጅ ቁጥር 361/1995 እና አዋጅ ቁጥር

    408/1996 ከተሰጧቸው ስልጣኖች መካከል የወራሽነት ምስክር ወረቀት መስጠት፣የባልና ሚስትነት፣የሞግዚትነት ማስረጃ መስጠት ይገኙበታል፡፡በዚህ ረገድ የተሻሻለውን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቻርተር አዋጅ (ማሻሻያ) አዋጅ ቁጥር 408/1996 አንቀጽ 2 በአዋጅ ቁጥር 361/1995 አንቀጽ 41(1)(ሸ) ስር የተመለከተው ድንጋጌ ሰርዞ የአዲስ አበባ ከተማ ፍርድ ቤቶች የወራሽነት፣የባልና ሚስትነት እና የሞግዚትነት የምስክር ወረቀት ለማግኘት የሚቀርብ አቤቱታ ላይ የዳኝነት ሥልጣን ያላቸው መሆኑ ተደንግጓል፡፡የድንጋጌው የእንግሊዝኛው ቅጂም "application for certification of succession,marriage and guardianship."በሚል የተቀመጠ ነው፡፡ከእነዚህ የድንጋጌዎች ይዘት መገንዘብ የሚቻለው የአዲስ አበባ ፍርድ ቤቶች ስለጋብቻ በሚሰጡት ማስረጃ ላይ በሚቀርብ ክርክር የሚኖራቸው የዳኝነት ሥልጣን አድማሱ እስከምን ድረስ መሄድ አለበት? የሚለው ጥያቄ የሚነሳ መሆኑን ነው፡፡በሌላ አገላለጽ የአዲስ አበባ ከተማ ፍርድ ቤቶች የዳኝነት ሥልጣን የባልና ሚስትነት ማስረጃ ለመስጠት ነው ተብሎ የተቀመጠው የሕጉ አገላለፅ ፍርድ ቤቶቹ የባልነት ወይም የሚስትነት ማስረጃ ከሰጡ በኃላ በማስረጃው ተቃውሞ ቢቀርብ እና የተቃውሞው መሰረት የሚሆኑት ምክንያቶች የባልነት ወይም የሚስትነት ማስረጃው የተሰጠው በቤተሰብ ሕጉ ስለጋብቻ መኖር ያለመኖር ሊቀርቡ የሚገባቸው የማስረጃ አይነቶች ሳይቀርቡ ነው፣ጋብቻ ሳይኖር ነው፣የቀረበው አቤቱታ ከሕጉ ስርዓት ውጪ ነው፤ሕጉን በሚጻረር መልኩ ነው የሚል ከሆነ ማስረጃዎች በማስረጃነቱ ከመስጠት ባለፈ በተጠቀሱት ነጥቦች ክርክር እንዲካሄድ በማድረግ ዳኝነት ሊሰጡ ይችላሉ? ወይስ አይችሉም? የሚል ነው፡፡ይህንኑ ጥያቄ ለመመለስ የባልነት ወይም የሚስትነት ማስረጃ ምንነት፣ማስረጃው የሚሰጥበትን ሁኔታ፣የማስረጃውን ይዘት፣አቤቱታው የሚስተናገድበትን ሥርዓት መመልከት አስፈላጊ ነው፡፡

    የጋብቻ ምስክር ወረቀት ስለሚሰጥበት ሁኔታና ስለይዘቱ የተሻሻለው የቤተሰብ ሕግአዋጅ ቁጥር 213/1992 ይደነግጋል፡፡ ይሄው ህግ ለጋብቻ መኖር መቅረብ ያለባቸውን የማስረጃ አይነቶች ቅደም ተከተል እንዲሁም በማስረጃው ሊረጋገጡ ስለሚገባቸውሁኔታዎች አስፍሮ እናገኛለን፡፡ከእነዚህ ድንጋጌዎች ይዘትና መንፈስ መገንዘብ የሚቻለው ፍርድ ቤቱ በሕጉ በተመለከተው አግባብ መረጋገጡን በቂ ነው ብሎ የገመተውን ያህል ማስረጃ ተቀብሎና መዝኖ ጋብቻ መኖር ያለመኖሩን የሚያረጋገጥ መሆኑን፣ጋብቻው አለ ወይም የለም ተብሎ ሊሰጥ የሚችለውም በሕግ የተቀመጠውን መመዘኛ በማሟላታቸው በመለየት ስለሆነ ይህንኑ የሚገልፅ ወይም የሚያሳይ ምክንያት በመስጠት ውሳኔ የሚሰጥ መሆኑን ነው፡፡በአንፃሩ የባልነት ወይም የሚስትነት ማስረጃ መስጠት ግን ከላይ የተመለከቱት ሕጋዊ ክርክሮች በሌሉበት ሁኔታ የሚሰጥ ማስረጃ እንጂ ጋብቻ ስለመኖሩ ያለመኖሩ ክርክር ተደርጎ የግራ ቀኙ ተከራካሪ ወገኖች ማስረጃ በሕጉ አይን ተመዝኖ የሚሰጥ አይደለም፡፡ፍርድ ቤቱ ጥያቄው ሲቀርብ የሚሰጠው ውሳኔ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕጉ ስለውሳኔ የተቀመጠውን ትርጉም የሚያሟላ ነው ሊባል የሚችል ሳይሆን የባልነት ወይም የሚስትነት የምስክር ወረቀቱን ስለሕጋዊ ማስረጃነቱ የሚያረጋገጥበት ነው፡፡ ይህን አይነት ውሳኔ ለመስጠት ፍርድ ቤቱ ሊከተለው የሚገባው ስነ ሥርዓት ሲታይም ተከራካሪ ወገን የሌለበት፣አቤቱታ አቅራቢው ብቻ በማስረጃ በተደገፈ አቤቱታ መሰረት ይገባኛል የሚለውን መብት ወይም ጥቅም ትክክለኛነቱን፣ሕጋዊነቱን እንዲረጋገጥለት የሚያቀርብ በመሆኑ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 305 መሰረት የተፋጠነ ሥርዓት ነው ሊባል የሚገባው ነው፡፡   ስለሆነም


    የባልነት ወይም የሚስትነት ማስረጃ ይሰጠኝ አቤቱታ ይዘቱና ፍርድ ቤቱ ሊከተለው  የሚገባው ስነ ሥርዓት ሲታይ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፍርድ ቤቶች የማስረጃ ይሰጠኝ ጥያቄውን ተገቢነቱን፣ ትክክለኛቱንና ሕጋዊነቱን ከማረጋገጥ ባለፈ ጋብቻ አለ ወይስ የለም? የሚለውን ጭብጥ ይዘው በጉዳዩ ላይ የቀረቡትን ማስረጃዎችን በመስማት፣ጉዳዩን በማጣራት እና ሌሎች ተያያዥነት ባላቸው ጉዳዮች ክርክር ሲኖር አቤቱታውን ተቀብሎ ለማስተናገድ የዳኝነት ሥረ ነገር ሥልጣን የሌላቸው መሆኑን ያስገነዝባል፡፡በጉዳዩ ላይ ሚስትነት ወይም ባልነት የለም የሚልና ተቃውሞውን ለማቅረብ መብትና ጥቅም ያለው ወገን ጋብቻው ያለመኖሩንና እና ተያያዥነት ያላቸውን ሌሎች ሕጋዊ ክርክሮችን መሰረት በማድረግ ተቃውሞ በማቅረብ ሕጋዊ መፍትሔ ሊያገኝ የሚገባው ጥያቄውን ወይም አቤቱታውን ለፌዴራል ፍርድ ቤቶች ለማቅረብ እንጂ ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፍርድ ቤቶች በማቅረብ አይደለም፡፡

    የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፍርድ ቤቶች በባልነት ወይም የሚስትነት ማስረጃ ወረቀት ላይ ውሳኔ ሰጥተዋል በሚል ምክንያት ብቻ ተቃውሞ ያለው ወገን የፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 358"ን" መሰረት በማድረግ የተቃውሞ አቤቱታ ሲያቀርብና ፍርድ ቤቶቹም አቤቱታውን ተቀብለው የባልነት ወይም የሚስትነት ማስረጃ ትክክለኛነቱንና ሕጋዊነቱን ከማረጋገጥ ባለፈ ተከራካሪ ወገኖችን በማከራከር ስለጋብቻ መኖር ያለመኖር ላይ ማስረጃ ሳይሆን በጋብቻ ውጤት ላይ የራሱ የሆነ ትርጉም ያለውንና ሊፈፀም የሚችል ውሳኔ ሲሰጡ በተግባር ይስተዋላል፡፡ይሁን እንጂ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 358 መሰረት የተቃውሞ አቤቱታ የሚቀርበው በፍትሐ ብሔር ሥነ ሥርዓት ሕጉ በተሰጠው የውሳኔ ትርጉም(አንቀፅ 3 ይመልክቷል) መሰረት ሊፈፀም የሚችል ውሳኔ ከተሰጠ እና ውሳኔው የክርክሩ ተካፋይ ያልሆነ ወገን መብትና ጥቅም የሚነካ መሆኑ ሲረጋገጥና አቤቱታው ውሳኔው ከመፈፀሙ በፊት ከቀረበ ነው፡፡የፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 358 አይነተኛ አላማ ማስረጃው ትክክለኛነቱና ሕጋዊነቱ ተረጋግጦ በማስረጃነቱ (Declaratory Judgement) በሚሰጠው ውሳኔ ላይ ሳይሆን ከላይ እንደተገለፀው ሊፈፀም በሚችል ውሳኔ የክርክሩ ተካፋይ ያልሆነ ወገን መብትና ጥቅምን ማስከበር ነው፡፡በአጠቃላይ የባልነት ወይም የሚስትነት ማስረጃ አቤቱታ ስለሚሰጥበት ሁኔታና ስለይዘቱ እንዲሁም  በፍ/ብ/ስ/ስ/ሕ/ቁጥር 358 መሰረት ተቃውሞ የሚቀርብበት ሥርዓት በአንድነት ሲታዩ የአዲስ አበባ ከተማ ፍርድ ቤቶች በዚህ ረገድ የማስረጃው ይሰጠኝ ጥያቄ /አቤቱታ/ ትክክለኛነቱንና ሕጋዊነቱን በማረጋገጥ ለማስረጃነት ውሳኔ ከመስጠት ባለፈ ማስረጃውን ትክክለኛነቱንና ሕጋዊነቱን የሚቃወም ወገን አቤቱታ ሲያቀርብ ለተቃውሞው መሰረት ሊሆኑ በሚችሉት ጋብቻ የለም፣ተገቢው ማስረጃ አልቀረበም፣የቀረቡት ማስረጃዎችም ሐሰተኛ ናቸው በሚሉት ነጥቦች ላይ ክርክር በመስማት ዳኝነት ለመስጠት በአዋጅ ቁጥር 361/1995"ም" ሆነ የዚሁ አዋጅ ማሻሻያ በሆነው አዋጅ ቁጥር 408/1996 መሰረት ሥልጣን ያልተሰጣቸው ሆኖ አግኝተናል፡፡

    ወደተያዘው ጉዳይ ስንመለስም ተጠሪ ለአዲስ አበባ ከተማ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አቤቱታ ሲያቀርቡ መሰረት ያደረጉት ከሟች ወ/ሮ ኪሮስ ጋር በጋብቻ ተሳስረው የነበሩ መሆኑን ጠቅሰው የባልነት ማስረጃ እንዲሰጣቸው ሲሆን ይህ ማስረጃ እንዲሰጣቸው ሲያመለክቱም አቤቱታቸውን በቃለ መሃላ ያስደገፉ መሆኑ የተረጋገጠ ሲሆን ፍርድ ቤቱም ለተጠሪ በተጠየቁት አግባብ ማስረጃ ከሰጠ በሁዋላ የአሁኗ አመልካች ተጠሪና ሟች ወ/ሮ ኪሮስ ውቤ ባልና ሚስት አይደሉም፣ጥያቄውና ማስረጃው የተሰጠበት አግባብ ሕጋዊ አይደለም የሚል ይዘት ያለው ተቃውሞ አቅርበዋል፡፡ይህ በግልፅ የሚያሳየው የአመልካች የተቃውሞ አቤቱታ ተጠሪ ያገኙት የባልነት ማስረጃ ከማስረጃነቱ ባለፈ ሌሎች የቤተሰብ ሕግ ክርክሮችን የሚያስነሳ መሆኑን ሲሆን ጉዳዩን በመጀመሪያ ደረጃ የተመለከተው የከተማው ፍርድ ቤትም የተሻሻለውን የፌዴራሉን የቤተሰብ ሕግ ሁሉ በመጥቀስ ውሳኔ መስጠቱን ከውሳኔው ተመልክተናል፡፡የአዲስ አበባ   ከተማ


    ፍርድ ቤቶች በአዋጅ ቁጥር 361/1995 እና 408/1996 መሰረት ካገኟቸው ሥልጣኖች መካከል ከመሰረታቸው የፌዴራል ጉዳዮች የሆኑት የሚገኙት ሲሆን እነዚህ ጉዳዮች ለእነዚህ ፍርድ ቤቶች ከፌዴራል ፍርድ ቤቶች ሥልጣን ተቆርሰው ሲሰጡ በሕግ አውጪው የታሰበው በባሕርያቸው ውስብስብ ያልሆኑ ናቸው በሚል ነው፡፡የጋብቻ መኖር ያለመኖር ውስብስብ ያልሆነ ክርክር የማይቀርብበት ሳይሆን ክርክር ተደርጎበት ውስብስብ የሕግ ጥያቄ ምላሽ የሚሰጥበት ነው፡፡በመሆኑም የአዲስ አበባ ከተማ ፍርድ ቤቶች የጋብቻ መኖር ያለመኖርን ለመወሰን ሥረ ነገር ስልጣን ያልተሰጣቸው በመሆኑ ጉዳዩ በአዲስ አበባ ከተማ ፍርድ ቤቶች መስተናገዱ ያላግባብ ነው፡፡ተጠሪ ያገኙትን ማስረጃ አመልካች ሊቃወሙት የሚገባቸው ስልጣን ባለው የፌዴራል ፍርድ ቤት ነው፡፡ስለሆነም የአዲስ አበባ ከተማ መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በአመልካች የቀረቡት ምክንያቶችን በመመልከት ጉዳዩን ለማስተናገድ ስልጣን የሌለው መሆኑን ገልፆ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 9 እና 231(1(ለ)) መሰረት መዝገቡን መዝጋት ሲገባው ጉዳዩን ማስተናገዱም ሆነ የበላይ ፍርድ ቤቶች ይህንኑ ሳያረጋግጡ የስር ፍርድ ቤትን ውሳኔ በትእዛዝ ማፅናታቸው መሰረታዊ የሆነ የሕግ ስህተት ሁኖ አግኝተናል፡፡በዚህም መሰረት ተከታዩን ወስነናል፡፡

     ው ሣ ኔ

    1. በአዲስ አበባ ከተማ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በመ/ቁጥር 961/02 ጥቅምት 16 ቀን

    2004 ዓ/ም ተሰጥቶ በከተማው ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤት በመ/ቁጥር 17036 ሕዳር 25 ቀን

    2004 ዓ/ም፣በከተማው ሰበር ሰሚ ችሎት በመ/ቁጥር 17119ታህሳስ 13 ቀን 2004 ዓ/ም የጸናው ውሳኔ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 348(1) መሰረት በአብላጫ ድምፅ ተሽሯል፡፡

    2. የአዲስ አበባ ከተማ ፍርድ ቤቶች የባልነት ወይም የሚስትነት ማስረጃ በተመለከተ የቀረበው ጥያቄ ትክክለኛነቱንና ሕጋዊነቱን በማረጋገጥ በማስረጃነቱ ውሳኔ (Declaratory Judgement) ከመስጠት ውጪ ማስረጃው የተሰጠበትን ውሳኔ መሰረት በማድረግ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 358 መሰረት የተቃውሞ አቤቱታ መቀበልና ጋብቻ መኖር ያለመኖርን ሌሎች ተያያዥነት ያላቸውን ክርክሮችን ለማስተናገድ የሥረ ነገር ሥልጣን የላቸውም ብለናል፡፡

    3. ተጠሪ አለኝ የሚሉትን ማስረጃ አመልካች በተጠሪና በሟች ወ/ሮ ኪሮስ ውቤ ጋር ጋብቻ የላቸውም የሚሉበትን ምክንያት መሰረት አድርገው ሊቃወሙ የሚችሉት በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 358 መሰረት ሳይሆን በሌላ ክስ ሁኖ ስልጣን ባለው በፌዴራሉ ፍርድ ቤት ነው ብለናል፡፡

    4.  በዚህ ችሎት ለተደረገው ክርክር የወጣውን ወጪና ኪሳራ የየራሳቸውን ይቻሉ ብለናል፡፡

     

    መዝገቡ ተዘግቷል፤ ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ፡፡

    የማይነበብ የአራት ዳኞች ፊርማ አለበት

     

     የሃ ሳብ ል ዩነ ት

     

    እኔ ስሜ በሶስተኛው ተራ ቁጥር የተጠቀሰው ዳኛ አብላጫው ድምፅ በሰጠው የሕግ ትርጉምና ከደረሰበት መደምደሚያ የማልስማማ በመሆኑ በሀሳብ ተለይቻለሁ፡፡

     

    የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፍርድ ቤቶች የወራሽነት፣ የባልና ሚስትነት የሞግዚትነትና የምስክር ወረቀት ለማግኘት የሚቀርብ አቤቱታ አከራክረው የመወሰን የዳኝነት ሥልጣን ያላቸው


    መሆኑ አዋጅ ቁጥር 361/1995 አንቀጽ 41/ሸ/ ለማሻሻል በወጣው አዋጅ ቁጥር 408/1996 አንቀጽ 1 በግልፅ ተደንግጓል፡፡

     

    የባልና ሚስትነት የምስክር ወረቀት ለማግኘት የሚቀርብ አቤቱታ፣ ባል ወይም ሚስት ነኝ በማለት አንድ ሰው የሚያቀርበውን ማመልከቻና መግለጫ ብቻ የሚመለከት አይደለም፡፡ የባልና ሚስትነት ምስክር ወረቀት ለማግኘት የሚቀርብ አቤቱታ ማናቸውም ያገባኛል የሚል ሰው ባል ወይም ሚስት አይደለም በማለት የሚያቀርበውን ተቃውሞና ክርክርን የሚጨምር እንደሆነ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ ህጉ አንቀጽ 80 ንዑስ አንቀጽ 1 "የአቤቱታ ፅሁፍ ማለት ከሳሽ የሚጠይቀውን ሁሉ ዘርዝሮ የሚገልፅ ፅሁፍ፣ ተከሳሽ የሚሰጠው የመከላከያ ፅሁፍ፣ የተከሳሽ ከሳሽ የሚያቀርበው ፅሁፍ የይግባኝ ማቅረቢያ ፅሑፍ ወይም በሌላ አይነት ተፅፎ ለፍርድ ቤትና ክስ መነሻ ወይም ለዚሁ መልስ የሚመለከት ማናቸውም ፅሑፍ ነው በማለት የሰጠውን ሰፊ ትርጉም በማየት ለመረዳት ይቻላል፡፡

     

    ከአዋጅ ቁጥር 408/1996 አንቀጽ 1 የባልና ሚስትነት የምስክር ወረቀት ለማግኘት የሚቀርብ አቤቱታ የመዳኘት ሥልጣን የአዲስ አበባ ፍርድ ቤቶች እንደሆነ ሲደነግግ፣ አንዲት ሴት የአንድ ሰው ሚስት መሆኔ ተጣርቶና በማስረጃ ተረጋግጦ ይወሰንልኝ በማለት የምትጠይቀውን የዳኝነት ጥያቄ ወይም አንድ ሰው የአንዲት ሴት ባል መሆኔ ተጣርቶና በማስረጃ ተረጋግጦ ውሳኔ ይሰጥልኝ በማለት በሚያቀርበው የዳኝነት ጥያቄ ላይ ባል ነው የተባለው ሰው ወይም ሚስት ናት የተባለችው ሰው በህይወት ያለች ከሆነ የመከላከያ መልሷንና ማስረጃዋን  እንድታቀርብ በማድረግ፣ ፍሬ ጉዳይ በማጣራት፣ ማስረጃ በመመርመርና በመመዘን በሁለቱ ተከራካሪዎች መካከል ህጋዊ ዕውቅና ያለው ጋብቻ መኖሩን ወይም አለመኖሩን የመወሰን ሙሉ ሥልጣን ያላቸው መሆኑን የሚያጠቃልል ነው፡፡

     

    ከዚህ በተጨማሪ የባልነት ወይም ሚስትነት የምስክር ወረቀት እንዲሰጥና አቤቱታ የቀረበው አንደኛው ወገን ላይ የመጥፋት ውሳኔ ከተሰጠ በኋላ ወይም አንደኛው ወገን ከሞተ በኋላ እንደሆነ፣ በፍትሐብሔር ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 41 መሰረት በጉዳዩ ጣልቃ ገብተው የመከራከር መብት ያላቸው ሰዎች የሚያቀርቡትን ክርክርና የመከላከያ ማስረጃ በተሟላ ሁኔታ በመስማት ተገቢውን ውሳኔ የመስጠት ሥልጣንን የሚያካትት ስለመሆኑ የአዋጅ ቁጥር 408/1996 አንቀጽ 1 ድንጋጌ ከፍትሐብሔር ሥነ ሥርዓት ህግ ቁጥር 41 ድንጋጌ ጋር በማጣመር ለመገንዘብ ይቻላል፡፡

     

    የአዲስ አበባ አስተዳደር ፍርድ ቤቶች ባል ወይም ሚስት መሆናቸውን የሚያረጋገጥ ማስረጃ ከመስጠታቸው በፊት፣ ተገቢውን የፍሬ ጉዳይ ማጣራት በማድረግ፣ አስፈላጊም በሆነ ጊዜ በፍትሐብሔር ሥነ ሥርዓት ህግ ቁጥር 145/1/ እና በፍትሐብሔር ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 264 መሠረት ተጨማሪ የሰነድና የሰው ማስረጃ በማስቀረብ ፣ ውሣኔ የመስጠት ኃላፊነት ያለባቸው የከተማው ፍርድ ሰጭ ተቋማት መሆናቸውን በአዋጅ ቁጥር 361/1995 አንቀፅ 39 ተደንግጓል፡፡

     

    የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፍርድ ቤቶች ባል መሆኑ ወይም ሚስት መሆኗ ተጣርቶና ተረጋግጦ ማስረጃ እንዲሰጣቸው የቀረቡ የዳኝነት ጥያቄዎችን ፣ ለጉዳዩ መልስ መስጠት ያለበት

    - የትዳር አጋር /ካለ/ች/ መልስ እንዲሰጡና መከላከያ ማስረጃ እንዲያቀርቡ በማድረግ፣ በራሳቸው አነሳሽነት ተጨማሪ የሰውና የፅሑፍ ማስረጃ በማስቀረብ ወይም በጉዳዩ ጣልቃ ገብ ተከራካሪ


    ወገን ሊሆን የሚችል ሰው ሲቀርብ በፍትሐብሔር ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 41 መሠረት የጣልቃገቡን ክርክርና ማስረጃ በመስማት በአንድ ወንድና በአንዲት ሴት መካከል ጋብቻ መኖሩን ወይም በጋብቻ አለመኖሩን በማረጋገጥ የሰጡት ውሣኔ መብቴንና ጥቅሜን ይነካብኛል፤ በክርክሩ ተካፋይ መሆን ነበረብኝ የሚለው ሰው በክርክሩ ተካፋይ ያልሆነ ሰው ቀደም ብሎ የተሰጠውን ውሣኔ ለማሰረዝ የፍርድ መቃወሚያ የሚያቀርበው ቀደም ብሎ ጋብቻ መኖሩን ወይም አለመኖሩን አከራክሮና አጣርቶ ለወሰነው ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፍርድ ቤት እንደሆነ የአዋጅ ቁጥር 408/1996 አንቀፅ 1 ድንጋጌና የፍትሐብሔር ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 358 እና በፍትሐብሔር ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 359 ንዑስ አንቀፅ 1 “መቃወሚያው የሚቀርበው በአቤቱታ አቀራረብ መልክ ሆኖ ተገቢው ዳኝነት ተከፍሎበት፣ መቃወሚያ ያቀረበለትን ለወሰነው ፍርድ ቤት ነው” በማለት በግልፅ የደነገገውን ድንጋጌ ይዘት መንፈስና ዓላማ በማገናዘብ ለመረዳት ይቻላል፡፡

     

    ስለሆነም በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፍርድ ቤቶች የባል ወይም ሚስት ስለመሆን የቀረበላቸውን አቤቱታ ተቀብለው አጣርተው በሰጡት ውሣኔ ላይ የሚቀርብን  የፍርድ መቃወሚያ አቤቱታ ተቀብሎ የማስተናገድ ሙሉ የዳኝነት ሥልጣን አላቸው፡፡ አብላጫው ድምፅ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፍርድ ቤቶች ጋብቻ አለ ወይም የለም በሚለው ጭብጥ ላይ መከራከር ያለባቸውን ሰዎች ክርክር በመስማት አስፈላጊውን ማጣራት በማድረግ ውሣኔ እንደማይሰጡና ሥልጣን እንደሌላቸው በመቁጠር፣ የፍርድ መቃወሚያው መቅረብ ያለበት ለፌዴራል ፍርድ ቤቶች መሆን አለበት በማለት የሰጠው ትርጉም የአዋጅ ቁጥር 408/96 አንቀፅ 1፣ የፍትሐብሔር ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር አንቀጽ 80/1/፣ አንቀጽ 41 እና አንቀጽ 358፣ አንቀጽ 359/1/፣ ድንጋጌዎች ይዘትና ተግባራዊ ተፈፃሚነት መሠረት ያደረገ ነው የሚል እምነት የሌለኝ በመሆኑ፣ በጉዳዩ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፍርድ ቤቶች የፍርድ መቃወሚያውን በመቀበል የማከራከርና የመወሰን የዳኝነት ሥልጣን አላቸው፡፡ ስለሆነም ጉዳዩ ጭብጥ በተያዘበት በዳኝነት ሥልጣንን መሠረት በማድረግ ሳይሆን የአዲስ አበባ ፍርድ ቤቶች የተጠሪን የፍርድ መቃወሚያ በመቀበል የሰጡት ውሣኔ መሠረታዊ የሕግ ስህተት ያለበት ነው ወይስ አይደለም? በሚለው ነጥብ ላይ ግራ ቀኙን በማከራከር ውሣኔ ሊሰጠው ይገባ ነበር በማለት በሀሳብ ተለይቻለሁ፡፡

     

     

    የማይነበብ የአንድ ዳኛ ፊርማ አለበት፡፡

  • የባልና ሚስት ጋብቻ ፈርሶ የጋራ የሆነ ንብረት  ክፍፍል በሚፈፀምበት ጊዜ በፍ/ሕጉ ላይ የተቀመጡት በቅድሚያ የመግዛት መብት ድንጋጌዎች ተፈፃሚነት የሌላቸው ስለመሆኑ

     

    የፍ/ሕ.ቁ. 1386፣1388፣1391፣1392፣1393፣(1)፣1397

    የሰ/መ/ቁ.88275

    ጥር 19 ቀን 2007.ዓ.ም

     

    ዳኞች፡-አልማው ወሌ

    ዓሊ መሐመድ ሡልጣን አባተማም ሙስጠፋ አህመድ ተኽሊት ይመሰል

    አመልካች፡- አቶ ኃይለሚካኤል ልኬ ሎሶ - የቀረበ የለም ተጠሪ፡- 1. አቶ መኮነን በለጠ - ጠበቃ መለሰ ጦና ቀረቡ

    2. ወ/ሮ አምሳለች ዘበን - አልቀረቡም መዝገቡን መርምረን የሚከተለውን ፍርድ ሰጥተናል፡፡

     ፍ ርድ

     

    ጉዳዩ የቅድሚያ ግዥ መብት ጥያቄ የሚስተናገድበትን የሕግ አግባብ የሚመለከት ሲሆን ክርክሩ የተጀመረውም በሐዋሳ ከተማ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የአፈፃጸም ከሳሽ የሆኑት የአሁኗ 2ኛ ተጠሪ በአሁኑ አመልካች ላይ በዋናው ፍርድ መሰረት እንዲፈፅምላቸው ባቀረቡት የአፈጻም ክስ መነሻ ነው፡፡ የአሁኑ አመልካችና 2ኛ ተጠሪ ባልና ሚስት የነበሩ ሲሆን ጋብቻው በፍርድ ቤት ውሳኔ ፈርሶ የጋብቻ ውጤት ከሆኑት ንብረቶች መካከል ለአሁኑ ክርክር መነሻ የሆነውን መኖሪያ ቤት በክልሉ የቤተሰብ ሕግ መሰረት የተቀመጡት የክፍፍል ስርዓቶችን መሰረት በማድረግ ቤቱ በግልጽ ጨረታ መሸጥ እንደአለበት ፍርድ ቤቱ ውሳኔ አሳርፎ የጨረታ ማስታወቂያ ወጥቶ የአሁኑ 1ኛ ተጠሪተወዳድረው የጨረታ አሸናፊ በመሆን የቤቱ ገዥነታቸው ከታወቀ  በኋላ የአሁኑ አመልካች ቤቱን የመልሶ መግዛት መብት እንደአላቸው ጠቅሰው ቤቱን እንዲያስቀሩ እንዲወሰንላቸው ለፍርድ ቤቱ አመልክተው የአሁኑ ተጠሪዎች ይህንኑ የአመልካችን ጥያቄ ተቃውመው የመልሶ መግዛት መብት ለአመልካች ሊሰጣቸው አይገባም የሚለውን መከራከሪያ ሁለቱም ተጠሪዎች ከማቅረባቸውም በተጨማሪ የአሁኗ 2ኛ ተጠሪ አመልካች አዲስ አበባ ውስጥ መንግስት በሰጣቸው ደረጃውን በጠበቀ ቤት እንደሚኖሩና ራሳቸው ግን ሁለት ልጆችን ይዘው ቤት የሌላቸው መሆኑን ጠቅሰው የመልሶ መግዛት መብት ለራሳቸው እንዲጠበቅላቸው ጭምር ዳኝነት ጠይቀዋል፡፡የሀዋሳ ከተማ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤትም የግራ ቀኙን ክርክር መርምሮ የአመልካች ጥያቄ ተቀባይነት የለውም በማለት ውደቅ አድርጎ የጨረታውን ውጤት እንዲቀጥል ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡በዚህ የስር ፍርድ ቤት ትዕዛዝ የአሁኑ አመልካች ቅር በመሰኘት ይግባኛቸውን ለሐዋሳ ከተማ ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቅርበው ፍርድ ቤቱም ግራ ቀኙን ከአከራከረ በኋላ ጉዳዩ በክልሉ የቤተሰብ ሕግ የሚገዛ ቢሆንም የክልሉ የቤተሰብ ሕግ ስለመልሶ የመግዛት መብት የሚደነግገው ጉዳይ ያለመኖሩንና በዚህ ሁኔታ ደግሞ በፍትሐ ብሔር ሕጉ የጋራ ንብረትን መልሶ ስለመግዛት የተደነገጉትን ድንጋጌዎችን ተፈፃሚ ማድረግ በሕግ አተረጓጎም መርህ ተገቢ መሆኑን ጭምር ዘርዝሮ የአመልካች ቤቱን መልሶ የመግዛት መብታቸው ሊጠበቅ ይገባል በማለት የስር ፍርድ ቤትን ትዕዛዝ ሽሮታል፡፡በዚህ ውሳኔ የአሁኑ ተጠሪዎች ቅር በመሰኘት ይግባኛቸውን ለክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ   ችሎት


    አቅርበው ተቀባይነት ያጡ ሲሆን የሰበር አቤቱታቸውን በተናጠል ለክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት አቅርበው ችሎቱ ግራ ቀኙን ከአከራከረ በኋላ መዝገቦችን አጣምሮ በመመርመር የአሁኑ አመልካች የመልሶ መግዛት መብት አላቸው ተብሎ የተሰጠውን የከተማውን ከፍተኛ ፍርድ ቤት ውሳኔ እና ይህንኑ ውሳኔ ያጸናውን የክልሉን ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ትዕዛዝ ሽሮ የከተማው የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የሰጠውን ትዕዛዝ አፅንቶታል፡፡የአሁኑ የሰበር አቤቱታ የቀረበውም ይህንኑ ውሳኔ በመቃወም ለማስለወጥ ነው፡፡የአመልካች የሰበር አቤቱታ መሰረታዊ  ይዘትም፡- የጋብቻ ውጤት የሆነውን ቤት መልሶ ለመግዛት በፍትሃ ብሔር ሕጉ በአንቀጽ 1261፣ከአንቀፅ 1386- 1409 ስር የተጠቀሱት ድንጋጌዎች መብት የሚሰጣቸው ሁኖ እያለ የክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት ጉዳዩ በክልሉ የቤተሰብ ሕግ መሰረት የሚዳኝ እንጂ በፍትሐ ብሔር ሕጉ ድንጋጌዎች የሚዳኝ አይደለም በማለት የሰጠው ውሳኔ ተገቢውን የሕግ አተረጓጎምና አተገባበር ያልተከተለ ከመሆኑም በላይ በዚህ ችሎት በሰ/መ/ቁጥር 37297 የተሠጠውን አስገዳጅ የሕግ ትርጉም ያላገናዘበ ነው በማለት መከራከራቸውን የሚያሳይ ነው፡፡የሰበር አቤቱታቸው ተመርምሮም ከተጠቃሽ ድንጋጌዎችና ከክልሉ የቤተሰብ ሕግ አንጻር የአመልካች ጥያቄ ውድቅ የመደረጉን አግባብነት ለመመርመር ሲባል ለዚህ ችሎት እንዲቀርብ የተደረገ ሲሆን ለተጠሪዎች ጥሪ ተደርጎላቸው ቀርበውም ግራ ቀኙ በጽሑፍ እንዲከራከሩ ተደርጓል፡፡

    የጉዳዩ አመጣጥ አጠር አጠር ባለ መልኩ ከላይ የተገለፀው ሲሆን ይህ ችሎትም የግራ ቀኙን የጽሁፍ ክርክር የሰበር አቤቱታ ከቀረበበት ውሳኔ እና አግባብነት ካላቸው የህግ ድንጋጌዎች ጋር በማገናዘብ ጉዳዩ ለሰበር ችሎቱ ሲቀርብ ከተያዘው ጭብጥ አንፃር በሚከተለው መልኩ መርምሮታል፡፡ጉዳዩ ለሰበር ሲቀርብ የተያዘው ጭብጥ የአሁኑ አመልካች የጋራ ንብረት ነው የሚለውን ቤት ከ1ኛ ተጠሪ መልሶ የመግዛት መብት ያለው መሆኑ አለመሆኑን፣ከፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 1394፣ ከቁጥር 1405-1408 ከተመለከቱት ድንጋጌዎች እና የፍትሐብሔር ሕጉ ስለ ጋራ ባለሃብትነት በቁጥር 1257 እና የሚቀጥሉት አንቀጾች የደነገገውን ከክልሉ የቤተሰብ ሕግ አንቀጽ 103(2) እና 102 ድንጋጌዎች አኳያ ለመመርመር ተብሎ በመሆኑ ከዚሁ ጭብጥ አንጻር እንደሚከተለው ተመልክተናል፡፡

    በክርክሩ ሂደት መገንዘብ የተቻለው አመልካችና 2ኛ ተጠሪ በቤቱ ላይ እኩል መብት ያላቸው መሆኑን፣የቤቱ የክፍፍል ስርዓት እንዲፈጸም የተደረገውም የክልሉን የቤተሰብ ሕግ መሰረት በማድረግ መሆኑን፣አመልካች አሁን አጥብቀው የሚከራከሩት የክልሉ የቤተሰብ ሕግ ስለመልሶ መግዛት የሚያስቀምጠው መፍትሄ ስለሌለ በፍትሐ ብሔር ሕጉ ያሉት ድንጋጌዎች ተፈፃሚነት ሊኖራቸው ይገባል በማለት መሆኑን፣2ኛ አመልካችም ቤቱን መልሶ የመግዛት መብት ሊጠበቅልኝ ይገባል በማለት ያቀረቡት ጥያቄ እስከዚህ ሰበር ሰሚ ችሎት ደርሶ ተቀባይነት ያጣ መሆኑን የሰ/መ/ቁጥር 90586 የሚያሳይ መሆኑን፣1ኛ አመልካች አከራካሪውን ቤት የገዙት በግልጽ በተደረገው ጨረታ ተወዳድረው ጨረታው ሕጋዊነቱ ተረጋግጦ መሆኑን ከመሆኑም በላይ በዚህ የጨረታ ሂደት አመልካችም ሆነ የአሁኗ 2ኛ ተጠሪ እንዲሳተፉ ጨረታው እንዲከናወን ያዘዘው የሥር ፍርድ ቤት ትዕዛዝ ያልሰጠበት ጉዳይ መሆኑን ነው፡፡

    በመሰረቱ የባልና ሚስት የጋራ ንብረት ክፍፍል ስርዓት በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ መንግስትም ሆነ በክልል ሕግጋት መንግስታት የተረጋገጠውን የእኩልነት መብት መሰረት አድርጎ መከናወን ያለበት ጉዳይ ነው፡፡ የባልና ሚስት የጋራ ንብረት ክፍፍል ስርዓት የሚከናወንበትን መንገድ የተሻሻለው የፌዴራል የቤተሰብ ሕግ አዋጅ ቁጥር 213/1992 በቅደም ተከተል ያስመቀጣቸው መንገዶች ከአንቀፅ 90 እስከ 93 ድረስ ባሉት የሰፈሩ ሲሆን ስራ ላይ ያሉት የክልል የቤተሰብ ሕግጋትም አግባብነት ያላቸውን ድንጋጌዎችን ይዘው እናገኛለን፡፡ ለተያዘው ጉዳይ ቀጥተኛ ተፈፃሚነት ያለው የክልሉ የቤተሰብ ሕግ አዋጅ ቁጥር 75/1996 ሲታይም የባልና ሚስት ንብረት የሚከፋፈልበትን ሥርዓት ከአንቀፅ    101


    እስከ 105 ድረስ ባሉት ድንጋጌዎች አካቶ ይዟል፡፡ ከእነዚህ ድንጋጌዎች ይዘትና መንፈስ መገንዘብ የሚቻለውም የጋብቻ ውጤት የሆነው የጋራ ንብረት ክፍፍል ሊከናወን የሚገባው የእኩልነት መርህን መሰረት አድርጎና የተጋቢዎችን ፈቃድ በመመርኮዝ መሆኑን ነው፡፡የተጋቢዎች ስምምነት ከሌለ ደግሞ ክፍፍሉ መፈፀም ያለበት በሕጉ የተመለከተውን ቅደም ተከተል መሰረት አድርጎ ሊሆን እንደሚገባ ሕጉ ያስገነዝባል፡፡በመሆኑም የጋብቻ ውጤት የሆነውን ንብረት ለማከፋፈል የበላይነት ያለው የቤተሰብ ህጉ ነው፡፡

     

    በመሰረቱ በፍ/ብ/ሕጉ አንቀጽ 1386 እና ተከታዩቹ የተመለከተው ድንጋጌ ተፈፃሚነት የሚኖረው የጋራ ባለሐብቶች ለሆኑ ወገኖች እንዲሁም የጋራ ባለሐብት የሆኑ ወራሾች መካከል ስለመሆኑ የፍ/ብ/ሕግ ድንጋጌ ቁጥር 1388 እና 1392 ይዘት ያመለክታል፡፡ በመሆኑም በቅድሚያ የመግዛት መብት በሕግ ጥበቃ የተደረገለት መብት ሲሆን ሕጉ ሊያሳካ ያሰበው አላማም ከዘር የወረደ ንብረትን በተመለከተ ዘመዳሞች የሚኖራቸውን ስሜት ለመጠበቅና ከቤተሰቡ እጅ ወጥቶ ወደ ሌላ ወገን እንዳይተላለፍ ነው ተብሎ ይታሰባል፡፡በዘመዳሞች መካከል ይህ መርህ ተፈጻሚ የሚሆነው በውርስ ሀብት ላይ ሲሆን መብቱን ተግባራዊ የሚያደርጉትም በፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 1391 ስር እንደተመለከተው በወራሽነት ቅደምተከተላቸው መሰረት ነው፡፡ ለቅድሚያ ግዥ መብት የሚወዳደሩት  በእኩል የዝምድና ደረጃ ላይ የሚገኙ ሰዎች የሆኑ እንደሆነ በመሬቱ ላይ የሚኖረውና የሚጠቀምበት ሰው ቅድሚያ የሚሰጠው መሆኑ በፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 1392 ስር በግልጽ ተመልክቷል፡፡ ይህ ካልተቻለ ደግሞ መሬቱን በአንድነት እንደሚሰሩበት እኩል በሆነ ድርሻ የጋራ ባለሃብቶች እንደሚሆኑ የፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 1393(1) ድንጋጌ ያሳያል፡፡በሌላ በኩል ሕጉ በባለጥቅሞቹ ላይ ያስቀመጠው ገደብም ያለ መሆኑን የፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 1397 ድንጋጌ ያሳያል፡፡በዚህ ድንጋጌ መሰረት ባለጥቅሞቹ በቀዳሚነት የመግዛት መብትን ለሌላ ሰው ሊያስተላልፉ እንደማይችሉና እንዲሁም በእዳ ሊያዝ እንደማይችል አስገዳጅነት ባለው ሁኔታ ተቀምጧል፡፡ሌላው ስለቅድሚያ የመግዛት መብት በሕጉ የተቀመጠው ጉዳይ የመብቱ የተፈፃሚነት ጊዜ ነው፡፡በዚህም መሰረት በቅድሚያ የመግዛት መብት ተፈጻሚ የሚሆነው ባለሃብቱ ሀብቱን ወይም የሀብቱን አላባ በዋጋ በሚሸጥበት ጊዜ ስለመሆኑ የፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 1398 ድንጋጌ የሚያመላክት ሲሆን የፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 1407(1) ድንጋጌም ንብረቱ የተላለፈው ያለ ዋጋም ቢሆንም ግምቱን በመክፈል ይገባኛል ባዩ ሊገለገልበት እንደሚችል ያስረዳል፡፡እንዲሁም የፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 1400 ድንጋጌ ማንም ሰው በቀዳሚነት ይገባኛል በማለት መብት ሊገለገልበት የፈለገ እንደሆነ ንብረቱ በሀብትነት ወይም በአላባነት ለገዥ ወይም በሐራጅ ለሚገዛው ሰው የተላለፈ መሆኑ ለይገባኛል ባዩ ከተነገረበት ቀን አንስቶ በሁለት ወር ጊዜ ውስጥ በመብቱ ሊገለገልበት የፈለገ መሆኑ ካስታወቀ መብቱ እንደሚቀርበት አስገዳጅነት ባለው ሁኔታ አስቀምጧል፡፡ የፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 1401 ደግሞ በቀዳሚነት ይገባኛል በማለት መብት እንዲገለገልበት ለመጠየቅ የማስተላለፍያ ማስታወቂያ ሳይነገር የቀረ እንደሆነ የጋራ ባለሃብቶቹ በማያጠራጥር አኳኋን ንብረቱ ለሌላ ሰው የተላለፈ መሆኑን ካወቁበት ቀን አንስቶ በሚቆጠር በሁለት ወር ጊዜ ውስጥ በቀዳሚነት ይገባኛል  በማለት በመብታቸው ሊገለገሉበት የፈለጉ መሆናቸውን ማስታወቅ እንደአለባቸውና የስጋ ዘመዳሞች ከሆኑ ደግሞ አዲሱ ባለሃብት ወይም የአላባ ጥቅም ተቀባዩ የማይንቀሳቀሰውን ንብረት እጅ ካደረገበት ቀን አንስቶ በሚቆጠር በስድስት ወር ጊዜ ውሰጥ በቀዳሚነት ይገባናል በማለት መብታቸውን ሊገለገሉበት የፈለጉ መሆናቸውን ማስታወቅ እንደአለባቸው እንደቅደምተከተሉ በተጠቃሹ ቁጥር ንዑስ አንቀጽ አንድ እና ንዑስ አንቀጽ ሁለት ድንጋጌዎች ስር በሕጉ የተመለከተውን ጊዜ ያለማስታወቅ እና ውጤቱን በተመለከተ ደንግገው እናገኛለን፡፡


    እንግዲህ በቀዳሚነት የመግዛት መብትን አድማስ በተመለከተ በሕጉ የተቀመጡ ሁኔታዎች ከላይ የተቀመጡ ከሆኑ አሁን የተያዘው ጉዳይም እልባት ማግኘት ያለበት ከእነዚህ ድንጋጌዎች ይዘትና መሰረታዊ አላማ እንዲሁም ጉዳዩን በተለይ ለመግዛት የወጣው ህግ ድንጋጌዎች አንፃር ነው፡፡ከዚህ አኳያ ጉዳዩን ስንመለከተው አመልካችና 2ኛ ተጠሪ በንብረቱ ላይ እኩል መብት ያላቸው ቢሆንም አንዱ ከሌላው በቅድሚያ ቤቱን መልሶ የመግዛት መብት የሚያገኝበት አግባብ የለም፡፡ የክልሉ የቤተሰብ ሕጉ በአንቀጽ 102 ስር ክፍፍሉ መሰረት ከሚያደርግባቸው ሁኔታዎች አንዱ ንብረቱ የተለየ ጥቅም የሚሰጠውን ተጋቢ መለየት እንደሆነ በተመለከተው አግባብም ለአመልካች ቤቱ እንዲሰጥ የሚደረግበት ህጋዊ ምክንያት መኖሩ አልተረጋገጠም፡፡ጉዳዩን የሚገዛው ልዩ ሕግ ስለ አንድ ክርክር መፍትሔ ለመስጠት የሚያስችል ድንጋጌ ባልያዘበት ሁኔታ አግባብነት ያላቸው ሌሎች ሕጎች ስር ያሉትን ድንጋጌዎችን መሰረት አድርጎ ለአንድ የክርክር ጭብጥ መፍትሔ መስጠት ተገቢ መሆኑን ተቀባይነት ያላቸው የህግ አተረጓጎም ደንቦች የሚያስገነዝቡን ጉዳይ ቢሆንም በዚህ ጉዳይ ግን በክልል የቤተሰብ ሕግ የጋብቻ ውጤት የሆነው ንብረት ክፍፍል የሚፈፀምበትን አግባብ በግልጽ የተቀመጠ በመሆኑና ተጋቢዎች ግራ ቀኙ በሚያደርጉት ስምምነት መሰረት ክፍፍሉ ሊፈጸም ያልቻለ ከመሆኑም በላይ 2ኛ ተጠሪም የመልሶ መግዛት ጥያቄ ያቀረቡ በመሆኑ የአሁኑ አመልካች ንብረቱን መልሰው የመግዛት መብት የሚያገኙበት አግባብ ከፍትሃ ብሔር ሕጉ ድንጋጌዎች አንፃር የሚታይበት አግባብ የለም፡፡ጨረታው እንዲከናወን ያደረገው የሥር ፍርድ ቤትም የግራ ቀኙን ተጋቢዎች መብት አነጻጽሮ በጨረታው ላይ እንዲሳተፉና መልሶ የመግዛት መብት እንደሚኖራቸው ከመነሻውም ግልጽ ትዕዛዝ ያልሰጠበት መሆኑን ክርክሩ ያሳያል፡፡ በዚህ አግባብ በጨረታው ላይ ተወዳድሮ የጋብቻ ውጤት የሆነውን ንብረት የገዛ ተጫራች የጨረታው ውጤት ከታወቀ በኋላ ንብረቱን ለጋራ ባለሃብት መልሶ እንዲሸጥ ማድረግ የባልና ሚስት ንብረት በሐራጅ እንዲሸጥ በሚደረግበት ጊዜ ተወዳዳሪ እንዲቀርብ ያለማድረግ ውጤት የሚያስከትል በመሆኑ ተቀባይነት አግኝቶ ሊተገበር የሚገባው አይደለም፡፡ስለሆነም ጉዳዩ ልዩ ሕግ በሆነው የክልሉ የቤተሰብ ሕግ የሚዳኝ እና በዚህ ሕግ የተቀመጡ የክፍፍል ስርዓቶች ደግሞ የጋራ ባለሃብት መብቱን እንዲጠቀም የሚያስችሉ ቅደም ተከተል ያላቸው በመሆኑ አመልካችና 2ኛ ተጠሪ በዚህ በህጉ በተቀመጡ ቅደም ተከተሎች መጠቀም ሳይችሉ ከቀሩ በኋላ በጨረታው ላይ የመልሶ መግዛት መብት እንዳላቸው ባልተቀመጠበትሁኔታ ሶስተኛ ወገኖች ተወዳድረው አሸናፊው ከተለየ በኋላ ንብረቱን መልሰን እንግዛ ሲሉ ጥያቄው በዚህ ረገድ በተደነገጉት የፍትሐ ብሔር ድንጋጌዎች የሚታይበት አግባብ የሌለ ሁኖ አግኝተናል፡፡ሲጠቃለለም የክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት በጉዳዩ ላይ የሰጠው ውሳኔ ሕጋዊ እንጂ መሰረታዊ የሆነ የሕግ ስህተት ያለበት ነው ለማለት አልተቻለም፡፡በዚህም ምክንያት ተከታዩን ወስነናል፡፡


     

     

     ው ሣ ኔ

     

    1. በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦች ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ጠቅላይ ፍርድ ቤት በመ/ቁጥር 58418 መጋቢት 06 ቀን 2005 ዓ/ም የተሰጠው ውሳኔ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 348(1) መሰረት ጸንቷል፡፡

    2. አመልካች አከራካሪውን ቤት የመልሶ መግዛት መብት የላቸውም ተብሎ መወሰኑ ባግባቡ ነው ብለናል፡፡

    3.  በዚህ ችሎት ለተደረገው ክርክር የወጣውን ውጪ እና ኪሳራ የየራሳቸውን ይቻሉ ብለናል፡፡

     ት ዕ ዛዝ

    ነሐሴ 07 ቀን 2005 ዓ/ም ተሰጥቶ የነበረው እግድ ተነስቷል፡፡ ለሚመለከታቸው አካላት ይጻፍ፡፡

     

    መዝገቡ ተዘግቷል፤ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ ብለናል፡፡

     

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት ::

     

     

    መ/ተ

  • የDNA ምርመራ እንዲደረግ ትዕዛዝ መሰጠቱ አንደኛው ወገን አሉኝ የሚላቸውን የመከላከያ ማስረጃዎች የማሰማት መብት የማይከለክል ስለመሆኑ፣

     

    የDNA ምርመራ እንዲረግ ፍ/ቤት ትዕዛዝ ስለሚሠጥበት አግባብ፣

     

    የሰ//.90121 ቀን 28/01/2007 ዓ/ም

     

    ዳኞች፡-አልማው ወሌ

     

    ሱልጣን አባተማም መኮንን ገ/ህይወት ሙስጠፋ አህመድ ተኽሊት ይመለስ

    አመልካች፡- አቶ ………ጠበቃ ሀይልዬ ሰሀለ ቀረቡ ተጠሪ፡- አቶ …………- ቀረቡ

    መዝገቡ ተመርምሮ ተከታዩ ፍርድ ተሰጥቷል

     

     ፍ ር ድ

     

    በዚህ በመዝገብ የቀረበው ክርክር የአባትነት ይረጋገጥልኝ ጥያቄ የሚመለከት ነው፡፡ ለክርክሩ ምክንያት የሆነው ጉዳይ የተጀመረው በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የአሁን ተጠሪ ከሳሽ በመሆን በአመልካች ላይ ያቀረቡትን ክስ እናታቸው ወ/ሮ ….. ከአመልካች ጋር ከጥር ወር 1973 ዓ/ም እሰከ ህዳር ወር 1974 ዓ/ም ድረስ ጋብቻ ሳይኖር እንደባልና ሚስት አብሮው በመቂ ከተማ ድግዳቦራ ወረዳ ቀበሌ 02 የቤት ቁጥር 190 ወስጥ ሲኖሩ መቆያታቸውን ገልጸው በዚህ ግንኙነታቸው መሰረት ተጠሪ በጋንዲ ሆስፒታል ሚያዝያ 02 ቀን 1974 ዓ/ም የተወለዱ መሆናቸውን በመግለጽ አመልካች የተጠሪ አባት ነው ተብሎ እንዲወሰን የሚጠይቅ ነው የአሁን አመልካች በስር ፍርድ ቤት በሰጡት መልስ ልጅነት የሚረጋገጠው የተሻሻለው የቤተሰብ ህግ አዋጅ ቁጥር 213/1992 አንቀፅ 154 እና 155 ላይ እንደተመለከተው የልደት ምስክር ወረቀት በማቅረብ መሆኑን፤ተጠሪ ያቀረቡትማስረጃ አለመኖሩ አመልካች መቂ  ከተማ  ኑረው እንደማያወቁ ተጠሪም አንድም ቀን እራሳቸውም ሆነ በሰው የአመልካች ልጅ መሆናቸው ጠይቀው እንደማያውቁ በመጥቀስ ክሱ ውድቅ ተደርጐ እንዲሰናበቱ አመልክተዋል፡፡

     

    የስር ፍርድ ቤት የተጠሪ ሁለት ምስክሮች በማዳመጥ በሰጠው ውሳኔ በአሁን አመልካች እና የተጠሪ እናት እንደ ባልና ሚስት አብረው ይኖሩ ነበር በሚል ስላልተረጋገጠ የአመልካች ምስክር መስማት አያስፈልግም፡፡ የአመልካች እና የተጠሪ እናት ግንኙነት በተሻሻለው የቤተሰብ ህግ አዋጅ ቁጥር 213/1992 አንቀጽ 143 በሚያዘው አግባብ ሳይረጋገጥ የደም ምርመራ (የDNA ምርመራ) ማድረግ ተገቢ ስላልሆነ ፍ/ቤቱ የተጠሪ ጥያቄ ውድቅ ማድረጉን በመግልጽ አመልካች በነጻ ይሰናበቱ በማለት ፍርድ ሰጥቷል፡፡ የአሁን አመልካች በዚህ  ውሳኔ  ቅር በመሰኘት ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቤቱታውን ያቀረበ ሲሆን ፍ/ቤቱም ግራ ቀኙ በማከራከር በሰጠው ውሳኔ ተጠሪ በቃል ክርክር የድኤንኤ ምርመራ እንዲደረግለት ጠይቋል፡፡ የስር ፍርድ ቤት ምርመራውን ለማዘዝ የልጅ አባት ነው የሚያሰብል ግምት መያዝ አለበት በማለት መደምደሙ ከሰ/መ/ቁ.63195 አኳያ ተገቢነት የለውም፡፡ የአሁን ተጠሪ በስር ፍ/ቤት በማስረጃነት


    የጠቀሰውን የዲ.ኤን.ኤ ምርምራ ጥያቄ ሳይቀበለው አልፎ የሰጠው ውሳኔ  የህግ አግባብ ባለመሆኑ ምርመራ ተደርጎ በምርምራው ውጤት የመስለውን እንዲወሰን ውሳኔውን በማሻር በነጥብ መልሶታል፡፡

     

    የከፍተኛውን ፍ/ቤት ውሳኔ በመቃወም አመልካች ለፌዴራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ያቀረቡትን ይግባኝ በፍ/ብ/ስ/ስ/ህ/ቁ.337 መሰረት ተሰርዟል፡፡ አመልካች በስር ፍርድ ቤቶች ተፈጽሟል ያሉትን የህግ ስህተት እንዲታረም ግንቦት 13 ቀን 2005 ዓ/ም የተጻፈ አቤቱታ አቅርበዋል፡፡ የአመልካች አቤቱታ ዋና ፍሬ ነገሩ፡- የሰበር ውሳኔው ለዚህ ጉዳይ አግባብነት የለውም ፤ የስር ፍርድ ቤት የዲ.ኤን.ኤ ምርመራ ጥያቄ የተቀበለው ስርዓቱን ጠብቆ አይደለም ፤ ከአመልካች ስለመወለዱ አልተረጋገጠም በማለት ስር ፍ/ቤት ውሳኔ እንዲሻር አመልክቷል፡፡ ተጠሪ በበኩላቸው በስጡት መልስ በአመልካች እና የተጠሪ እናት ግንኙነት መኖሩ ተረጋግጧል፡፡ የዲኤንኤ ምርመራ በመጀመሪያ ቀጠሮ መጠየቃቸው፤ ምርመራውም ጉዳዩን ግልጽ የሚያደረግ መሆኑ በመጥቀስ የስር ፍ/ቤት ውሳኔ እንዲጸና ጠይቋል፡፡ አመልካች የመልስ መልስ ያቀረቡ ሲሆን አቤቱታቸውን የሚያጠናክር ክርክር አቅርበዋል፡፡ ሰበር ሰሚ ችሎቱ ህዳር 05 ቀን 2006 ዓ/ም ግራ ቀኙ በችሎት በቃል አከራክሮ ውጤቱን መዝግበዋል፡፡

     

    የክርክሩ አጭር ይዘትና አመጣጥ ከላይ የተመለከተው ነው፡፡ እኛም መዝገቡን በአጣሪ ችሎቱ ያስቀርባል ከተባለው ጭብጥ እና አግባብነት ካላቸው ድንጋጌዎች አኳያ ጉዳዩን መርምረናል፡፡ እንደመረመርነውም የአሁን ተጠሪ በአመልካች እና እናቱ መካከል የነበረው ግንኙነት ለማስረዳት ምስክሮች በማቅረብ ያስማ መሆኑ ከመዝገቡ መገንዘብ ተችሏል፡፡ የስር ፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የዲኤንኤ ምርምራ ጥያቄ ውድቅ ያደረገው በአመልካች እና የተጠሪ እናት ነበረ የተባለው ግንኙነት በተሻሻለው የቤተሰብ ህግ አንቀጽ 143 መሰረት ከተመለከቱት ግምት የሚያሰጡ ምልክት ሰጪ ነገሮች በአንዴ አልተረጋገጠም የሚል ነው፡፡ የስር ከፍተኛ ፍርድ ቤት የዲኤንኤ ምርምራ በተጠሪ በቃል ክርክር ወቅት የተጠየቀ በመሆኑ በፍ/ብ/ስ/ስ/ህ/ቁ.259(1) መሰረት እንዲሁም ሰበር ሰሚ ችሎት በሰ.መ.ቁ. 63195 ከሰጠው አስገዳጅ ውሳኔ አኳያ ዲኤንኤ ምርመራ ይደረግ ጥያቄ ተቀብሎታል፡፡ የአባትነት ይረጋገጥልኝ ጥያቄ በአንዱ በኩል አባት የማግኘት መብት ሲያረጋግጥ በሌላ በኩል ደግሞ አባት ያልሆኑ ግለሰቦች አባት ነህ ተብሎ እንዳይወሰን ለመከላከል የተበጀ ህጋዊ ስርዓት ነው፡፡ የአሁኑ ተጠሪ የዲኤንኤ ምርመራ ይደረግልኝ ጥያቄ በስር ፍርድ ቤት ማቅረቡ አልተካደም፡፡ የዲኤንኤ ምርመራ እንደ አንድ የማስረጃ ይዘት እንዲታይለት መጠየቁ እና ይህንን ጥያቄም ስርዓቱን ጠብቆ ማቅረቡ በስር መጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤትም የተካደ ጉዳይ አይደለም፡፡ የስር ፍርድ ቤት ጥያቄውን ውድቅ ለማድረግ መነሻ ያደረገው የደም ምርመራ ለማድረግ አመልካች የዲኤንኤ ምርምራ እንዲያደርጉ ለማስገደድ ተጠሪ እናትና አመልካች በተሻሻለው የቤተሰብ ህግ አንቀጽ 143 መሰረት ግንኙነት የነበራቸው መሆኑ እና ተጠሪም በዚህ ግንኙነት የተወለደ መሆኑ በቅድሚያ መረጋገጥ አለበት በሚል ምክንያት ነው፡፡ ይሁንና ይህ የስር ፍርድ ቤት ድምዳሜ በይግባኝ ሰሚ ፍ/ቤት ተቀባይነት አላገኘም፡፡ የስር መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የፍሬ ነገር ማጣራትና ማስረጃ ምዘና ስርዓት ተገቢ አይደለም ተብሎ በይግባኝ ሰሚ ፍ/ቤቱ ከተሻረ በሰበር ችሎቱ የማስረጃ ምዘና ሂደቱ የሚታይበት ስርዓት አይኖርም፡፡

     

    በአመልካች እና ተጠሪ እናት መካከል ግንኙነት ነበረ ወይስ አልነበረም የሚለው የፍሬ ነገር ክርክር የስር ፍርድ ቤቶች የየራሳቸው አቋም የወሰዱበት መሆኑ ከስር ፍርድ ቤት ውሳኔ መገንዝብ ይቻላል፡፡ ይህ ሰበር ሰሚ ችሎት መሰረታዊ የህግ ስህተት መኖር አለመኖሩን መርምሮ


    ውሳኔ ከመስጠት ውጪ ፍሬ ነገርን በማጣራትና ማስረጃ ምዘና ረገድ የስር ፍርድ ቤቶች የደረሱበት ድምዳሜ ተገቢ መሆን አለመሆኑን ለመመርመር የሚያስችል ስልጣን የሌለው ስለመሆኑ ከኢፌዴሪ ህገ መንግስት አንቀጽ 80(3)(ሀ) እና አዋጅ ቁጥር 25/1988 አንቀጽ 10 መሰረታዊ ይዘትና መንፈስ የምንገነዘበው ነው፡፡ የቤተሰብ ህጉ የአባትነት ይረጋገጥልኝ ጥያቄ የሚቀርብበት የጊዜ ገደብ በግልጽ አልተገደበም፡፡ ይህ ከሆነ ደግሞ አመልካች ከ30 ዓመት በኃላ የአባትነት ይረጋገጥልኝ ጥያቄ ማቅረቡ የጥያቄውን ህጋዊነት ከወዲሁ ውድቅ ለማድረግ የሚያስችል ምክንያት ሆኖ አልተገኘም፡፡ የሰበር ችሎቱ በመ/ቁ. 63195 የዲኤንኤ ምርመራ ወጪ ከመሸፈን ጋር በተያያዘ የሰጠው ትርጉም በስር ከፍተኛ ፍርድ ቤት እንደ አስገዳጅ ውሳኔ መጠቀሱ የክርክር ምክንያት ቢሆኑም በዚህ ጉዳይ በዋናነት መታየት ያለበት ይህ ሰበር ችሎት በተመሳሳይ ጉዳይ ላይ የዲኤንኤ ምርመራ እንዳይደረግ የክልከላ ውጤት ያለው ውሳኔ ከመስጠቱ አንፃር ብቻ ነው፡፡ በዚህ ረገድ የሰበር ችሎቱ ከኤክሰፐርት ምርመራ ውጤትና የማሳረዳት ብቃቱ በተያያዘ የተሰጠ ትርጉም መኖሩ ግልጽ ቢሆንም በእጃችን ከተያዘው ጉዳይ ጋር በፍሬ ነገርና በጭብጥ ረገድ አንድና ተመሳሳይ የሆነ ምርምራ የሚከለክል ውሳኔ ያልተሰጠ ከመሆኑ አንፃር የስር ፍርድ ቤት ከላይ የተጠቀሰው መዝገብ በአስገዳጅ ውሳኔ መመዝቡ የውሳኔውን ህጋዊነት ጥያቄ ውስጥ የሚከተው ሆኖ አልተገኘም፡፡

     

    የተሻሻለው የቤተሰብ ህግ አዋጅ ቁጥር 213/1992 አባትነት የሚረጋገጥባቸውን መንገዶች አስቀምጧል፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ የሚጠቀሱት አባትነት በህግ ግምት የሚወሰድባቸው ሲሆኑ በጋብቻ ውስጥ የተወለዱ ልጆች እንዲሁም እንደባልና ሚስት ሆነው ከኖሩ ግለሰቦች የተወለደው ህፃን የሚመለከት መሆኑ ከቤተሰብ ህግ አንቀጽ 126 እና 130 ድንጋጌዎች መሰረታዊ ይዘትና መንፈስ መገንዘብ ይቻላል፡፡ ከዚህ ወጪ አባትነት እውቅና በመስጠት ሊረጋገጥ ይችላል፡፡ የአባትነት ይረጋገጥልኝ ጥያቄ ከላይ በተጠቀሱ ምክንያቶች ማረጋገጥ በማይቻልበት ሁኔታ በፍርድ ቤት ክስ በማቅረብ እንደሚታይ ነው፡፡ በፍርድ ቤት አባትነት ለማረጋገጥ መነሻ ነጥቦች በተሻሻለው የቤተሰብ ህግ አንቀጽ 143 የተዘረዘሩት ሲሆኑ በዚህ ረገድ የሚነሳው ክርክር ወይም ግምትና ምልክት ሰጪ ግምቶች ለማስተባበል የሚያስችሉ ምክንያቶች በዚህ ህግ አንቀጽ 144 በዝርዝር ተመልክቷል፡፡ በስር ፍርድ ቤት በተጠሪ የቀረበው የአባትነት ይረጋገጥልኝ ጥያቄ በአመልካች ተክዷል፡፡ ተጠሪ በስር ፍርድ ቤት የዲኤንኤ ምርመራ እንዲታዘዝለት ጠይቋል፡፡ የስር የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ጥያቄውን ውድቅ ቢያደረገውም ይግባኝ ሰሚ ፍ/ቤት የጥያቄው ተገቢነት በመቀበል ምርመራው እንዲደረግ አዟል፡፡ የስር ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤት የተጠሪ የዲኤንኤ ምርመራ ይታዘዝልኝ ጥያቄ በወቅቱ የቀረበ መሆኑ በማረጋገጥ የስር ፍርድ ቤት ጉዳዩን እንዲመለከተው መልሶ መላኩ በህግ አተረጓጎም ረገድ የፈጸመው ስህተት አለ ማለት አልተቻለም፡፡ የዲኤንኤ ምርመራ ውጤት በማንኛውም ሁኔታ እንዲደረግ የሚጠይቅ አለመሆኑ ችሎቱ የሚገነዘብ ቢሆንም የስር ከፍተኛ ፍርድ ቤት የስር የመጀመሪያ ደረጃ የፍሬ ነገር ድምዳሜና የማስረጃ ምዘና ባለመቀበል ምርምራ እንዲደረግ ማዘዙ በፍ/ብ/ስ/ስ/ህግ የተደነገጉት የክርክር አመራር መሰረታዊ የስነ ስርዓት ድንጋጌዎች በአግባቡ አልተተረጎሙም ለማለት የሚያስችል ነገር አልቀረበም፡፡ በአመልካች እና ተጠሪ መካከል ያለው የአባትነት ይረጋገጥልኝ ጥያቄ የዲኤንኤ ምርመራ ተደረጎ የስር ፍርድ ቤት የመሰለውን  እንዲወሰን መታዘዙ ፤ የምርመራ ወጤት ምን ሊሆን እንደሚችል ከወዲሁ መተንበይ በማይቻልበት ሁኔታ አመልካች ለመጉዳት ታስቦ የተደረገ ነው የሚያስብል የህግ ምክንያት የለውም፡፡ በመሆኑም የስር ከፍተኛ ፍርድ ቤት በአመልካች እና ተጠሪ መካከል ያለው አባትነት ይረጋገጥልኝ ጥያቄ ለመወሰን የዲኤንኤ ምርምራ አስፈላጊ መሆኑ በስር ፍርድ ቤት ከታመነበት የፍ/ቤቱ    ትእዛዝ


    ተፈጻሚ መሆን አለበት፡፡ ከዚህ አንጻር የስር ከፍተኛ እና ጠቅላይ ፍርድ ቤቶች የዲኤንኤ ምርመራ እንዲደረግ ማዘዛቸው በአግባቡ ነው፡፡ በሌላ በኩል አመልካች በስር ፍርድ የመከላከያ ማስረጃ ማቅረብ እንደሚችሉ ግልጸዋል፡፡ የስር ፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ክሱን ውድቅ በማድረግ የመከላከያ ማስረጃ አለማዳመጡን ከስር ፍርድ ቤት ውሳኔ ተገንዝበናል፡፡ በመሆኑም አመልካች የዲኤንኤ /DNA/ ምርምራ ቢደረግም አለኝ የሚሉትን የመከላከያ ማስረጃ የማስማት መብታቸው የሚከለክል አይሆንም፡፡

     

    በማጠቃለል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤትን ውሳኔ በመሻር የዲኤንኤ ምርመራ እንዲደረግ ማዘዙ እና ውሳኔው በፌዴራል ጠቅላይ ፍ/ቤት መጽናቱ መሰረታዊ የህግ ስህተት የተፈጸመበት ሆኖ አላገኘነውም፡፡ በዚህ መሰረትም ተከታዩን ወስነናል፡፡

     

     ው ሳኔ

     

    1. የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት በኮ/መ/ቁ. 57163 በ1/09/2004  ዓ/ም የሰጠውን ውሳኔ በመሻር የፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት በኮ/መ/ቁ. 126002 ጥር 30 ቀን 2005 ዓ/ም የሰጠው ውሳኔና ፤ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በኮ/መ/ቁ.87769 የሰጠው ውሳኔ ጸንቷል፡፡

    2. የስር ፌዴራል ከፍተኛ ፍ/ቤት የዲኤንኤ ምርመራ እንዲደረግ ማዘዙ በአግባብ ነው ብለናል፡፡

    3. የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤትም በትእዛዙ መሰረት ይፈጸም ብለናል፡፡ አመልካችም አለኝ የሚሉትን መከለከያ ማስረጃ የማሰማት መብታቸው የተጠበቀ ነው፡፡

    4. በዚህ ጉዳይ ክርክሩ ለጊዜው እንዲቆም ግንቦት 28 ቀን 2006 ዓ/ም የተሰጠው ትእዛዝ ተነስቷል፡፡

    5. በዚህ የሰበር ጉዳይ ክርክር የተነሳ የግራ ቀኙ ላወጡት ወጪና ኪሳራ የየራሳቸው ይቻሉ ብለናል፡፡

    መዝገቡ ተዘግቷል፡፡ ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ፡፡

     

     


     

     

    ሃ/ወ


     

     

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት::

  • የወንጀል ህጉ አንቀጽ 420 ድንጋጌ ተፈፃሚነት የሚኖረው የመወሰን ስልጣን በሌላቸው እና የሙያ አገልግሎት የመስጠት ኃላፊነት ያለባቸው በመንግስት ስራ ተመድበው ባሉበት ሁኔታ በመንግስት ንብረት ላይ የሥራ ኃላፊነት ወይም ግዴታቸውን ባልተወጡት ላይ ስለመሆኑ፣

     

    የወ/ህ/አንቀጽ 420/1/

    የሰ//.92826 ጥር 05 ቀን 2007 ዓ/ም

    ዳኞች፡-አልማው ወሌ

     

    ዓሊ መሐመድ ሡልጣን አባተማም ሙስጠፋ አህመድ ተኽሊት ይመሰል

    አመልካች፡- የደ/ብ/ብ/ሕ/ብ/ክልላዊ መንግስት ዐቃቤ ሕግ - የቀረበ የለም ተጠሪ፡-  ወ/ሮ ፀሐይ መጫሎ - ቀረቡ

    መዝገቡ ተመርምሮ ተከታዩ ፍርድ ተሰጥቷል፡፡

     

     ፍ ርድ

     

    ጉዳዩ የወንጀል ጉዳይ ሲሆን ክርክሩ የተጀመረው የአሁኑ አመልካች የክልሉን የሥነ ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽንን በመወከል በአሁኗ ተጠሪና በሌሎች ሁለት ሰዎች ላይ በካፋ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመሰረተው ክስ መነሻ ነው፡፡የአመልካች ክስ ይዘትም፡- ተጠሪና በስር ፍርድ ቤት 1ኛ ተከሳሽ የነበሩት አቶ ኢምቶ ወ/ማሪያም አቶ ዳዊት ደስታ የተባሉት ግለሰቦች ተገቢ ያልሆነ ብልጽግና ለራሳቸው ለማግኘት በማሰብ በዬቻ ወረዳ ፋይናንስና ኢኮኖሚ ልማት ፅ/ቤት ውስጥ የስር 1ኛ ተከሳሸ የነበሩት አቶ ኢምቶ ወ/ማሪያም ዋና ገንዘብ ያዥ፣የአሁኗ ተጠሪ ደግሞ የክፍያ ኦፊሰር፣ቼክ አዘጋጅና ፈራሚ፣የስር ሶስተኛ ተከሳሽ የነበሩትና በብይን በነፃ የተሰናበቱት አቶ ዳዊት ደስታ ደግሞ የክፍያ ሰራተኛ እና ቼክ ፈራሚ በመሆን እየሰሩ የአሁኗ ተጠሪ ከኢትዩጵያ ንግድ ባንክ ቦንጋ ቅርንጫፍ ከሂሳብ ቁጥር GOV 787 ብር 100,000.00(አንድ መቶ ሺህ) ብር ወጪ ተደርጎ ለስር አንደኛ ተከሳሽ እንዲከፈል ቁጥሩ 0741998 የሆነውን ቼክ ሰኔ 30 ቀን 2004 ዓ.ም አዘጋጅተው ከስር ሶስተኛ ተከሳሽ ጋር ፈርማ በኃላፊ ሳይታዘዙ በመስጠታቸውና የስር 1ኛ ተከሳሽም ብር 100,000.00(አንድ መቶ ሺህ) ከተጠቃሹ ባንክ አውጥቶ ለግል ጥቅማቸው በማዋላቸው በኢ.ፌ.ዲ.ሪፐብሊክ የወንጀል ሕግ አንቀጽ 32(1(ሀ)) እና 676(1) ስር የተመለከተውን በመተላለፍ በግብረአበርነት ከባድ የእምነት ማጉደል ወንጀል ፈፅመዋል የሚል ነው፡፡ ተጠሪ ክሱን ክደው የተከራከሩ ሲሆን አቃቤ ሕግ በበኩሉ አሉኝ ያላቸውን ማስረጃዎቸን አቅርቦ ካሰማ በሁዋላ የተጠሪ የመከላከል መብታቸው ተጠብቆላቸው የመከላከያ ምስክሮችን አሰምተዋል፡፡የሥር ፍርድ ቤትም ጉዳዩን መርምሮ ተጠሪ በመከላከያ ምስክሮች የአቃቤ ሕግ ማስረጃዎችን ሊያስተባብሉ አልቻሉም በሚል ምክንያት ክስ በቀረበባቸው ድንጋጌ ስር ጥፋተኛ አድርጓል፡፡ቅጣቱን በተመለከተም የግራ ቀኙን የቅጣት አስተያየት በመቀበልና በፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በወጣው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ ቁጥር 1/2002 መሰረት አስልቶ በአስራ  አራት


    አመት ፅኑ እስራት እና በብር 7000.00(ሰባት ሺህ) እንዲቀጡ ሲል ወስኗል፡፡በዚህ ውሳኔ የአሁኗ ተጠሪ ቅር በመሰኘት ይግባኛቸውን ለክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ይግባኛቸውን ቢያቀርቡም ተቀባይነት አላገኙም፡፡ተጠሪ የሰበር አቤቱታቸውን ለክልል ሰበር ሰሚ ችሎት አቅርበው ግን ግራ ቀኙ እንዲከራከሩ ተደርጎ ችሎቱ ጉዳዩን መርምሮ ተጠሪ የወንጀል ድርጊት መፈፀማቸው መረጋገጡን ተቀብሎ አድራጎቱ የሚሸፈንበትን ድንጋጌ በተመለከተ አመልካች ተጠሪ ገንዘቡን ለግል ጥቅማቸው ስለማዋላቸው ወይም ለሌላ ሰው ያልተገባ ጥቅም ስለማዋላቸው በማስረጃ አልተረጋገጠም በሚል ምክንያት በዓቃቤ ሕግ የክስ ማመልከቻ የተጠቀሰውን በወ/መ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 113 (2) መሰረት ወደ የወንጀል ሕጉ አንቀጽ 420(1) ለውጦ በዚሁ ድንጋጌ ስር የሙያ ግዴታ የመጣስ አድራጎት ፈጽመዋል በማለት ወስኗል፡፡ቅጣቱንም በተመለከተም በዚሁ በተለወጠው ድንጋጌ ስር በፌዴራሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የቅጣት አወሳሰን መመሪያ መሰረት ደረጃ ላልወጣላቸው የወንጀል ድንጋጌዎች ደረጃ የሚወጣበትን አግባብ ዘርዝሮና ከግራ ቀኙ የቅጣት አስተያየት ጋር በማገናዘብ  መመርመሩን ገልፆ ተጠሪ በአንድ አመት ቀላል እስራት እና በብር 5000.00 (አምስት ሺህ) ብር እንዲቀጡ ወስኗል፡፡የሰበር አቤቱታ የቀረበውም ይህንኑ ውሳኔ በመቃወም ለማስለወጥ ነው፡፡የአመልካች የሰበር አቤቱታ መሰረታዊ ይዘትም፡-የተጠሪ አድራጎት ከባድ የእምነት ማጉደል ወንጀል ሁኖ እያለ የስራ ኃላፊነትን ባለመወጣት የተፈፀመ ነው ተብሎ መወሰኑ ያላግባብ ነው የሚል ሲሆን አቤቱታው ተመርምሮም የተጠሪ አድራጎት የሚሸፈነው በወንጀል ሕጉ አንቀጽ 676(1) ሳይሆን በአንቀጽ 420(1) ስር ነው ተብሎ የመወሰኑን አግባብነት ለመመርመር ሲባል ጉዳዩ ለሰበር ችሎት እንዲቀርብ ተደርጓል፡፡ለተጠሪ ጥሪ ተደርጎላቸውም ቀርበውም በፅሑፍ በሰጡት መልስ የክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት የሰጠው ሕጋዊ ነው የሚሉባቸውን ምክንያቶችን ዘርዝረው ውሳኔው ሊፀና ይገባል በማለት ተከራክረዋል፡፡

     

    የጉዳዩ አመጣጥ አጠር አጠር ባለመልኩ ከላይ የተገለፀው ሲሆን ይህ  ችሎትም ለሰበር አቤቱታው መነሻ የሆነውን ውሳኔ አግባብነት ካላቸው ድንጋጌዎች ጋር በማገናዘብ ጉዳዩ ለሰበር ችሎት ከተያዘው ጭብጥ አንፃር በሚከተለው መልኩ መርምሮታል፡፡

     

    በመሠረቱ አንድ ወንጀል ተደረገ የሚባለው ወንጀሉን የሚያቋቋሙት  ሕጋዊ፣ግዙፋዊ እና ሞራላዊ ፍሬ ነገሮች በአንድነት ተሟልተው ሲገኙ ብቻ መሆኑን በአዋጅ ቁጥር 414/1996 የወንጀል ሕጉ አንቀጽ 23 (2) በግልፅ ደንግጓል፡፡እንግዲህ አንድን ድርጊት ወንጀል ነው ብሎ ለመወሰን ሕጋዊ፣ግዙፋዊ እና ሞራላዊ ፍሬ ነገሮች ተጣምረው መገኘት የግድ ይላል፡፡ሕጋዊ ፍሬ ነገሮች የሚባሉት ደግሞ ለጉዳዩ አግባብነት አለው ተብሎ የተጠቀሰውን ድንጋጌ ለማቋቋም ሙሉ በሙሉ መሟላት ያለባቸውን ነጥቦች የሚመለከት ሲሆን ግዙፋዊና ሞራላዊ ፍሬ ነገሮች የሚባሉት ደግሞ እንደየቅደምተከተላቸው ከድርጊት ማድረግ ወይም አለማድረግና ከሐሳብ ክፍል ጋር በሕጉ አንቀፅ 24፣57 እና 58 ድንጋጌዎች ስር የተመለከቱትን ሁኔታዎችን የሚመለከቱ መሆኑ ይታመናል፡፡

     

    ወደ ተያዘው ጉዳይ ስንመጣ ተጠሪ ጥፋተኛ የተባሉት በመንግስት መስሪያ ቤት በክፍያ ኦፊሰርነት፣ቼክ አዘጋጅነትና ፈራሚነት የስራ መደብ ላይ ተመድበው ሲሰሩ በቀን 30/10/2002 ዓ/ም ቁጥሩ 0741998 በሆነ ቼክ ብር 100,000.00(አንድ መቶ ሺህ) ለስር አንደኛ ተከሳሽ እንዲከፈል አዘጋጅተው በቼኩ ጉማጅና በባንክ ክፍያ ደረሰኝ ላይ ሳያስፈርሙ ሰጥተው የስር አንደኛ ተከሳሽ ከኢትዩጵያ ንግድ ባንክ ቦንጋ ቅርንጫፍ ከሂሳብ ቁጥር GOV 787 ብር 100,000.00(አንድ መቶ ሺህ) ብር ወጪ አድርጎ ለግል ጥቅሙ እንዲያውል  አድርገዋል፣ተጠሪ


    ይህንኑ ያደርጉትም ያዘዛቸው ኃላፊ ሳይኖር መሆኑ በፍሬ ነገር ደረጃ ተጋግጧል በሚሉ ምክንያቶች መሆኑን ከስር ፍርድ ቤት የውሳኔ ግልባጭ ተገንዝበናል፡፡ከክርክሩ አመጣጥና ከስር ፍርድ ቤቶች የውሳኔ ይዘት አንጻር በዚህ ችሎት ምላሽ የሚያስፈልገው አቢይ ነጥብ የተጠሪ አድራጎት የሚሸፈነው በየትኛው ድንጋጌ ስር ነው? የሚለው ነው፡፡

     

    ተጠሪ በአመልካች የተከሰሱትና በስር ፍርድ ቤት ጥፋተኛ የተባሉት የወንጀል ሕጉን አንቀጽ 676/1/ የተመለከተውን በመተላለፍ ከመንግስት የሂሳብ ቁጥር ብር 100,000.00 ለሌላ ሰው ጥቅም እንዲውል በማድረጋቸው ከባድ የእምነት ማጉደልና የሙስና ወንጀል ፈፅመዋል ተብሎ ነው፡፡የወንጀል ሕጉ 676 በወንጀል ሕግ 675 የሚፈፀመውን የእምነት ማጉደል ወንጀል የሚከብ ድበትን ሁኔታ የሚዘረዝር ነው፡፡የድንጋጌው መሰረታዊ ማቋቋሚያ ነጥቦች በወንጀል ሕጉ አንቀጽ 675 ስር የተመለከቱት የእምነት ማጉደል ወንጀል ማቋቋሚያ ሁኔታዎች ስለመሆናቸው የሁለቱ ድንጋጌዎች ይዘት ያስገነዝባል፡፡ከባድ የእምነት ማጉደል የሙስና ወንጀል የሚሆነው ደግሞ የመንግስት ሰራተኛ ወይም የመንግስት ሰራተኛ ያልሆኑት ሰዎች በመንግስት ንብረት ላይ የእምነት ማጉደል ተግባሩን መፈፀማቸው ሲረጋገጥ ነው፡፡በወንጀል ሕጉ 675 ንዑስ አንቀጽ 3 ተከሣሹ ሲጠየቅ በእምነት ወይም ባደራ የተሰጠውን ዕቃ ወይም ጥሬ ገንዘብ ለመመለስ ወይም ለመክፈል ወይም ዕቃው ያለበትን ሁኔታ ለማሳየት ወይም ለተገቢው አገልግሎት ያዋለው መሆኑን ለማስረዳት ካልቻለ ንብረቱን ለራሱ ወይም ለሌላ ሰው ያልተገባ ጥቅም የማዋል ሀሳብ እንዳለው የሚቆጠር መሆኑን በግልፅ ደንግጓል፡፡ይህ የህግ ግምት የሚስተባበለው ደግሞ በተከሳሹ ነው፡፡የክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት ተጠሪን ተጠያቂ ያደረጋቸው በወንጀል ሕግ አንቀጽ 420(1) ስር ነው፡፡በዚህ ድንጋጌ የወንጀል ተጠያቂነት የሚመጣው ማንኛውም የመንግስት ሰራተኛ የሥራ ግዴታ ተግባሩን በአግባቡ ሳይፈጽም በመቅረቱ በመንግስት፣በህብረተሰብ ወይም በግለሰብ ጥቅም ላይ ጉዳት አድርሶ የተገኘ እንደሆነ ነው፡፡የወንጀል ሕጉ አንቀፅ 420 ድንጋጌ ተፈጻሚነት የሚኖረው የመወሰን ሥልጣን የሌላቸውና የሙያ ግልጋሎት የመስጠት ኃላፊነት ባለባቸው ሰዎች ነው፡፡ስለሆነም በአንቀጽ 420 ድንጋጌ ይዘትና መንፈስ መሰረት አንድን ሰው ተጠያቂ ለማድረግ የሙያ ተግባሩንና ሥራው በአግባቡና በጥንቃቄ ባለመፈፀሙ ምክንያት  በመንግስት ላይ ጉዳት መደረሱ ሊረጋገጥ ይገባል፡፡

    ወደተያዘው ጉደይ ስንመለስ የክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት የተጠሪ አድራጎት በወንጀል ሕጉ አንቀጽ 420(1) ስር የሚሸፈን ነው ወደሚለው ድምዳሜ የደረሰው ተጠሪ አድራጎቱን የፈፀሙት ተገቢ ያልሆነ ብልጽግና ለማግኘት ወይም ለሌላ ሰው ለማስገኘት በማሰብ ለግል ጥቅሙ ወይም ለሌላ ሰው ያልተገባ ጥቅም ለማዋል በማሰብ መሆኑን በማስረጃ አልተረጋገጠም በሚል አቢይ ምክንያት ነው፡፡በእርግጥ ተጠሪ የተከሰሱት በከባድ የእምነት ማጉደል ወንጀል መሆኑ ሲታይ የወንጀል ሕግ አንቀጽ 676(1) የወንጀል ሕጉ አንቀጽ 675 መሰረታዊ የወንጀል ማቋቋሚያ የያዘ በመሆኑ በወንጀል ሕጉ አንቀጽ 675(3) በተመለከተው የሕግ ግምት መሰረት ተከሣሹ ሲጠየቅ በእምነት ወይም ባደራ የተሰጠውን ዕቃ ወይም ጥሬ ገንዘብ ለመመለስ ወይም ለመክፈል ወይም ዕቃው ያለበትን ሁኔታ ለማሳየት ወይም ለተገቢው አገልግሎት ያዋለው መሆኑን ለማስረዳት ካልቻለ ንብረቱን ለራሱ ወይም ለሌላ ሰው ያልተገባ ጥቅም የማዋል ሀሳብ እንዳለው የሚቆጠር መሆኑን መረዳት ይቻላል፡፡ በተያዘው ጉዳይ ግን ተጠሪ የክፍያ ኦፊሰር፣ቼክ አዘጋጅና ፈራሚ መሆናቸው እንጂ በመሰረታዊ የስራ ሂደት መሰረት በጉርዱ ላይ ለመመዝገብ የስራ ሂደቱን አስተባባሪ ትዕዛዝ መጠበቅ የግድ የሚላቸው መሆኑን የክርክሩ ሂደት ማስገንዘቡ ሲታይ ተጠሪ ብቻቸውን የመወሰን ሥልጣን የሌላቸውና የሙያ ግልጋሎት የመስጠት ኃላፊነት ብቻ የነበራቸው ናቸው  ለማለት  የሚያስችል  ሁኖ  አግኝተናል፡፡በስራ  መደባቸው ተጠሪ  ብቻቸውን የመወሰን


    ስልጣን ሳይኖራቸው ባልተገባ መንገድ ቼኩን አዘጋጅተውና ፈርመው ለስር  1ኛ ተከሳሽ በመስጠት ከመንግስት የባንክ ሂሳብ ውስጥ ብር 100,000.00 ወጪ ሁኖ ለስር 1ኛ ተከሳሽ የግል ጥቅም እንዲውል ማድረጋቸው በመንግስት ሰራ ተመድበው በመስራት ላይ ባሉበት ሁኔታ በመንግስት ንብረት ላይ የስራ ኃላፊነት ወይም ግዴታቸውን ያለመወጣታቸውን የሚያሳይ ሁኖ አግኝተናል፡፡ በመሆኑም የክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት የወንጀል ሕጉ አንቀጽ 420(1) የተፈፃሚነት አድማሱን ከተጠሪ የስራ ኃላፊነት ዝርዝር ይዘት እና በወቅቱ  ከነባራቸው  ተሳትፎ ጋር በማዛመድ የተጠሪ አድራጎት የሥራ ኃላፊነትን ባለመወጣት የሚፈፀም ወንጀል ነው በማለት የሰጠው ውሳኔ መሰረታዊ የሆነ የሕግ ስህተት ያለበት ሁኖ ስላላገኘን ተከታዩን ወስነናል፡፡

     ው ሣኔ

     

    1. በደ/ብ/ብ/ሕ/ብ/ክ/መንግስት ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት በመ/ቁጥር  00723 ሐምሌ 02 ቀን 2005 ዓ/ም የተሰጠው የጥፋተኝነትና የቅጣት ውሳኔ በወ/መ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 195(2)(ለ-2)) መሰረት ጸንቷል፡፡

    2.  የተጠሪ አድራጎት የሚሸፈነው በወንጀል ሕግ አንቀጽ 420(1) ስር ነው መባሉ  በአግባቡ ነው ብለናል፡፡

    መዝገቡ ተዘግቷል፤ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ፡፡

     


     

    መ/ተ


    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡

  • በወንጀል ክስ ክርክር የክስ ይሻሻል ጥያቄ ቀርቦ ጥያቄው ውድቅ ከተደረገ ጥያቄው ውድቅ የተደረገበት ትእዛዝ በድጋሚ ለክርክር ሊቀርብ የሚችልበት ዕድል የሌለ በመሆኑና ትእዛዙ የመጨረሻ እንጂ ጊዜያዊ አገልግሎት እንዳለው ተቆጥሮ በስረ ነገሩ ከሚሰጠው ፍርድ ጋር ተጠቃሎ ይግባኝ የሚባልበት ነው ሊባል የሚችል ስላለመሆኑና በተሠጠው ትእዛዝ ላይ በስረ ነገሩ ከሚሰጠው ፍርድ በፊት ይግባኝ ሊቀርብበት የሚችል ስለመሆኑ፡-

     

    የወ/መ/ሥ/ሥ/ህ/ቁ. 118፣184፣

    የሰ/መ/ቁ. 93234

    መስከረም 27 ቀን 2007 ዓ.ም.

     

    ዳኞች፡- አልማው ወሌ

     

    ሡልጣን አባተማም መኰንን ገ/ሕይወት ሙስጠፋ አህመድ ተፈሪ ገብሩ

    አመልካች፡- የትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የስነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ዐቃቤ ሕግ - የቀረበ የለም፡፡

     

    ተጠሪ፡- አቶ ኃይለኪሮስ ወልደብርሃን ካሕሳይ - የቀረበ የለም፡፡ መዝገቡ ተመርምሮ የሚከተለው ፍርድ ተሰጥቷል፡፡

     ፍ ር ድ

     

    በዚህ መዝገብ አመልካች አቤቱታ ያቀረበው በትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት በማዕከላዊ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት በአሁኑ ተጠሪ ላይ አቅርቧቸው በነበሩት ሁለት የሙስና ወንጀል ክሶች ጉዳዩ የከሳሽን ምስክሮች ለመስማት በተቀጠረበት ዕለት ምስክሮቹ እንዲሰሙ ከመደረጉ በፊት ተከሳሹ ከተከሰሱባቸው ሁለት የሙስና ወንጀሎች መካከል በሁለተኛው ክስ የተመለከተውን ወንጀል ያደረጉት ከሌላ ሰው ጋር በመተባበር ስለመሆኑ በሂደት የተደረሰበት መሆኑን ገልጾ የወንጀሉ ተካፋይ ነው የተባለውን ሌላኛውን ግለሰብ በክሱ በማካተት ክሱን አሻሽሎ ለማቅረብ እንዲፈቀድለት ያቀረበውን ጥያቄ የዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት በአብላጫ ድምጽ ውድቅ በማድረግ የሰጠው ብይን እና በብይኑ ቅር በመሰኘት አመልካች ያቀረበውን ቅሬታ የክልሉ የበላይ ፍርድ ቤቶች ባለመቀበል የሰጡት ውሳኔ መሰረታዊ የሕግ ስህተት የተፈጸመበት በመሆኑ ሊታረም ይገባል በማለት ነው፡፡

     

    የዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የክስ ማሻሻል ጥያቄውን በአብላጫ ድምጽ ሳይቀበል የቀረው በወንጀለኛ መቅጫ ሕግ ስነ ስርዓት ቁጥር 118 እና 119 ድንጋጌዎች መሰረት ክስ እንዲሻሻል ሊደረግ የሚችለው ክሱ ተከሳሹን የሚያሳስት ወይም ትክክለኛ ፍርድ ለመስጠት የሚያስቸግር በሆነ ጊዜ መሆኑን እና ተጨማሪ ተከሳሽን በክሱ የማካተት ጉዳይ ለክስ ማሻሻል ጥያቄ በምክንያትነት መቅረቡ ሕጋዊ መሰረት የሌለው መሆኑን በመግለጽ ሲሆን አነስተኛው ድምጽ በበኩሉ ክስ እንዲሻሻል የሚደረገው ተከሳሹን የሚያሳስት ወይም ትክክለኛ ፍርድ ለመስጠት የሚያስቸግር በሆነ ጊዜ ብቻ ሳይሆን በቁጥር 118 ድንጋጌ አነጋገር መሰረት በክሱ መገለጽ ይገባው የነበረ ነገር ግን ሳይገለጽ የቀረ መሰረታዊ ነገር መኖሩ ሲረጋገጥ ጭምር መሆኑን እና በወንጀሉ ተሳታፊ ነበረ የተባለ ሰው በማናቸውም ምክንያት በክሱ ውስጥ በተከሳሽነት ሳይካተት መቅረቱም ለክሱ መሰረታዊ የሚባል ነገር መሆኑን በመግለጽ ክሱ እንዲሻሻል ሊደረግ ይገባው ነበር በማለት የልዩነት ሀሳቡን አስፍሯል፡፡


    በዚህ ብይን ቅር በመሰኘት የማስረጃ ማሰማት ሂደቱን አቋርጦ አመልካች ባቀረበው ይግባኝ ሳቢያ የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት በስር ፍርድ ቤት የተያዘው ክርክር ለጊዜው ታግዶ እንዲቆይ በማድረግ የግራ ቀኙን ክርክር ከሰማ በኃላ ይግባኝ ወደ ተባለበት ፍሬ ጉዳይ ሳይገባ በቅድሚያ ሊመረመር የሚገባው የይግባኝ አቀራረቡ ስነ ስርዓታዊ አግባብነት መሆኑን ገልጾ በወንጀለኛ መቅጫ ሕግ ስነ ስርዓት ቁጥር 181(1) እና 184(መ) ድንጋጌዎች መሰረት ተከሳሹን ጥፋተኛ በማለት ወይም ነፃ በመልቀቅ ወይም ለጊዜው በመልቀቅ ውሳኔ ከተሰጠ በኋላ በዋናው ጉዳይ በተሰጠው ውሳኔ ላይ ከሚቀርበው ይግባኝ ጋር በአንድነት ካልሆነ በቀር በዋናው ጉዳይ ላይ ፍርድ ከመሰጠቱ በፊት በክስ ማሻሻል ክርክር ረገድ በሚሰጥ ብይን ወይም ትዕዛዝ ላይ ይግባኙን ነጥሎ ማቅረብ የሚቻልበት ስነ ስርዓታዊ አግባብ አለመኖሩን በምክንያትነት በመጥቀስ ይግባኙን ሳይቀበለው ቀርቷል፡፡

     

    አመልካች አቤቱታውን ለዚህ ችሎት ያቀረበውም የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ሰበር ችሎት አቤቱታውን ዘግቶ በማሰናበቱ ሲሆን የሰበር አቤቱታው ተመርምሮ በዚህ ጉዳይ አመልካች ክስ አቅርቦ ማስረጃ ከማሰማቱ በፊት ከተጠሪ ጋር አብሮ መከሰስ ያለበት ሌላ ግለሰብ መኖሩን ስለደረስኩበት ግለሰቡን ጨምሬ ክስ ላቅርብ በማለት ያቀረበውን ጥያቄ የስር ፍርድ ቤቶች ክስ ለማሻሻል የሚፈቀደው ክሱ ተከሳሹን የሚያሳስት ወይም ፍርድ ለመስጠት አስቸጋሪ ሲመስል ብቻ ነው በማለት ጥያቄውን ውድቅ የማድረጋቸውን አግባብነት ከወንጀለኛ መቅጫ ሕግ ስነ ስርዓት ቁጥር 119 ድንጋጌ አንጻር ተጠሪው ባሉበት ለማጣራት ይቻል ዘንድ ጉዳዩ ለሰበር ክርክር እንዲቀርብ በመደረጉ ግራ ቀኙ የጽሁፍ ክርክር ተለዋውጠዋል፡፡የጉዳዩ አመጣጥ እና የክርክሩ ይዘት ከላይ የተመለከተው ሲሆን እኛም ለክርክሩ ወደ ተያዘው የፍሬ ጉዳይ የክርክር ጭብጥ ከመገባቱ በፊት እልባት ማግኘት የሚገባው በዋናው ጉዳይ ላይ ፍርድ ከመሰጠቱ በፊት በክስ ማሻሻል ክርክር ረገድ በሚሰጥ ብይን ወይም ትዕዛዝ ላይ ይግባኙን ነጥሎ ማቅረብ የሚቻልበት ስነ ስርዓታዊ አግባብ አለመኖሩን በምክንያትነት ጠቅሶ ይግባኙን ባለመቀበል የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት የሰጠው እና በጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ሰበር ችሎት ተቀባይነት ያገኘው ውሳኔ ሕጋዊ መሰረት ያለው ነው ወይስ አይደለም? የሚለው ነጥብ መሆኑን በመገንዘብ አቤቱታ የቀረበበት ውሳኔ መሰረታዊ የሕግ ስህተት የተፈጸመበት መሆን አለመሆኑን ከዚሁ ጭብጥ አንፃር መርምረናል፡፡

     

    በዚህም መሰረት የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት  ለውሳኔው መሰረት ካደረጋቸው የወንጀለኛ መቅጫ ስነ ስርዓት ሕጉ ሁለት ድንጋጌዎች መካከል ከላይ ለተጠቀሰው ጭብጥ ቀጥተኛ አግባብነት ያለው ቁጥር 184 ድንጋጌ ሲሆን ይህ ድንጋጌም ተከሳሹን ጥፋተኛ በማለት ወይም ነፃ በመልቀቅ ወይም ለጊዜው በመልቀቅ ውሳኔ ከተሰጠ በኃላ በዋናው ጉዳይ በተሰጠው ውሳኔ ላይ ከሚቀርበው ይግባኝ ጋር በአንድነት ካልሆነ በቀር በቁጥር 94 መሰረት ቀጠሮ መስጠትን ወይም አለመስጠትን ወይም በቁጥር 131 መሰረት የሚቀርብ መቃወሚያን ወይም በቁጥር 146 መሰረት ማስረጃን መቀበልን ወይም አለመቀበልን አስመልክቶ በሚሰጡ ትዕዛዞች ላይ ይግባኙን ነጥሎ ማቅረብን የሚከለክል ነው፡፡

     

    እንደሚታየው ይህ ድንጋጌ ትዕዛዞቹ መሰረት የሚያደረጓቸውን ድንጋጌዎች ጭምር በመጥቀስ ከስረ ነገሩ ፍርድ በፊት የትዕዛዝ ይግባኝ ክልከላ የተጣለባቸውን ጉዳዮች የሚዘረዝር ሲሆን ከዝርዝሩ ውስጥ የክስ ማሻሻል ጉዳይም ሆነ የክስ ማሻሻል ጉዳይ መሰረት የሚያደርጋቸውን ቁጥር 118 እና 119 ድንጋጌዎች አልተካተቱም፡፡ይህም ሕጉ የትዕዛዝ ይግባኝ ክልከላ በግልጽ ከጣለባቸው ውጪ በሆኑ የመጨረሻ ትዕዛዝ በተሰጠባቸው ጉዳዮች ላይ (የክስ ማሻሻል   ጥያቄን


    ውድቅ ከማድረግ ጉዳይ ጋር የተያያዙትን ጨምሮ) ከስረ ነገሩ ፍርድ በፊትም ቢሆን ይግባኝ ማቅረብን አስመልክቶ የስነ ስርዓት ሕጉ ያስቀመጠው ክልከላ አለመኖሩን መገንዘብ የሚያስችል ነው፡፡በተያዘው ጉዳይ የክስ ማሻሻል ጥያቄውን ውድቅ በማድረግ የተሰጠውን ትዕዛዝ በየትኛውም ደረጃ በሚገኝ ፍርድ ቤት ቢሆን ከአሁኑ ተጠሪ ቀጣይ የወንጀል ክርክር ሂደት ጋር የሚያስተሳስረው ነገር ባለመኖሩ እና ትዕዛዙ የተሰጠበት ጉዳይ በድጋሚ ለክርክር ሊቀርብ የሚችልበት ዕድል የሌለ በመሆኑ ትዕዛዙ የመጨረሻ እንጂ ጊዜያዊ አገልግሎት እንዳለው ተቆጥሮ በስረ ነገሩ ከሚሰጠው ፍርድ ጋር ተጠቃሎ ይግባኝ የሚባልበት ነው ሊባል የሚችል አይደለም፡፡በመሆኑም ይግባኙ የቀረበው በስነ ስርዓት ሕጉ የተመለከተውን የይግባኝ አቀራረብ ስርዓት መሰረት አድርጎ ባለመሆኑ ሊስተናገድ አይገባውም በማለት በክልሉ የበላይ ፍርድ ቤቶች የተሰጠው ውሳኔ ሕጋዊ መሰረት ያለው ነው ለማለት የሚቻል ሆኖ አልተገኘም፡፡

     

    ሲጠቃለል የወንጀለኛ መቅጫ ስነ ስርዓት ሕግ ቁጥር 184 ድንጋጌ የትዕዛዝ ይግባኝ ክልከላን የሚጥለው ከስረ ነገሩ ፍርድ በፊት በሚሰጡ ሁሉም ትዕዛዞች ላይ እንደሆነ አድርጎ በመተርጎም የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት የሰጠው እና በጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ሰበር ችሎት ተቀባይነት ያገኘው ውሳኔ መሰረታዊ የህግ ስህተት የተፈጸመበት ሆኖ በመገኘቱ የሚከተለው ውሳኔ ተሰጥቷል፡፡

     

     ው ሳ ኔ

     

    1. በትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በመዝገብ ቁጥር 57074 በ06/06/2005 ዓ.ም. ተሰጥቶ በጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ሰበር ችሎት በመዝገብ ቁጥር 58589 በ12/10/2005 ዓ.ም. በትዕዛዝ የጸናው ውሳኔ ተሽሯል፡፡

    2. የወንጀለኛ መቅጫ ስነ ስርዓት ሕግ ቁጥር 184 ድንጋጌ የትዕዛዝ ይግባኝ ክልከላ በግልጽ ከጣለባቸው ውጪ በሆኑ የመጨረሻ ውሳኔ ወይም ትዕዛዝ በተሰጠባቸው ጉዳዮች ላይ ከስረ ነገሩ ፍርድ በፊትም ቢሆን ይግባኝ ማቅረብን አስመልክቶ የስነ ስርዓት ሕጉ ያስቀመጠው ግልጽ ክልከላ ባለመኖሩ በዚህ መዝገብ ለተያዘው ክርክር ምክንያት የሆነው የክስ ማሻሻል ጉዳይ ከስረ ነገሩ ፍርድ በፊት ይግባኝ ሊቀርብበት የሚችል ነው በማለት ወስነናል፡፡

    3. ይህንኑ በመገንዘብ የቀረበለትን የይግባኝ ክርክር መርምሮ ተገቢውን ውሳኔ ይሰጥበት ዘንድ የዚህ ውሳኔ ግልባጭ ለክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት እንዲላክ ወስነናል፡፡

    4.  ውሳኔ ያገኘ ስለሆነ መዝገቡ ተዘግቷል፡፡

     

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡

  • Family law

    Pecuniary effect of marriage

    Common property

    ጋብቻ ፀንቶ በነበረበት ጊዜ ባንደኛው ተጋቢ ተገዝቶ ነገር ግን ስመሀብቱ ከ3ኛ ወገን ሻጭ ሳይዛወር የቀረ መሆኑ ንብረቱ የተጋቢዎች የጋራ ሀብትነው ከመባል የሚያስቀረው ስላልመሆኑ፣

    94811

  • ከጋብቻ በፊት በአንደኛው ተጋቢ ስም የነበረን የግል ንብረት በጋብቻ ወቅት በንብረቱ ላይ መሰረታዊ መሻሻል ቢደረግበትና ይሄው መሻሻል የተደረገው የባለንብረቱ የግል ገንዘብ መሆኑ እስካልተረጋገጠ ድረስ ህጉ ንብረቱ የጋራ ነው የሚል ግምት የሚወስድ ስለመሆኑ፣

    አዋጅ ቁጥር 213/1992 አንቀፅ 63(1)

    የሰ/መ/ቁ. 94952

     

    መስከረም 30 ቀን 2007 ዓ.ም.

     

    ዳኞች፡- አልማው ወሌ

     

    ሡልጣን አባተማም መኰንን ገ/ሕይወት ሙስጠፋ አህመድ ተፈሪ ገብሩ

    አመልካች፡- ወ/ሮ ዙሪያሽ ተገኝ - የቀረበ የለም፡፡

     

    ተጠሪ፡- ወ/ሮ የሺ ውድዬ - ረ/ኢንስፔክተር ይመር ዮሴፍ ቀረቡ፡፡ መዝገቡ ተመርምሮ የሚከተለው ፍርድ ተሰጥቶአል፡፡

     ፍ ር ድ

     

    ጉዳዩ በሞት የተለየው ተጋቢ የግል ንብረት ነው የተባለን ቤት ከሌላኛዋ ተጋቢ  ለማስለቀቅ ከቀረበ ክስ ጋር ተያይዞ የተነሳ ክርክርን የሚመለከት ሲሆን የተጀመረውም ከሳሽ የነበሩት የአሁኗ ተጠሪ በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ተከሳሽ በነበሩት በአሁኗ አመልካች ላይ በ08/02/2003 ዓ.ም. አዘጋጅተው ባቀረቡት ክስ ነው፡፡

     

    የክሱይዘትም ባጭሩ፡-ከሳሽ የሟች ልጃቸው አቶታደሰ የሱፍ እናት እና ወራሽ መሆናቸውን፣ሟች እና ተከሳሽ በ17/09/1997 ዓ.ም. በባህላዊ ስርዓት ጋብቻ ፈጽመው አብረው ይኖሩ የነበረ መሆኑን፣በን/ስ/ላፍቶ ክፍለ ከተማ በቀበሌ 09/14 የሚገኘው ቁጥሩ አዲስ የሆነው መኖሪያ ቤት ከጋብቻው በፊት የተፈራ የአቶ ታደሰ የሱፍ የግል ሀብት ስለመሆኑ ጋብቻውን በፈጸሙበት ጊዜ ባደረጉት የጋብቻ ውል ማረጋገጣቸውን፣ይሁን እንጂ ጋብቻው በልጃቸው ሞት ምክንያት መፍረሱን ተከትሎ ተከሳሽ ቤቱን እና በክሱ የተጠቀሱ የቤት ቁሳቁሶችን ለከሳሽ እንዲያስረክቡ ተጠይቀው ፈቃደኛ ሳይሆኑ መቅረታቸውን የሚገልጽ ሆኖ ተከሳሽ የዋጋ ግምቱ ብር 25,000 (ሃያ አምስት ሺህ) የሆነውን ቤት እና የብር 10,000 (አስር ሺህ) የዋጋ ግምት ያላቸውን የቤት ቁሳቁሶች ለከሳሽ እንዲያስረክቡ እና ለስምንት ወራት ከቤቱ ኪራይ የሰበሰቡትን ገንዘብ ብር 8,000 (ስምንት ሺህ) ለከሳሽ እንዲከፍሉ ይወሰን ዘንድ ዳኝነት የተጠየቀበት ሲሆን ተከሳሽ በበኩላቸው በ09/07/2003 ዓ.ም. በሰጡት መልስ ከጋብቻው በፊት ሟች የሰሩት አንድ ሳሎን እና አንድ መኝታ ያለው ሁለት ክፍል ቤት ሆኖ ከጋብቻቸው በኃላ ሶስት ተጨማሪ ክፍሎችን ከሟች ጋር የሰሩ በመሆኑ ቤቱ በሙሉ የሟች የግል ሀብት እንደሆነ ተደርጎ የቀረበው ክስ ተገቢነት የሌለው መሆኑን፣የቤት ቁሳቁሶቹ ግምት ከብር 1,000 የማይበልጥ መሆኑን እና ከቤቱ ኪራይ የተሰበሰበው የገንዘብ መጠንም ከቀለብ አልፎ ሊጠራቀም የማይችል መሆኑን በመግለጽ ክሱ ውድቅ እንዲደረግ ተከራክረዋል፡፡


    ፍርድ ቤቱ ውርሱ ተጣርቶ ሪፖርት እንዲቀርብለት ጉዳዩን ለውርስ አጣሪ የመራው ሲሆን አጣሪው ውርሱን ማጣራቱን ገልጾ ነገር ግን ቤቱ ሰነድ አልባ ስለመሆኑ ግራ ቀኙ የተማመኑ በመሆኑ የውርስ ሀብት ነው ለማለት ያልተቻለ መሆኑን በመግለጽ ሪፖርት  አቅርቧል፡፡ፍርድ ቤቱ በበኩሉ ቤቱ ሰነድ አልባ መሆኑ ክርክሩን አይቶ ውሳኔ ከመስጠት የማይከለክል  መሆኑን እና በመዝገቡ የሚሰጠው ውሳኔ ተፈጻሚነት የሚኖረው የቤቱን ሕጋዊነት በተመለከተ ጉዳዩ የሚመለከተው አካል በሚሰጠው ውሳኔ ላይ ተመስርቶ መሆኑን ገልጾ ተጋቢዎቹ ከጋብቻቸው በኃላ የሰሩት ተጨማሪ ግንባታ መኖር አለመኖሩን ለማጣራት የግራ ቀኙን ምስክሮች ከሰማ በኋላ ቤቱ የአንደኛው ተጋቢ የግል ሀብት ስለመሆኑ ተከሳሽ                                        በፈረሙት  የጋብቻ ውል በማረጋገጣቸው ከቤቱ ድርሻ አላቸው ማለት ያልተቻለ መሆኑን፣ቤቱ በጋብቻ  ውሉ ላይ የተገለጸው "ቤት" ተብሎ እንጂ የተከሳሽ ምስክሮች እንደገለጹት "የሸራ ወይም የላስቲክ ቤት" ተብሎ አለመሆኑን፣ስለቤት ቁሳቁሶች በከሳሽ ምስክሮች የተገለጸ ነገር አለመኖሩን እና ከቤቱ ኪራይ ይሰበሰብ የነበረው የገንዘብ መጠንም ከቀለብ አልፎ ሊጠራቀም የሚችል አለመሆኑን በዝርዝር በመግለጽ ተከሳሽ ክስ ያስነሳውን ቤት ለከሳሽ ለቀው እንዲያስረክቡ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ አመልካች አቤቱታቸውን ለዚህ ችሎት ያቀረቡት የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ይግባኙን ዘግቶ በማሰናበቱ ሲሆን አቤቱታው ተመርምሮ በጋብቻ ውሉ ላይ ቤቱ የአቶ ታደሰ የሱፍ የግል ንብረት ነው ተብሎ መጠቀሱን ብቻ መሰረት በማድረግ በጋብቻው ጊዜ በሁለቱ ተጋቢዎች በጋራ ከታደሰው ቤት እና በጋራ ከተሰሩት ተጨማሪ ክፍሎች ውስጥ አመልካች ድርሻ የላቸውም ተብሎ የመወሰኑን አግባብነት ተጠሪዋ  ባሉበት                                        ለማጣራት ይቻል ዘንድ ጉዳዩ ለሰበር  ክርክር እንዲቀርብ በመደረጉ ግራ ቀኙ የጽሁፍ ክርክር ተለዋውጠዋል፡፡የጉዳዩ አመጣጥ እና የክርክሩ ይዘት ከላይ የተመለከተው ሲሆን እኛም ክርክሩ የታየበትን የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት መዝገብ በማስቀረብ ጭምር ውሳኔው መሰረታዊ የሕግ ስሕተት የተፈጸመበት መሆን አለመሆኑን ለጉዳዩ ከተያዘው ጭብጥ አንፃር መርምረናል፡፡

    በዚህም መሰረት አመልካች አድራሻው በክሱ የተጠቀሰው ቤት ከጋብቻው በፊት የተፈራ የተጠሪ አውራሽ የግል ንብረት መሆኑን በማረጋገጥ ጋብቻው በተፈጸመበት ጊዜ የጋብቻ ውል የፈረሙ መሆኑ በአመልካች ያልተካደ እና የጋብቻ የውል ሰነዱን ጨምሮ በማስረጃ የተረጋገጠ በመሆኑ የጋብቻ ውሉ በተፈረመበት ጊዜ የነበረው ከላስቲክ እና ከሸራ የተሰራ ዳስ ሆኖ እያለ ቤት እንደሆነ አድርገው ያስፈረሙኝ አላግባብ ነው በማለት አመልካች  በሰበር ማመልከቻቸው ያቀረቡት ክርክር ሕጋዊ ተቀባይነት ያለው ነው ለማለት የሚቻል ሆኖ አልተገኘም፡፡

    በሌላ በኩል ግን በጋብቻው ወቅት ተጨማሪ ክፍሎች የተገነቡ ወይም የተሰሩ ስለመሆኑ በማስረጃ ተረጋግጦ እያለ ቤቱ ሙሉ በሙሉ የሟች የግል ሀብት እንደሆነ ተደርጎ ለተጠሪ እንድትለቅ የተሰጠው ውሳኔ መሰረታዊ የህግ ስህተት የተፈጸመበት ነው በማለት አመልካች ያቀረቡት የአቤቱታ ነጥብ በክርክሩ ከተረጋገጡት ፍሬ ነገሮች አንጻር በአግባቡ ሊጤን እና ሊመረመር የሚገባው መሆኑን ተገንዝበናል፡፡በዚህም መሰረት ጉዳዩን በመጀመሪያ  ደረጃ የሚያየው ፍርድ ቤት በፍትሐብሄር ስነ ስርዓት ህግ ቁጥር 246፣247 እና 248 ድንጋጌዎች መሰረት ለጉዳዩ ትክክለኛ ውሳኔ ለመስጠት የሚያስችለውን ጭብጥ ይዞ ጉዳዩን በማስረጃ ካጣራ በኃላ ፍርድ በሚሰጥበት ጊዜ በክርክሩ የተያዘው ጭብጥ ምን እንደሆነ፣ጭብጡ እንዴት እንደተወሰነና በአንድ ወይም በሌላ አግባብ የተወሰነው በምን  ምክንያት  እንደሆነ በፍርድ ሀተታው ውስጥ መግለጽ እንዳለበት በቁጥር 182 (1) ስር በአስገዳጅነት ተደንግጎአል፡፡

    በተያዘው ጉዳይ ተጠሪ ክስ ያቀረቡት እና የተከራከሩት በጋብቻ ውሉ መሰረት ክርክር ያስነሳው ቤት የልጃቸው የግል ሀብት መሆኑን በመግለጽ ሲሆን አመልካች በበኩላቸው መልስ  የሰጡት እና የተከራከሩት ከተጠሪ  ልጅ ጋር  በጋብቻ  ውስጥ  በኖሩባቸው ከ1997  ዓ.ም.እስከ   2002


    ዓ.ም.ድረስ ባሉት ጊዜያት ቀደም ሲል ከነበሩት ሁለት ክፍል ቤቶች በተጨማሪ ሶስት ክፍል ቤቶችን በጋራ መስራታቸውን በመግለጽ ነው፡፡ከዚህ የግራ ቀኙ የክርክር አቋም በመነሳት በማስረጃ ሊጣራ የሚገባው ተጋቢዎቹ ከጋብቻቸው በኃላ የሰሩት ተጨማሪ ግንባታ አለ ወይስ የለም? የሚል ነጥብ መሆኑን በመግለጽ ፍርድ ቤቱ ለክርክሩ የያዘው ጭብጥ ተገቢነት ያለው መሆኑን ተገንዝበናል፡፡

    በዚህ ጭብጥ ላይ የተሰሙት የግራ ቀኙ ምስክሮች ቃል ሲታይም በአሁኗ አመልካች በኩል የተሰሙት ሁለት ምስክሮች ሟች ከቀድሞ ሚስታቸው ጋር የሰሩትን አንድ ክፍል ቤት አመልካች እና የተጠሪ ልጅ በጋብቻቸው ጊዜ አፍርሰው ቤቱን እንደ አዲስ ሶስት ክፍል አድርገው መስራታቸውን በተመሳሳይ ሁኔታ የገለጹ መሆኑን እንዲሁም በአሁኗ ተጠሪ በኩል ከተሰሙት ሁለት ምስክሮች መካከል 2ኛው ምስክር ቤቱ ጎርፍ የሚገባበት በመሆኑ አጥሩ ሲፈርስ የተጠጋገነ ከመሆኑ ውጪ ከጋብቻው በኃላ የተሰራ ቤት አለመኖሩን በመግለጽ የመሰከሩ ቢሆንም የተጠሪ 1ኛ ምስክር ግን ሟች ከቀድሞ ባለቤታቸው ጋር የሰሩት ዋናውን ቤት መሆኑን እና ከአመልካች ጋር ጋብቻ ከፈጸሙ በኃላ ደግሞ ሁለት ክፍል ቤት እና ኩሽና በጋራ መስራታቸውን በመግለጽ መመስከራቸውን የመዝገቡ ግልባጭ ያመለክታል፡፡ፍርድ ቤቱም ከላይ በተጠቀሰው የፍትሐብሔር ስነ ስርዓት ህግ ቁጥር 182 (1) አስገዳጅ ድንጋጌ መሰረት ውሳኔውን በሚሰጥበት ጊዜ ይህንን የግራ ቀኙን ምስክሮች የምስክርነት ቃል መዝኖ የአንደኛውን ወይም የሌላኛውን ወገን ምስክሮች የምስክርነት ቃል የተቀበለበትን ወይም ያልተቀበለበትን ምክንያት በውሳኔው ላይ ማስፈር የሚጠበቅበት ሆኖ እያለ ቤቱ የሟች የግል ሀብት ነው በማለት ለደረሰበት ድምዳሜ እና ለሰጠው ውሳኔ መሰረት ያደረገው የጋብቻ ውሉን ብቻ መሆኑን የውሳኔው ይዘት ያመለክታል፡፡ ይህም በአንድ በኩል ተጋቢዎቹ ከጋብቻቸው በኃላ የሰሩት ተጨማሪ ግንባታ አለ ወይስ የለም? በሚል ፍርድ ቤቱ በጭብጥነት የያዘው ነጥብ ከግራ ቀኙ የክርክር አቋም አንጻር ተገቢነት ያለው ቢሆንም በሌላ በኩል ግን ቤቱ በጋብቻ ውሉ መሰረት የሟች የግል ሀብት  ነው በማለት የደረሰበት ድማዳሜ እና የሰጠው ውሳኔ ከላይ የተጠቀሰውን ጭብጥ ለማጣራት በተሰሙት የግራ ቀኙ ምስክሮች ከተረጋገጠው ፍሬ ነገር ውጪ መሆኑን መገንዘብ የሚያስችል ነው፡፡የዚህ ዓይነቱ የውሳኔ አሰጣጥ ስርዓት ደግሞ የፍትሐብሔር ስነ ስርዓት ህግ ቁጥር 182 (1) አስገዳጅ ድንጋጌን እና በአንድ ክርክር በመዝገቡ ከተረጋገጠው ፍሬ ነገር ውጪ የሚሰጥ ውሳኔ ተገቢነት የሌለው ስለመሆኑ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ችሎት በመዝገብ ቁጥር 36848 በ11/02/2001 ዓ.ም. እና በሌሎችም መዝገቦች የሰጠውን አስገዳጅ የሕግ ትርጉም የሚቃረን በመሆኑ ሕጋዊ ተቀባይነት ሊሰጠው የሚገባ አይደለም፡፡

    በክርክሩ በማስረጃ የተረጋገጠው ፍሬ ነገር ከጋብቻው በፊት የአንደኛው ተጋቢ የግል ሀብት መሆኑ በጋብቻ ውሉ ከተረጋገጠው አንድ ክፍል ዋናው ቤት በተጨማሪ ተጋቢዎቹ በጋብቻቸው ጊዜ ሶስት ተጨማሪ ክፍሎችን መስራታቸው ከሆነ ደግሞ ይህ ሁኔታ በግራ ቀኙ መብትና ግዴታ ላይ የሚያስከትለው ሕጋዊ ውጤት መታየት ይኖርበታል፡፡በመሰረቱ ተጋቢዎች ከጋብቻቸው በፊት በየግል የነበሯቸው ንብረቶች የየግላቸው ሆነው እንደሚቀሩ እና ከጋብቻቸው በኃላ ያፈሯቸው ንብረቶች ግን የጋራቸው እንደሚሆኑ በአዋጅ ቁጥር 213/1992 በተሻሻለው የቤተሰብ ሕግ በአንቀጽ 57 እና 62 ድንጋጌዎች ተመልክቷል፡፡በተያዘው ጉዳይ ከጋብቻው በፊት የነበረው እና በጋብቻ ውሉ የአንደኛው ተጋቢ የግል ንብረት ነው ተብሎ የነበረው አንድ ክፍል ዋናው ቤትም ቢሆን በጋብቻው ውስጥ ፈርሶ እንደ አዲስ መሰራቱ እና ኩሽናውን ጨምሮ ሶስት ተጨማሪ ክፍሎች በጋብቻው ውስጥ መሰራታቸው በማስረጃ ተረጋግጧል፡፡ከጋብቻው በፊት የነበረው ቤት ፈርሶ እንደ አዲስ የተሰራ እና ሶስት ተጨማሪ ክፍሎች የተሰሩ መሆኑ ከተረጋገጠ ደግሞ እነዚህ ስራዎች የተከናወኑት በጋብቻው ውስጥ እስከሆነ እና እነዚህ ተጨማሪ   ስራዎች


    የተከናወኑት በሟች የግል ገንዘብ ነው በሚል የቀረበ ክርክር እና ማስረጃ እስከሌለ ድረስ በቤተሰብ ሕጉ አንቀጽ 63 (1) መሰረት ክርክር ያስነሳው ቤት የተጋቢዎቹ የጋራ ሀብት ስለመሆኑ የሕግ ግምት የሚወሰድበት ነው፡፡

    ሲጠቃለል ከጋብቻው በኃላ ስለተከናወኑት ተጨማሪ ስራዎች በግራ ቀኙ ምስክሮች የተመሰከረውን ፍሬ ነገር በዝምታ አልፎ በጋብቻ ውሉ ላይ ብቻ በማተኮር ክርክር ያስነሳው ቤት ከጋብቻው በፊት የተፈራ የሟች የግል ንብረት ነው በማለት በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ተሰጥቶ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የጸናው ውሳኔ በማስረጃ ከተረጋገጠው ፍሬ ነገር ውጪ የተሰጠ እና መሰረታዊ የሕግ ስሕተት የተፈጸመበት ሆኖ በመገኘቱ የሚከተለው ውሳኔ ተሰጥቷል፡፡

     ው ሳ ኔ

    1. በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በመዝገብ ቁጥር 58686 በ02/07/2005 ዓ.ም. ተሰጥቶ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመዝገብ ቁጥር 135319 በ22/02/2006 ዓ.ም. በትዕዛዝ የጸናው ውሳኔ በፍትሐብሔር ስነ ስርዓት ህግ ቁጥር 348  (1) መሰረት ተሻሽሏል፡፡

    2. በተራ ቁጥር 1 ከተጠቀሰው ውሳኔ ውስጥ በን/ላ/ክፍለ ከተማ በቀበሌ 09/14 የሚገኘው ቁጥሩ አዲስ የሆነው መኖሪያ ቤት ከጋብቻው በፊት የተፈራ የአቶ ታደሰ የሱፍ የግል ንብረት በመሆኑ አመልካች ቤቱን ለቀው ለተጠሪ ሊያስረክቡ ይገባል በሚል የተሰጠው የውሳኔ ክፍል በፍትሐብሔር ስነ ስርዓት ህግ ቁጥር 348(1) መሰረት ተሽሯል፡፡

    3. ለክርክሩ ምክንያት የሆነው በን/ላ/ክፍለ ከተማ በቀበሌ 09/14 የሚገኘው ቁጥሩ አዲስ የሆነው መኖሪያ ቤት ሟች አቶ ታደሰ የሱፍ እና አመልካች በጋብቻው ጊዜ ያፈሩት የጋራ ሀብት ነው በማለት ወስነናል፡፡

    4. ከላይ ከተጠቀሰው ቤት ውስጥ ግማሹ የአመልካች በጋብቻ ወቅት የተፈራ የጋራ ሀብት፣ቀሪው ግማሽ ደግሞ የተጠሪ የውርስ ሀብት በመሆኑ ግራ ቀኙ የሚቻል ከሆነ በዓይነት፣የማይቻል ከሆነ በስምምነት አንዳቸው ለሌላኛው የዋጋ ግምት ድርሻ ከፍሎ በማስቀረት፣በዚህ የማይስማሙ ከሆነም በሐራጅ እንዲሸጥ ተደርጎ የሽያጩን ገንዘብ እኩል እንዲካፈሉ በማድረግ ሊካፈሉት ይገባል በማለት ወስነናል፡፡

    5. ከላይ በተራ ቁጥር 4 የተጠቀሰው የክፍፍል ውሳኔ አፈጻጸም  ጉዳዩ የሚመለከተው የአስተዳደር አካል የቤቱን ሕጋዊነት አስመልክቶ ሊያነሳ የሚችለውን ጥያቄ የሚያስቀር አይሆንም በማለት ወስነናል፡፡

    6. በተራ ቁጥር 1 ከተጠቀሰው ውሳኔ ውስጥ የቤት ቁሳቁሶችን እና ከቤቱ ኪራይ  የተገኘውን ገቢ አስመልክቶ የተሰጠው የውሳኔ ክፍል በፍትሐብሔር ስነ ስርዓት ህግ ቁጥር 348 (1) መሰረት ፀንቷል፡፡

    7. ጥያቄው ሲቀርብለት ከላይ በተራ ቁጥር 3፣4 እና 5 በተጠቀሰው ውሳኔ መሰረት እንዲያስፈጽም የዚህ ውሳኔ ግልባጭ ለፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ይላክ፡፡

    8.  ቁጥሩ 58686 የሆነው መዝገብ ተመላሽ ይደረግ፡፡

    9.  የሰበር ክርክሩ ያስከተለውን ወጪና ኪሳራ ግራ ቀኙ የየራሳቸውን ይቻሉ፡፡

    10. ውሳኔ ያገኘ ስለሆነ መዝገቡ ተዘግቷል፡፡

     

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡                              ብ/ግ

  • አንድ የኤሌክትሮኒክስ ዕቃ ለገዥ የሸጠ ሻጭ የገባው ውል እቃው ቢበላሽ ጥገና ለማድረግ እያለ ሆኖ እያለና ለድብቅ ጉድለቶች ኃላፊነት ሳይኖርበት ከውላቸው ውጭ እና ከህግ ውጭ እቃው ስላልሰራ እቃውን እንዲቀይር ወይም ገንዘቡን እንዲመልስ ሊደረግ የማይችል ስለመሆኑ፡- የፍ/ህ/ቁ 1731፣2266፣2288-2293፣2300

    የሰ/መ/ቁ. 95072

    ጥር 07 ቀን 2007 ዓ/ም


     

    ጉዳዩ የማቀዝቀዣ(ፊሪጅ) ሽያጭን መሰረት አድርጎ የቀረበውን ክርክር የሚመለከት ሲሆን ክርክሩ የተጀመረው የአሁኗ ተጠሪ ባሁኑ አመልካች ላይ በመሰረቱት ክስ መነሻ ነው፡፡ የክሱ ይዘትም ከተጠሪ በብር 16,750.00 የገዙት ፊሪጅ አስፈላጊውን አገልግሎት መስጠት እንደማይችል እንደተረዱ ወደአመልካች ድርጅት አድርስው ድርጅቱ  እቃው እንደሚስተካከልላቸው ነግሯቸው እቃውን ተስተካክሏል በሚል ወደ ቤት ቢመልሱትም በተመሳሳይ ሁኔታ ለሁለተኛ ጊዜ ተበላሽቶ አገልግሎት መስጠት በማቆሙ እቃውን እንዲቀየርላቸው ድርጅቱን ቢጠየቁም ድርጅቱ ፈቃደኛ ያለመሆኑን ዘርዝረው አመልካች ድርጅት እቃውን እንዲቀይርላቸው ወይም የሽያጭ ገንዘቡን እንዲመልስላቸው ይወሰን ዘንድ ዳኝነት መጠየቃቸውን የሚያሳይ ነው፡፡ የአሁኑ አመልካች ለክሱ በሰጠው መልስም ከተጠሪ ጋር የፊሪጅ ሽያጭ ውል መኖሩን ሳይክድ ማቀዝቀዣው ተጠግኖ እንዲሰራ ማድረጉን፣ ለአንድ አመት ደግሞ የጥገና ዋስትና ግዴታ ከመግባቱ ውጪ ፊሪጁን ለመቀየር ወይም የሽያጭ ገንዘቡን ለመመለስ ግዴታ ያለመግባቱንና ባለው የጥገና ዋስትና መሰረት ማቀዝቀዣውን ጠግኖ  አመልካች ለመውሰድ ፈቃደኛ ያለመሆናቸውን ገልፆ ክሱ ውድቅ ሊሆንይገባል በማለት ተከራክሯል፡፡ ጉዳዩን በመጀመሪያ ደረጃ የተመለከተው የአዳማ ወረዳ ፍርድ ቤትም ፊሪጁ መስራት አለመስራቱን በቦታው ላይ ተገኝቶ ከተመለከተ በኋላ ጉዳዩን መርምሮ ፍሪጁ መስራቱን መመልከቱን ገልፆ አመልካች በውሉ ባለው የጥግና ዋስትና ውል ግዴታውን መወጣቱ መረጋገጡን በምክንያትነት ይዞ ክሱን ውድቅ አድርጎታል፡፡ በዚህ ውሳኔ የአሁኗ ተጠሪ ቅር በመሰኘት ይግባኛቸውን ለአዳማ ልዩ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቅርበው ፍርድ ቤቱ ፍሪጁ መስራት አለመስራቱ ከሁለት ድርጅቶች ባለሙያ ተመድቦ እንዲጣራ ትዕዛዝ ቢሰጥም አመልካች ድርጅት ከኦሜዳድ ድርጅት የተላከውን ባለሙያ ማቀዝቀዣውን እንዳይመለከት አድርጎ ሳልኔት ከተባለው ድርጅት የተላከው ባለሙያ ብቻ እንዲመለከት አድርጎ ይህ ድርጅት ያቀረበውን ሪፖርት በመመርመር የአመልካች አካሄድ ከቅን ልቦና የሆነ ነው በሚል ድምዳሜ አመልካች ለተጠሪ ተመሳሳይ ሞዴል ማቀዝቀዣ እንዲቀይርላቸው ወይም ዋጋውን ብር 16,750.00 እንዲመልስላቸው ሲል ወስኗል፡፡ በዚህ ውሳኔ የአሁኑ አመልካች ቅር በመሰኘት  ይግባኙን ለክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት አቅርቦ ፍርድ ቤቱም ግራ ቀኙን ከአከራከረ እና


    በኦሜዳድም ሆነ በሳልኔት ድርጅት ባለሙያዎች ማቀዝቀዣው መስራት ያለመስራቱ ተጣርቶ እንዲቀርብ አድርጎ ድርጅቶቹ ባቀረቡት ሪፖርት መሰረት ማቀዝቀዣ መስራቱ ቢረጋገጥም የባለሙያዎቹ አስተያየት እንደ አስገዳጅ ማስረጃ ሊወሰድ እንደማይችል፣እቃው ከሶስት ወራት በኋላ የማይበላሽ መሆኑን እርግጠኛ መሆን እንደማይቻል፣አዲስ የተገዛ እቃ ሁል ጊዜ እያስጠገኑ መጠቀም አለበት ሊባል እንደማይገባ በምክንያት ይዞ የዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት የሰጠውን ውሳኔ በድምፅ ብልጫ ሙሉ በሙሉ አንጽንቶታል፡፡በዚህ ውሳኔ የአሁኑ አመልካች መሰረታዊ የህግ ስህተት አለበት በማለት ለክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት አቤቱታውን ያቀረበ ቢሆንም ተቀባይነት አላገኘም፡፡የአሁኑ የሰበር አቤቱታ የቀረበውም ይህንኑ ውሳኔ በመቃወም ለማስለወጥ ነው፡፡የአመልካች የሰበር አቤቱታ መሰረታዊ ይዘትም፡- ለተጠሪ የተሸጠው ማቀዝቀዣ የተበላሸው በተጠሪ የአጠቃቀም ችግር የተከሰተ ሁኖ የሽያጭ ውሉም በአመልካች ላይ ለአንድ አመት የጥገና ግዴታ ከሚጥል በስተቀር እቃውን ለመቀየር ወይም የሽያጭ ገንዘቡን ለመመለስ የማያስገድድ ሁኖ እያለ የበታች ፍርድ ቤቶች የሰጡት ውሳኔ ከውሉና ከሕጉ ውጪ ነው የሚል ነው፡፡አቤቱታው ተመርምሮም በዚህ ችሎት እንዲታይ የተደረገ ሲሆን ለተጠሪም ጥሪ ተደርጎላቸው ግራ ቀኙ በጽሑፍ እንዲከራከሩ ተደርጓል፡፡

    የጉዳዩ አመጣጥ አጠር ባለመልኩ ከላይ የተገለጸው ሲሆን ይህ ችሎትም የግራ ቀኙን ክርክር ለሰበር አቤቱታው መነሻ ከሆነው ውሳኔ እና አግባብነት ካላቸው ድንጋጌዎች አንጻር በሚከተለው መልኩ መርምሮታል። እንደመረመረውም የበታች ፍርድ ቤቶች ውሳኔ በአመልካችና በተጠሪ የተገባውን የሽያጭ ውል ስምምነት መሰረት ያደረገ ነው ወይስ አይደለም የሚለው ነጥብ በጭብጥነት ሊታይ የሚገባው ሁኖ አግኝቶታል፡፡

    አመልካችና ተጠሪ የማቀዝቀዣ ሽያጭ ውል ማድረጋቸው፣አመልካች ማቀዝቀዣውን ቢበላሽ ለአንድ አመት የጥገና ዋስትና ግዴታ መግባቱን፣አመልካች እቃውን ለተጠሪ አስረክቦ ተጠሪ እቃውን በመጠቀም ላይ እንዳሉ መጀመሪያ ሲበላሽ አመልካች ባለው የጥገና ግዴታ እቃውን ጠግኖ ሲመልስ እንደገና በመበላሸቱ ተጠሪ እቃውን ለአመልካች መልሰው አመልካች እንደገና ጠግኖ እቃው እንዲሰራ ቢያደርግም ተጠሪ እቃው ካልተቀየረ አልረከብም ማለታቸው በክርክሩ ሂደት የተረጋገጡት ጉዳዮች ናቸው፡፡

    በመሰረቱ ሽያጭ ማለት ሻጭ የሆነው አንዱ ወገን ገዥ ለሆነው ሌላ ወገን ዋጋው በገንዘብ የተወሰነውን አንድ ነገር ገዥው ሊከፍለው ግዴታ በገባበት መሰረት ሊያስረክብና ሀብትነቱን ሊያስተላልፍ የሚገደድበት ውል መሆኑ በፍ/ሕ/ቁ.2266 ተመልክቷል ፡፡ በዚህ ድንጋጌ መሰረት ሻጭ የሆነ ወገን የሽያጩን ገንዘብ ከገዥ ወገን መጠየቅ መብት እንዳለው ሁሉ የተሸጠውን ነገር ደግሞ የማስረከብና ሀብትነቱን የማስተላለፍ ተነጻጻሪ ግዴታ ይኖርበታል፡፡ ሻጭ ያስረከበው ነገር በውሉ መሰረት ትክክል ለመሆኑና ጉድለት ስላለመኖሩ ለገዢው ኃላፊ ነው፡፡ ዕቃው እንደ ውሉ አይደለም የሚባለው ዋቢነት የሚሰጥባቸው ጉድለቶች እና ጉድለት ስለመኖሩ ፣ ጉድለት ያለከሆነ ደግሞ ጉድለቱ መቼ መመርመር እንዳለበት ፣ ገዢው የገዛው እቃ ጉድለት ያለበት ስለመሆኑ መቼ ማስታወቅ እንዳለበት እንዲሁም ጉድለትን አለማስታወቅና የሚያስከትለው ውጤትን አስመልክቶ በፍትሐብሔር ህጉ ከቁጥር 2288-2293 ድንጋጌዎች ስር በግልጽ ተመልክቷል ፡፡

    ገዢ ጉድለቱን ካወቀበት ወይም ጉድለት ያለበት መሆኑን ካስታወቀበት ግዜ አንስቶ እስከ አንድ ዓመት ክስ ካላቀረበ መብቱ በይርጋ የሚታገድ ስለመሆኑ በፍ/ሕ/ቁጥር 2298 የተመለከተ ሲሆን ይሁንና ሻጩ የደረሰውን ጉዳት የማስተካከል ወይም በአዲስ የመተካት መብቱ በፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 2300 ድንጋጌ ተጠብቆለታል፡፡


    የእቃውን ጉድለት መመርመርን በተመለከተ ህጉ ገዢው ግልፅ ጉድለትን በተመለከተ እቃውን በተረከበበት ግዜ የመመርመር ኃላፊነት እንዳለበት ሲያስቀምጥ ሻጩ ደግሞ ለድብቅ   ጉድለቶች

    /በርክክብ ወቅት ሊታዩ ወይም ሊገለጽ የማይችሉ/ ሃላፊነት / let the seller be aware of latent / hidden/ defects/ እንዳለበት ይደነግጋል፡፡

    ወደ ተያዘው ጉዳይ ስንመለስም ተጠሪ በአመልካች ላይ ክስ ያቀረቡት ጉድለት መኖሩን መሰረት አድርገው ሳይሆን ብልሽቱ እንዲጠገንላቸው ለአመልካች ጥያቄ አቅርበው አመልካች በግራ ቀኙመካከለ ባለው ውል መሰረት ጠግኖ ከሰጠ በኋላ እቃው እንደገና በመበላሸቱ ምክንያት በድጋሚ ሲጠገን ለታሰበው አገልግሎት ሊውል አይችልም በሚል  ነው፡፡ይሁን  እንጂ ማቀዝቀዣው የሚሰራ መሆኑ በባለሙያ የተረጋገጠ ሲሆን የባለሙያዎች አስተያየት ማቀዝቀዣው እስከመቼ እንደሚሰራ ባይረጋግጥም አመልካች ከተጠሪ ጋር ያለው ውል እቃው ቢበላሽ ጥገና ማድረግ መሆኑ ያልተካደ ጉዳይ ነው፤ስለሆነም አመልካች ለድብቅ ጉድለት ኃላፊነት አለበት ተብሎ ክስ ባልቀረበበትና በህጉ አግባብ የተቋቋመው ውል ደግሞ አድማሱ ለአንድ አመት ያህል አመልካች በነፃ የመጠገን ኃላፊነት ያለበት ስለመሆኑ የሚገልጽ ሁኖ እያለ ከግራ ቀኙ የውል ስምምነት እና ከፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 2300 ድንጋጌ ይዘት ውጪ አመልካች ማቀዝቀዣውን እንዲቀየር ወይም የሽያጭ ገንዘቡን እንዲመልስ ተብሎ የተወሰነው የፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 1731፣2298 እና 2300 ድንጋጌዎችን የጣሰ ሁኖ አግኝተናል፡፡ በመሆኑም በጉዳዩ ላይ የተሰጠው ውሳኔ የግራ ቀኙን ስምምነት እና በፍሬ ነገር ደረጃ የተረጋገጡትን ነጥቦችን ያላገናዘበ በመሆኑ መሰረታዊ የሆነ የሕግ ስህተት ያለበት ሁኖ ስለአገኘን ተከታዩን ወስነናል፡፡

     ው ሳ ኔ

     

    1. በአዳማ ልዩ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመ/ቁጥር 14450 መጋቢት 05 ቀን 2005 ዓ/ም ተሰጥቶ በኦሮሚያ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በመ/ቁጥር 160863 ነሐሴ 28 ቀን 2005 ዓ/ም ፣በክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት 174255 ህዳር 03 ቀን 2006 ዓ/ም በትዕዛዝ የፀናው ውሳኔ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 348(1) መሰረት ተሽሯል፡፡

    2. የአዳማ ወረዳ ፍርድ ቤት በመ/ቁ.58788 ሰኔ 15 ቀን 2004 ዓ/ም የሰጠው ውሳኔ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 348(1) መሰረት ፀንቷል፡፡

    3. አመልካች በውሉ በገባው ግዴታ መሰረት ማቀዝቀዣውን ጠግኖ አግልግሎት እንዲሰጥ ከማድረግ ውጪ ማቀዝቀዣውን የመቀየር ወይም የሽያጭ ገንዘቡን የመመለስ ግዴታ የለበትም ብለናል፡፡

    4. ግራ ቀኙ ወጪና ኪሳራ ይቻቻሉ ብለናል፡፡ መዝገቡ ተዘግቷል፤ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ ብለናል፡፡

     

     

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡

  • ሁለት የሞተር ተሽከርካሪዎች ሲጋጩ እያንዳንዱ ተሽከርካሪ በየራሱ አንዱ ከአንዱ ላይ ጉዳት እንዳደረሱ  የሚቆጠረውና የእያንዳንዱ መኪና ባለሀብት ለአደጋው ኃላፊ የሚሆነው አደጋው የደረሠው ከአንደኛው መኪና አሽከርካሪ ስህተት መሆኑ በማስረጃ ያልተረጋገጠ እንደሆነ ብቻ ስለመሆኑ፡-  የፍ/ሕ/ቁ 2084

    የሰ/መ/ቁ. 95267

    ጥቅምት 28 ቀን 2007 ዓ.ም.


     

    አመልካች፡-ናይል ኢንሹራንስ ኩባንያ አክሲዮን ማህበር ነገረ ፈጅ ይነበብ ደርሰህ-ቀረቡ ተጠሪዎች፡-

    1.  አቶ ካሣሁን ወንድሙ- ቀረቡ

    2.  አቶ  ግርማ ታጳኖ- ከክርክሩ ውጭ ተደርገዋል

    3. ኒያላ ኢንሹራንስ ኩባንያ አክሲዮን ማህበር- ነገረ ፈጅ ዮሴፍ ገብሬ ቀረቡ መዝገቡ ተመርምሮ የሚከተለው ፍርድ ተሰጥ~ል፡፡

     

     ፍ ር ድ

     

    ክርክሩ በተጀመረበት የሲዳማ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት ከሳሽ የነበረው የአሁኑ አመልካች በዚህ መዝገብ አቤቱታውን ያቀረበው በተሽከርካሪዎች ግጭት ምክንያት ጉዳት የደረሰበትን የደንበኛውን ተሽከርካሪ አስጠግኖ ወደ ነበረበት ለመመለስ ያወጣውን ወጪ ለማስተካት ያቀረበውን ክስ ውድቅ በማድረግ በስር ፍርድ ቤቶች የተሰጠው ውሳኔ መሰረታዊ የሕግ ስህተት የተፈጸመበት በመሆኑ ሊታረም ይገባል በማለት ነው፡፡

     

    የጉዳዩን አመጣጥ በተመለከተ አመልካች ለዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት በ24/04/2004 ዓ.ም.አዘጋጅቶ ባቀረበው ክስ ንብረትነቱ የአሁኑ 1ኛ ተጠሪ ሆኖ በአሁኑ 2ኛ ተጠሪ በመሽከርከር ላይ የነበረ የሰሌዳ ቁጥሩ 3-02598 ደ/ሕ. የሆነ ተሽከርካሪ በሾፌሩ ጥፋት  ንብረትነቱ የአድቫንስድ ኢንጂነርስ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ሆኖ በአመልካች የኢንሹራንስ ሽፋን የተሰጠውን የሰሌዳ ቁጥሩ 3-3277 የሆነ ተሽከርካሪ ገጭቶ ያደረሰበትን ጉዳት አስጠግኖ ወደ ነበረበት ለመመለስ አመልካች ያወጣውን ወጪ ብር 441,213.17 (አራት መቶ አርባ አንድ ሺህ ሁለት መቶ አስራ ሶስት ከአስራ ሰባት) 1ኛ እና 2ኛ ተጠሪዎች በአንድነትና በነጠላ እንዲከፍሉ ይወሰንለት ዘንድ የጠየቀ መሆኑን፣1ኛ እና 2ኛ ተጠሪዎች እንዲሁም ለ1ኛ ተጠሪ ተሽከርካሪ የመድን ሽፋን የሰጠው እና በተጠሪው ጠያቂነት ወደ ክርክሩ የገባው 3ኛ ተጠሪ ከመቃወሚያ በተጨማሪ በኃላፊነት እና በመጠን ረገድ ተገቢ ነው ያሉትን ክርክር ማቅረባቸውን፣ፍርድ ቤቱም የግራ ቀኙን ክርከር ከሰማ በኃላ 1ኛ እና 2ኛ ተጠሪዎችን ለክሱ ኃላፊ በማድረግ ክስ የቀረበበትን ገንዘብ በአንድነትና በነጠላ እንዲከፍሉ ውሳኔ መስጠቱን፣በዚህ ውሳኔ ቅር በመሰኘት 1ኛ እና 2ኛ ተጠሪዎች ባቀረቡት ይግባኝ ሳቢያ የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የግራ ቀኙን ክርክር ከሰማ በኃላ የተጠሪዎቹ ማስረጃ ሳይሰማ ውሳኔ መሰጠቱ እና የ3ኛ ተጠሪ ኃላፊነትም ተለይቶ አለመወሰኑ ተገቢ አለመሆኑን ገልጾ ውሳኔውን በመዝገብ ቁጥር 51395 በ30/11/2004 ዓ.ም. በመሻር ጉዳዩን በነጥብ የመለሰው መሆኑን፣ከፍተኛ ፍርድ ቤትም በተመለሰለት መሰረት የተጠሪዎችን ማስረጃ ከሰማ በኃላ የግራ ቀኙን ማስረጃ መዝኖ የሁለቱ ተሽከርካሪዎች ግጭት የደረሰው


    በአመልካች ደንበኛ ተሽከርካሪ ሾፌር ስህተት መሆኑ ተረጋግጧል ከሚል  ድምዳሜ ላይ በመድረስ ተጠሪዎቹ ለክሱ ኃላፊነት የለባቸውም ሲል በነጻ ያሰናበታቸው መሆኑን የመዝገቡ ግልባጭ ያመለክታል፡፡

     

    አመልካች አቤቱታውን ለዚህ ችሎት ያቀረበው የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት የግራ ቀኙን ክርክር ከሰማ በኃላ የከፍተኛ ፍርድ ቤት ውሳኔን በማጽናቱ ነው፡፡የሰበር አቤቱታው ተመርምሮ የስር ፍርድ ቤት እንደደረሰበት መደምደሚያ ለጉዳቱ መንሰኤ ለሆነው ጉዳት የሁለቱም ወገኖች ጥፋት የለም፣የመኪኖች ግጭት ጉዳይ ነው ከተባለ የአሁኑ አመልካች ያቀረበው የጉዳት ካሳ ክስ ሙሉ በሙሉ ውድቅ የመደረጉን አግባብነት ከፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2084(2) ድንጋጌ አንጻር ተጠሪዎች ባሉበት ለማጣራት ይቻል ዘንድ ጉዳዩ ለሰበር ክርክር እንዲቀርብ ተደርጎ አመልካች ከ1ኛ እና ከ3ኛ ተጠሪዎች ጋር የጽሁፍ ክርክር የተለዋወጡ ሲሆን ለ2ኛ ተጠሪ መጥሪያውን ተከታትሎ ማድረስ ባለመቻሉ አቤቱታውን እንደተወው ተቆጥሮ 2ኛ ተጠሪ ከክርክሩ ውጪ እንዲሆን በ15/08/2006 ዓ.ም.ትዕዛዝ ተሰጥቷል፡፡የጉዳዩ አመጣጥ እና የክርክሩ ይዘት ከላይ የተመለከተው ሲሆን እኛም አቤቱታ የቀረበበት ውሳኔ መሰረታዊ የህግ ስህተት የተፈጸመበት መሆን አለመሆኑን መርምረናል፡፡

     

    በዚህም መሠረት አመልካች አጥብቆ የሚከራከረው የግጭት አደጋው የደረሰው በ1ኛ ተጠሪ ተሽከርካሪ ሾፌር ጥፋት ምክንያት አይደለም በሚል በስር ፍርድ ቤቶች የተደረሰበት ድምዳሜ እና ይህንን ድምዳሜ መሰረት በማድረግ የተሰጠው ውሳኔ በግራ ቀኙ የቀረበውን አጠቃላይ ክርክርና ማስረጃ ያገናዘበ አይደለም፤የ1ኛ ተጠሪ ተሽከርካሪ ሾፌር ጥፋት አልነበረውም ቢባል እንኳ በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2084(1) እና (2) ድንጋጌዎች መሰረት ተጠሪዎቹ ያወጣነውን ወጪ አጋማሽ የመክፈል ግዴታ አለባቸው በማለት መሆኑን የክርክሩ ይዘት ያመለክታል፡፡እንደተባለው ሁለት ባለሞተር ተሽከርካሪዎች ሲጋጩ እያንዳንዱ ተሽከርካሪ በየራሱ አንዱ በአንዱ ላይ አደጋ እንዳደረሰ የሚቆጠር ስለመሆኑ በፍትሐብሔር ሕግ በቁጥር 2084 (1) ስር፣የእያንዳንዱ ተሽከርካሪ ባለሀብት ወይም ለአደጋው ኃላፊ የሆነው ሰው በአደጋው ምክንያት ከደረሰው ጠቅላላ ጉዳት ገሚሱን መክፈል የሚገባው ስለመሆኑ በዚሁ ሕግ በቁጥር 2084 (2) ስር እና አደጋው የደረሰው በተለይ ወይም በጠቅላላው በአንደኛው መኪና ነጂ ስህተት መሆኑ በማስረጃ በተገለጸ ጊዜ ግን ከዚህ በተጠቀሱት ሁለቱ ንዑሳን ቁጥሮች የተመለከተው ደንብ የማይጸና ስለመሆኑ በቁጥር 2084 (3) ስር ተደንግጎ ይገኛል፡፡

     

    በተያዘው ጉዳይ ክርክሩን በመጀመሪያ ደረጃ የተመለከተው የሲዳማ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት በግራ ቀኙ ወገኖች የቀረቡትን የሙያ እና የዓይን ምስክሮች ቃል እንዲሁም የትራፊክ ፕላንን ጨምሮ የቀረቡለትን ሰነዶች አገናዝቦ ከመረመረ እና ከመዘነ በኃላ ተጠሪዎቹ  ኃላፊነት የለባቸውም በማለት ውሳኔ የሰጠው አመልካች እንደሚከራከረው ጥፋቱ የ1ኛ ተጠሪ ተሽከርካሪ ሾፌር መሆኑ አልተረጋገጠም በማለት ሳይሆን ይልቁንም የግጭት አደጋው የደረሰው የአሁኑ አመልካች የመድን ሽፋን በሰጠው ተሽከርካሪ ሾፌር ስህተት ነው በማለት መሆኑን የውሳኔው ይዘት በግልጽ ያመለክታል፡፡ እንዲህ ከሆነ ደግሞ ከላይ በተጠቀሰው ቁጥር 2084 (1) እና (2) ድንጋጌዎች ስር የተመለከተው ጉዳቱን የመጋራት ደንብ ተፈጻሚነት የማይኖረው ስለመሆኑ በድንጋጌው ንዑስ ቁጥር (3) ስር በግልጽ የተመለከተ በመሆኑ አመልካች ያወጣውን ወጪ አጋማሽ ተጠሪዎቹ እንዲሸፍኑ መወሰን ነበረበት በማለት አመልካች የሚያቀርበው ክርክር ሕጋዊ መሰረት ያለው ነው ለማለት የሚቻል አይደለም፡፡


    በሌላ በኩል 1ኛ ተጠሪ በስር ፍርድ ቤት ለቀረበባቸው ክስ በሰጡት መልስ ለጉዳቱ መንስኤ ሁለቱም ተሽከርካሪዎች በመሆናቸው የየራሳችንን ጉዳት እንድንችል መደረግ ይገባዋል በማለት ተከራክረው እያለ አመልካች ያወጣውን ወጪ አጋማሽ እንዲጋሩ ሳይወሰን የቀረው አላግባብ ነው በማለት አመልካች ያቀረበውን የክርክር ነጥብ በተመለከተ 1ኛ ተጠሪ በስር ፍርድ ቤት ባቀረቡት መልስ ላይ ለጉዳቱ መንስኤ ሁለቱም ተሽከርካሪዎች በመሆናቸው የየራሳችንን ጉዳት እንድንችል መደረግ ይገባዋል በማለት የተከራከሩት በራሳቸው ተሽከርካሪ ላይም በተመሳሳይ ሁኔታ ጉዳት መድረሱን እና ለጥገና ወጪ ማውጣታቸውን ለመግለጽ እንጂ ጥፋቱ በራሳቸው ተሽከርካሪ አሽከርካሪ ነው በሚል  የቀረበባቸውን ክስ በማመን ካለመሆኑም በላይ በመልሳቸው  መጨረሻ ላይ ለክሱ ኃላፊነት የሌለባቸው መሆኑን በመግለጽ ክሱ ውድቅ እንዲደረግ የተከራከሩ መሆኑን አመልካች አቅርቦ ያያዘው የ1ኛ ተጠሪ መልስ ይዘት የሚያመለክት በመሆኑ እና ቀደም ሲል እንደተገለጸው ግጭቱ የተከሰተው አመልካች የመድን ሽፋን በሰጠው ተሽከርካሪ ሾፌር ስህተት መሆኑ በማስረጃ የተረጋጠ እስከሆነ ድረስ በቁጥር 2084(1) እና (2) ድንጋጌዎች ስር የተመለከተው ጉዳቱን የመጋራት ደንብ ተፈጻሚነት የማይኖረው በመሆኑ አመልካች በዚህ ረገድ ያቀረበው የክርክር ነጥብም ሕጋዊ ተቀባይነት ሊሰጠው የሚገባ ሆኖ አልተገኘም፡፡

    ሲጠቃለል ከላይ ከተመለከተው አጠቃላይ የክርክሩ ይዘት መገንዘብ የሚቻለው የሲዳማ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት አቤቱታ የቀረበበትን ውሳኔ የሰጠው ፍሬ ነገርን በማጣራት እና ማስረጃን በመመዘን ረገድ በሕግ በተሰጠው ስልጣን መሰረት መሆኑን ሲሆን ፍርድ ቤቱ የግራ ቀኙን ማስረጃ የመዘነበት አግባብ ደግሞ በይግባኝ ሰሚው የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤትም ተቀባይነት አግኝቷል፡፡ በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ መንግስት በአንቀጽ 80(3)(ሀ) እና በአዋጅ ቁጥር 25/88  በአንቀጽ 10 እንደተመለከተው የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ችሎት ስልጣን መሰረታዊ የሕግ ስህተት የተፈጸመበትን የመጨረሻ ውሳኔ መርምሮ በማረም የተገደበ በመሆኑ ፍሬ ነገርን የማጣራት እና ማስረጃን የመመዘን ስልጣን የተሰጣቸው የመጀመሪያ ደረጃ እና ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤቶች በዚህ ረገድ የሰጡት ውሳኔ አግባብነት በዚህ ሰበር ችሎት ሊመረመር የሚችልበት ስርዓት የለም፡፡ በሕግ ረገድ ደግሞ ውሳኔው መሰረታዊ ስሕተት የተፈጸመበት ነው ለማለት የሚቻል ሆኖ አልተገኘም፡፡በመሆኑም የሚከተለው ውሳኔ ተሰጥቷል፡፡

     ው ሳ ኔ

     

    1. የሲዳማ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመዝገብ ቁጥር 24449 በ26/07/2005 ዓ.ም. ተሰጥቶ በደቡብ ብ/ብ/ሕ/ብ/ክ/መንግስት ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በመዝገብ ቁጥር 59437 በ23/12/2005 ዓ.ም. በውሳኔ የጸናው ውሳኔ በፍትሐብሔር ስነ ስርዓት ሕግ  ቁጥር

    348(1) መሰረት ፀንቷል፡፡

    2.  እንዲያውቁት የውሳኔው ግልባጭ ለስር ፍርድ ቤቶች ይተላለፍ፡፡

    3.  የሰበር ክርክሩ ያስከተለውን ወጪና ኪሳራ ግራ ቀኙ የየራሳቸውን ይቻሉ፡፡

     

    4.  ውሳኔ ያገኘ ስለሆነ መዝገቡ ተዘግቷል፡

  • በኦሮሚያ የቤተሰብ ህግ መሠረት ባልና ሚስቱ በየግል ያገኟቸውን ንብረትም ሆነ ገንዘብ በግል ይዘው መቀጠል እንደሚችሉ  ሲደነገግ ይህ የግል የተባለው ንብረት የግል ሆኖ ሊቀጥል የሚችለው የግል ይባልልኝ ተብሎ በፍ/ቤት ሲፀድቅ ስለመሆኑ፣

    የኦሮሚያ ክልል የቤተሰብ ህግ ቁ.69/1995 አንቀፅ 741ዐ፣አንቀፅ 74/2

    የሰ/መ/ቁ. 95680

     

    መስከረም 26 ቀን 2007 ዓ/ም

     

    ዳኞች፡-አልማው ወሌ

     

    ሱልጣን አባተማም ሙስጠፋ አህመድ ተፈሪ ገብሩ ተኽሊት ይመሰል

    አመልካች፡- ወ/ሮ የሺ ተሾመ ተጠሪ፡- አቶ መስፍን ኃይሉ

    መዝገቡ ተመርምሮ የሚከተለው ፍርድ ተሰጥታል፡፡

     

     ፍ ር ድ

     

    ይህ ጉዳይ የተጀመረው በኦሮሚያ ክልል የሎሜ ወረዳ ፍ/ቤት ሲሆን የአሁን አመልካች ከሣሽ ሲሆኑ የአሁን ተጠሪ ተከሣሽ ነበሩ አመልካች ባቀረቡት ክስ፡- ከተጠሪ ጋር የነበረው ጋብቻ የፈረሰ መሆኑን በመግለፅ በጋብቻ ውስጥ የተፈራ የጋራ ንብረት ያካፍለኝ በማለት በኤጄሬ ከተማ የሚገኝ በ198 ካ.ሜ.ላይ ያረፈ ቤትና ኩሺና፣ ዲናሞ ብቻውንና የወፍጮ ዲናሞ በንግድ ባንክ ያለ ገንዘብ በ369 ካ.ሜ. ላይ 90 ቆርቆሮ የተሠራ ቤት የሞተር ቤት 2 ክፍል በልማት የተከፈለ 80,000 ብር እና የተሸጠ የወፍጮ እና ጀኔሬተር ገንዘብ(13,000) ያካፍለኝ ብላለች በ198 ካ.ሜ.ላይ  ያረፈው ቤት በ1982 ከጋብቻ በፊት (በ17/02/82) የገዛሁትን ነው፡፡በ369 ካ.ሜ. ላይ ያለው ቤት 85 ቆርቆሮ እንጂ 90 አይደለም በመንገድ ሥራ የመኖሪያ ቤት ፈርሶ የተከፈለኝ 54,000 ባገኘሁት ካሣ ከአቶ መለሰ ጫካ ከተባለ ሰው ገንዘብ ተበድሬ የሰራሁት የግል ንብረት ነው፡፡ የካሣ ገንዘቡም ብር 80,000 ሣይሆን ብር 54,000 ነው፡፡ በናፍጣ የሚሠራ ሁለት ወፍጮና ጀኔሬተር 13,000 የተገዛ ቢሆንም 11,495.55 ተጨምሮበት በ24,495.85 ወደ ኤሌክትሪክ ተቀይሮ በሥራ ላይ የሚገኝ እንጂ በጥሬ ገንዘብ የለም፡፡ በተጨማሪም የጋራችን የሆነ የላሜራ ሱቅ ሸቀጥ ግምቱ 60,000 በከሣሽ እጅ ይገኛል፡፡ የመብራት ሀይል ዕዳ (የወፍጮ) 21,000 የጋራችን ነው በመጨረሻም በ369 ካ.ሜ. ቦታ ላይ ያለውም ቤት የግሌ ነው በማለት ተከራክረዋል፡፡ ጉዳዩን ያየው ፍ/ቤትም በግራ ቀኙ የተማመኑትን ንብረት በማለፍ አከራካሪ የሆኑትን ፍሬ ነገሮች በመለየት ንብረቶችን አስመልክቶ መስተዳደሩና የአካባቢ ሽማግሌዎች  እንዲያጣሩ በማድረግ ተከሣሽ (ተጠሪ) ተበደርኩ የሚለውን 60,000 አመልካች የማታውቀውና ያልተረጋገጠ ነው፡፡ባንክ ቤት አለ የተባለው ገንዘብ በአመልካች በኩል እንዲያረጋግጡ አልተደረገም በማለት  ውድቅ ካደረገው በኃላ የተቀሩትን ንብረቶች በቀረበው ማስረጃ በማረጋገጥ እኩል እንዲካፈሉ ሲል በተለይ በ198 ካ.ሜ. ቦታ ላይ ያለው ቤት የተጠሪ በግል ገንዘባቸው ገዝተው በ369 ቦታ ላይ ቤት መስራታቸውን የካሣ ገንዘብ 54,000 ይክፈሉ ሲል በ369 ላይ ያረፈውን ቤት እኩል ይካፈሉ


    በማለት ወስኗል፡፡የይግባኙም ፍ/ቤት የግራ ቀኙን በማከራከር አጣርቶ ሲያፀናው በክልሉ ሰበርም በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ህ/ቁ.337 ተሰርዟል፡፡

     

    የአመልካች አቤቱታ የቀረበውም ይህንኑ ውሣኔ ለማሳረም ነው፡፡

     

    አመልካች ባቀረቡት የሰበር አቤቱታ በሥር ፍ/ቤት ከተጠሪ ጋር እንደባልና ሚስት ለ23 አመት ስንኖር ያፈራነውን ወፍጮ ከነ ቤቱ መኖሪያ ቤት አንድ ኩሽና አንድ ሽንት ቤት በ198 ካ.ሜ. ላይ ሰፍሮ የሚገኝ ጠጅ ቤት ፈርሶ መሬቱም ሲወሰድ የተከፈለውን ካሣ ገንዘብ 54,000 ብር በ369 ካ.ሜ ቦታ ላይ የተሰራውን ቤት አመልካች 54,000 ለተጠሪ ከፍላ ቤቱን በጋራ ትካፈል መባሉ መሠረታዊ የህግ ሥህተት የተፈፀመበት በመሆኑ ሊታረም ይገባዋል ሲሉ አመልካች ጠይቀዋል፡፡

     

    በዚህም መሠረት ይህ ችሎትም አመልካች 54,000 ብር ከፍላ በ369 ካ.ሜ.ቦታ ላይ ያረፈውን ቤት ትካፈል መባሉና በ198 ካ.ሜ ቦታ ላይ ያለው ቤት በላዩ ላይ የተተከለው ወፍጮ ቤት በግል የተሰራነው?ወይስ በጋብቻ ውስጥ? የሚለው ወደ ድርጅትነት የተለወጠው መቼ ነው?የሚለው እና ለመብራት ሀይል የተከፈለው 24,000 መቼ ነው?የሚሉት ነጥቦች እንዲጣሩ በጭብጥነት በመያዝ የግራ ቀኙ በቀረበው አቤቱታ ላይ መልስና የመልስ መልስ በመቀባበል እንዲከራከሩ አድርጓል፡፡

     

    በመሆኑም የግራ ቀኙን ክርክር አቤቱታ ከቀረበበት ውሣኔ እና ከህጉ ጋር አገናዝበን መርምረናል፡፡

     

    የጉዳዩ አመጣጥ ባጭሩ ከላይ የተጠቀሰውን ይመስላል፡፡እኛም እንዳየነው አመልካች ጋብቻ መፍረሱን ጠቅሰው የጋራ ንብረታችን ነውና ልንካፈል ይገባል የሚሉትን የንብረት ዝርዝር በማቅረብ የጠየቁ ሲሆን የሥር ወረዳ ፍ/ቤትም በዝርዝር የቀረበለትንና የዳኝነት ጥያቄ የታመነውንና ተቃውሞ በተጠሪ የቀረበበትን ነጥብ በመለየት በማስረጃ አጣርቶ ውሣኔ አሳርፎበታል፡፡

     

    እኛም በማስረጃ ረገድ ተጣርቶ ውሳኔ ያገኘውን በመቀበል በጭብጥነት በተያዙት ነጥቦችን ስናየው ተጠሪ በጋብቻ ውስጥ ከአመልካች ጋር በነበረበት ጊዜ የነበረው ወፍጮ አብረው ሲጠቀሙበት የነበረ የመብራት ኃይል የአገልግሎት ዋጋ ብር 24.000.00 መክፈላቸውን አረጋግጠው የጋራ ዕዳቸው መሆኑንና በድርሻቸው አመልካች እንዲከፍሉ ጠይቋል፡፡ የሥር ፍ/ቤትም ግራ ቀኙበጋብቻ ውስጥ እያሉ የተጠቀሙበት መሆኑን በማረጋገጥ አመልካች ቤት በነበሩበት ወቅት የቆጠረ የመብራት ዋጋ በመሆኑ ዕዳውን ሊከፈሉ ይገባል ሲል ወስኗል፡፡ እንግዲህ አመልካች ከወፍጮ ገቢ ተጠቃሚ አይደለሁም ሲሉ ባልተከራከሩበት የዕዳው ተጋሪ መሆን የለብኝም በማለት ያቀረቡት ክርክር የሕግ መሠረት የለውም በመሆኑም ይኽኛውም የውሳኔ ክፍል ባግባቡ ተጣርቶ የተወሰነ በመሆኑ ተቀብለነዋል፡፡

     

    ሁለተኛውን አከራካሪውን በ198 ካ.ሜ ይዞታ አስመልክቶ ተጠሪ ከጋብቻ በፊት ገዝቼ እያለሁ በመንገድ ምክንያት ፈርሶ ያገኜሁትን ካሳ ገንዘብ 54.000 ብር በመያዝ ከአመልካች ጋር ተጋብተው በ369 ካ.ሜ ቦታ ላይ የሰፈረውን ቦታ ሰራን ፣ ስለዚህ ንብረቶቹ የግል ንብረት ነው በማለት ሲከራከሩ አመልካች በበኩላቸው ይዞታው የተገዛውና የተሰሩት አንድ ክፍል ቤት ብቻ መሆኑንና ይህ ፈርሶ ተስፋፍቶ በ369 ካ.ሜ ቤት ተሰርቶ የጠጅ ቤት ድርጅት ስንጠቀምበት የነበረና የፈረሰ በመሆኑ ከ23 አመት በኃላ ተጠሪ የግሌ ነው ሲል መከራከሪያ ሊያደርጐት አይገባም ይላሉና እኛም ተጠሪ ተቀበልኩ የሚሉትን ገንዘብ ከጋብቻ በፊት ያገኜሁት ነው ቢሉም ከአመልካች ጋር የ369 ካ.ሜ ይዞታ ላይ ቤት በመስራት አስፋፍቶ ለረዥም ዓመታት መኖራቸው


    ያላከራከረ ነው፡፡ እንግዲህ በእነዚህ ባለፉት አመታት በግራ ቀኙ አስተዋጽኦ ቤቱ ከተገነባ በቀጣይነት የሚገኙት ገቢዎች የሉም ማለት አይቻልም፡፡ ይህ ከሆነ ደግሞ ንብረቶች መቀላቀላቸውን የሚያመለክት ነው፡፡ ተጠሪ ተጠቃሹ ገንዘብ የግሌ ነው የሚሉበት ምክንያት ከጋብቻ በፊት ያገኘሁትና በዚሁ ገንዘብ በ369 ካ.ሜ ይዞታ ላይ ቤት ሰርተናል በማለት ነው፡፡ ይሁን እንጂ የኦሮሚያ የቤተሰብ ህግ ቁ.69/1995 አንቀፅ 74/1/ መሠረት ባልና ሚስቱ በየግል ያገኟቸውን ንብረትም ሆነ ገንዘብ በግል ይዘው መቀጠል እንደሚችሉ ሲደነገግ ይህ የግል የተባለው ንብረት የግል ሆኖ ሊቀጥል የሚችለው በተጠቃሹ ህግ አንቀፅ 74/2/ ስር የግል ይባልልኝ ተብሎ በፍ/ቤት ሲፀድቅ መሆኑን በግልጽ ደንግጐታል፡፡ ይህ ደግሞ በህጉ እንደዋነኛ መስፈርት የተቀመጠ ጉዳይ ነዉ፡፡ በተያዘው ጉዳይም ተጠሪ በዚህ መልኩ ተጠቃሹን ንብረት ወይም ገንዘብ አስመዝግቤያለሁ ሲሉ ያቀረቡት ክርክር አልነበረም፡፡ ይህ ሆኖ ሣለ በስር ፍ/ቤቶች አመልካች 54,ዐዐዐ ብር በመክፈል ቤቱን ይካፈሉ የሚለውን የውሣኔ ክፍል ባለመቀበል፡፡ የተቀሩትን የውሣኔ ክፍሎች ባልነካ መልኩ በ369 ይዞታ ላይ ያረፈውን ቤት 54,ዐዐዐ አመልካች ይክፈሉና ቤቱን ይካፈሉ መባሉና በየደረጃው ባሉት ፍ/ቤቶች ያለመታረሙ መሠረታዊ የህግ ሥህተት የተፈፀመበት ሆኖ አግኝተናል፡፡ በመሆኑም ተከታዩን ውሣኔ ተሰጥቷል፡፡

     ው ሣ ኔ

    1.  የሉሜ ወረዳ ፍ/ቤት በመ.ቁ 34054 በቀን 23/07/05 የከፍተኛው ፍ/ቤት  በመ.ቁ

    33974 በቀን 06/12/2005 እና የክልሉ ሰበር ሰሚ በመ.ቁ 173245 በቀን

    28/02/2006  የሰጡት ውሣኔ ተሻሽሎ ፀንቷል፡፡

    2. አመልካች አከራካሪውን ብር 54,000.00 ለተጠሪ ሣይከፍሉ የጋራ ነው የተባለውን ቤት ሊካፈሉ ይገባል ብለናል፡፡

     

    3. የወጪ ኪሣራ የየራሳቸውን ይቻሉ፡፡ መዝገቡ ውሣኔ በማግኘቱ ተዘግቷል፡፡

     

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት::

     

     

    እ/ኢ

  • አንድ ኢንሹራንስ ኩባንያ በውል የመነጨውን ግዴታውን በወቅቱባለመወጣቱ ለተከሰተው ተጨማሪ ወጪ ተጠያቂ ሊሆን የሚችል ስለመሆኑ

    የን/ሕ/ቁ 665

    የሰ/መ/ቁ. 95751

    መስከረም 27 ቀን 2007 ዓ.ም


     

     ፍ ርድ

    ይህ ጉዳይ የተጀመረው በኦሮሚያ ክልል የአዳማ ወረዳ ፍ/ቤት ሲሆን የአሁኑ አመልካች ተከሳሽ ሲሆኑ የአሁኑ 1ኛ ተጠሪ ከሳሽ 2ኛ ተጠሪ ጣልቃ ገብ ነበሩ፡፡ ከሳሽ በቀረቡት ክስ ባለቤቴ ሟች ወንደሰን ከፍያለው በተከሳሽ መኪና የታርጋ ቁጥሩ 323459 በሆነው ላይ በአሽከርካሪነት ተቀጥሮ በወር 1000 እየተከፈለው ሲሰራ በደረሰው የመኪና አደጋ ህይወቱ አልፏል በአዋጅ 377/96 አንቀጽ 110/1/ ለከሳሽ እና የሟች ልጅ ለሆነው (ዳግም ወንድወሰን) ጭምር በድርጅታችን 60,000 (ስልሣ ሺ) ይከፈለኝ በተጨማሪም የጠበቃ አበል 10% እና ውጪ ኪሣራ ይከፈለኝ በማለት ጠይቀዋል፡፡ አመልካችም በሰጡት መልስ ተጠቃሹ መኪና የኢንሹራንስ ሽፋን ያለው መሆኑን በመግለፅ ግሎባል ኢንሹራንስ ጣልቃ ገብቶ እንዲከራከር በጠየቁት መሠረት ይኸው አካል ወደ ክርክሩ በመግባት እስከ 60,000 ብር ድረስ ሽፋን መስጠቱን በመጥቀስ ከውላቸው ውጭ የመክፈል ኃላፊነት የሌለበት መሆኑን ገልፆ ተከራክሯል፡፡

    ጉዳዩን ያየው የወረዳው ፍ/ቤት ግሎባል ኢንሹራንስ በሰጠው ሽፋን ልክ ይክፈል፡፡ በወቅቱ ባለመክፈሉ ምክንያት ለደረሰው ወጪና ኪሣራ እና የጠበቃ አበል ይክፈል በማለት ወሰነ፡፡ የይግባኝ ሰሚው ፍ/ቤትም ለደረሰው ጉዳት ይከፈል የተባለውን 60,000 በማጽናት የጠበቃ አበል፣ የወጪና ክሣራ አስመልክቶ ሊከፍል አይገባም በማለት አሻሽሎ አፀና በመጨረሻም 1ኛ ተጠሪ ለክልሉ ሰበር ሰሚ ቅሬታዋን በማቅረብ የሰበር ሰሚውም ሽፋን ከተሰጠው በላይ የአሁን 2ኛ ተጠሪ /ግሎባል/ ሊከፍል አይገባም ከሽፋኑ በላይ የሆነውን የአሁን አመልካች ተተክተው ሊከፍሉ ይገባል ሲል አሻሽሎ አፅንቷል፡፡

    የአመልካች የሰበር አቤቱታም ይህንኑ የሰበር ውሣኔ ለማሳረም ነው፡፡

    አመልካች ባቀረቡት የሰበር አቤቱታ 2ኛ ተጠሪ (ግሎባል ኢንሹራንስ) ለደረሰ ጉዳት ተተክቶ ሊከፍልእና በውላችን መሠረት ግዴታውን ለመወጣት ተስማምቷል (ውል ገብቷል) ይሁን እንጂ 2ኛ ተጠሪ በፍርድ ካልተገደድኩ በማለት በወቅቱ ግዴታውን ባለመወጣቱ ለቀረበዉ ክስ ሽፋንከሰጠው በላይ ልገደድ አይገባውም ተብሎ አመልካች የወጪ ኪሣራና የጠበቃ አበል ትክፈል ተብሎ መወሰኑ የህግ ስህተት የተፈፀመበት ስለሆነ ሊታረም ይገባዋል በማለት ጠይቀዋል፡፡ በመሆኑም የግራ ቀኙ ለአመልካች አቤቱታ መልስ በፅሑፍ በማቅረብ ክርክራቸውን አድርገዋል፡፡


    በዚሁ መሠረት 2ኛ ተጠሪ ለአመልካች ከሰጠው ሽፋን በላይ የወጪ ኪሣራ እና የጠበቃ አበል ሊከፍል አይገባም ተብሎ አመልካች እንዲከፍሉ የመወሰኑን አግባብነት በጭብጥነት ተይዞ ቀርቧል፡፡

    ይህ ችሎትም የግራ ቀኙን ክርክር አቤቱታ ከቀረበበት ውሣኔ እና አግባብነት ካለው ህግ አኳያ መርምረናል፡፡

    የጉዳዩ አመጣጥ ባጭሩ ከላይ የተጠቀሰውን ይመስላል፡፡ እንግዲህ ለጉዳዩ መነሻ የሆነው የሥር ከሳሽ የአሁን 1ኛ ተጠሪ የሆኑት በባለቤታቸው ላይ በደረሰው የሞት አደጋ ምክንያት የአዋጅ 377/96 አንቀጽ 110(2) ሀ,ለ መሠረት 60,000 ብር እንድከፍላቸው በአሁኑ አመልካች ላይ ክስ በማቅረባቸው ምክንያት የአሁን 2ኛ ተጠሪ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ህግ ቁ. 43 መሠረት ወደ ክርክሩ እንድገባ ተደርጐ ለደንበኛው በሰጠው የኢንሹራንስ ሽፋን መሠረት 60,00ዐ ብር እና የጠበቃ አበል 10% እና የወጪ ኪሣራ 1000 ብር እንዲከፍል በመወሰኑና በየደረጃው ባሉት የክልሉ ፍ/ቤቶች እያዩት የክልሉ ሰበር ሰሚ ደረሶ ግሎባል ኢንሹራንስ ከሰጠው የኢንሹራንስ ሽፋን በላይ የጠበቃ እና የወጪ ኪሣራ ልከፍል አይገባም የአሁን አመልካች ኢንሹራንስ ከከፈለው በላይ ያለውን 8000 ብር ይክፈሉ በመባሉ ነው፡፡ በዚህ ጉዳይ የክልሉ ሰበር አመልካች ሊከፍሉ ይገባል ሲል የሠጠው የአሁን 2ኛ ተጠሪ (ግሎባል ኢንሹራንስ የንግድ ህጉን አንቀጽ 665(2) መሠረት ግዴታው ከውላችን ላይ ካለው የሽፋን መጠን ልበልጥ አይገባውም የሚለውን ክርክር በመቀበል መሆኑ ግልፅ ነው፡፡ እንግዲህ የግራ ቀኙ መብትና ግዴታ የሚመነጨው በመሀከላቸው ከተቋቋመው ውል መሆኑ ይህ ችሎትም የሚቀበለው ጉዳይ ነው፡፡

    ይሁን እንጂ በተያዘው ጉዳይ የአመልካች ደንበኛ (ግሎባል ኢንሹራንስ) በአመልካች መኪና በደረሰው የሞት አደጋ በወቅቱ አግባብነት ያለውን ክፍያ ባለመፈፀሙ ምክንያት የአሁን 1ኛ ተጠሪ የመኪናውን ባለቤት የሆኑትን አመልካች ለመክሰስ ተገደዋል፡፡ ስለሆነም ለተለያዩ (ላልታሰበ) ወጪ መዳረጋቸው ያልተካደና የተረጋገጠ ፍሬ ነገር ነው፡፡ በመሆኑም ግሎባል ኢንሹራንስ ምንም እንኳ የሰጠው የኢንሹራንስ ሽፋን የተገለፀ ቢሆንም ከውል የመነጨውን ግዴታውን በወቅቱ ባለመወጣቱ ለተከሰተው ተጨማሪ ወጪ የአሁን አመልካች የሚቀጡበት የህግ አግባብ አይኖርም፡፡ በዚህ ሁሉ ምከንያት የሞት ካሣውን የገንዘብ መጠን 60,000 ብር ላይ የጠበቃ እና የወጪ ኪሣራውን ግሎባል ኢንሹራንስ ሊከፍል የሚገባው ሆኖ አግኝተነዋል፡፡ ባጠቃላይ የክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት የሥር ውሳኔዎችን በማሻሻል ከ60,000 ብር በላይ የተጠየቀውን ተጨማሪ ወጪ አመልካች ሊከፍሉ ይገባል ማለቱ መሠረታዊ የህግ ስህተት የተፈፀመበት ነው በማለት ተከታዩን ውሣኔ ሰጥተናል፡፡

     ው ሳኔ

    1. የአዳማ ወረዳ ፍ/ቤት በመ/ቁ.63103 በቀን 27/3/05 የልዩ ዞኑ ከፍተኛ ፍ/ቤት በመ/ቁ.15437 በ29/08/05 እና የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሠበር ሰሚ ችሎት በመ/ቁ. 164154 በቀን 23/03/2006 የሰጡት ውሣኔዎች ተሻሽሎ ፀንቷል፡፡

    2. የጠበቃ አበል እና የወጪ ኪሣራን ግሎባል ኢንሹራንስ /8000/ብር ለ 1ኛ ተጠሪ ሊከፍል ይገባል ብለናል፡፡

    የሰበሩን ክርክር አስመልክቶ ግራ ቀኙ የወጪ ኪሣራ ይቻቻሉ፡፡ መዝገቡ ተዘግቷል፡፡

     

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡

  • Family law

    Irregular union

    Condition for existence of irregular union

    Federal Family Code art. 97, 98, 99 and 106(2)

    ጋብቻ ሳይኖር እንደባልና ሚስት ለሚኖሩ ሰዎች የሚፈለገው ማስረጃ ወንዱና ሴትየዋ የተጋቡ ሰዎችን ሁኔታ ሲያሳዩና ቤተዘመዶቻቸውና ማህበረሠቡ እንደተጋቢ ሰዎች የሚኖሩ ናቸው ብለው የሚገምቷቸው መሆን ያለባቸው ስለመሆኑ፣ 

    በአንድ ወንድና ሴት መካከል ለተወሰነ ጊዜ የፍቅር ግንኙነት መኖሩ ብቻ እንደባልና ሚስት የሚኖሩ ናቸው ሊያስብል የማይችል ስለመሆኑ ፣

    አዋጅ ቁጥር 213/92 አንቀፅ 97፣98፣99 እና 106/2/

    96853

  • civil procedure

    Evidence law

    temporary injunction

    attachment of property before judgment

    priority of creditors

    በተያዘ ወይም በተከበረ ንብረት ላይ መብት አለን ብለው ተቃውሞ የሚያቀርቡ ሠዎች በንብረቱ ላይ ያላቸውን የቀዳሚነት መብት ወይም ባለይዞታነት ለማረጋገጥ በጽሁፍ ማስረጃ ብቻ ሳይወሠኑ ሌላ ማስረጃም ሊያቀርቡ የሚችሉ ስለመሆኑ፣

     

    የፍ/ስ/ስ/ህ/ቁ.418/3/ እና የፍ/ህ/ቁ 1193/1//2/

     

    የሰ/መ/ቁ 97094 ቀን 08/03/2ዐዐ7 ዓ.ም

    ዳኞች፡- አልማው ወሌ

     

    ዓሊ መሐመድ ሱልጣን አባተማም ሙስጠፋ አህመድ ተኽሊት ይመሰል

    አመልካች፡- ወ/ሮ አስቴር አምባው - ቀረቡ ተጠሪዎች፡- 1. አቶ አበባው ክፍሌ የቀረበ የለም

    2. ያሬድ አለማየሁ የቀረበ የለም መዝገቡ ተመርምሮ የሚከተለው ፍርድ ተሰጥቷል፡፡

     ፍ ር ድ

     

    ይህ ጉዳይ የተጀመረው በከፋ ዞን የቦንጋ ከተማ የመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት ሲሆን የአሁን አመልካች በስር ፍ/ቤት በፍ/ሥ/ሥ/ህ/ቁ 418 በአፈፃፀሙ ጉዳይ ጣልቃ የገቡ ሲሆኑ 1ኛ ተጠሪ የአፈፃፀም ከሳሽ 2ኛ ተጠሪ የአፈፃፀም ተከሳሽ ነበሩ የአፈፃፀም ከሳሽ /የአሁንተጠሪ/ ለአፈፃፀም ይውሉ ዘንድ 1. የልብስ ስፌት ማሽን፣ ኮንትሮል ብፌ፣ የሴቶች ፀጉር ቤት ካስክ፣ ስሶት የፀጉር ማሽን፣ የፀጉር ቤት መስታወት፣ የመቀመጫ ወንበር፣ ባለ 21 ኢንች ቴሌቪዥን እና አራት የሶፋ ወንበሮች ተሽጦ እዳው ይከፈለኝ በማለት ጠይቀዋል፡፡ ፍ/ቤቱም የተጠቀሱት ንብረቶች ተገመተው እንዲቀርቡለት ትዕዛዝ በመስጠቱ ምክንያት የአሁን አመልካች ንብረቶች የግሌ ናቸው በማለት ሊፈፀም አይገባም በማለት በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ቁ. 418 መሰረት በመቅረቧ ፍ/ቤቱም አመልካች ተጠቃሹ ንብረቶች የራሳቸው ለመሆኑ ያቀረቡት የፅሁፍ ሰነድ የለም፣ በሰው ምስክር አስረዳለሁ ያሉትን ክርክር በስነ ስርዓት ህጉ 418/3/ መሰረት ተቀባይነት የለውም በማለት ጥያቄውን ውድቅ አድርጐታል፡፡ በየደረጃው ያሉትም የክፍሉ ፍ/ቤቶችም ይህንኑ ተቀብለውታል፡፡

     

    የአመልካች አቤቱታም የቀረበው ይህንኑ ውሳኔ ለማስቀየር ነው፡፡አመልካች ባቀረቡት የሰበር አቤቱታ ቅሬታቸውን ሲገልፁ 2ኛ ተጠሪ በእኔ ድርጅት ተቀጥሮ የሚሠራ ነው፤ ተጠቃሾቹ ንብረቶች የግሌ እና መጠቀሚያዎቼ ናቸው ብዩ ብቀርብምበሰው ምስክር ማስረዳት አይቻልም፤የፅሑፍ ሰነድ ካልሆነ በቀር በማለት ላቀርብ እችላለሁ ያልኩትን ሰነድ ሳይቀበለኝ ጥያቄየን ውድቅ ማድረጉ መሰረታዊ የህግ ስህተት የተፈፀመበት በመሆኑ ሊታረምልኝ ይገባዋል ሲሉ አመልክተዋል፡፡

     

    በዚህም መሰረት እኛም አመልካች በሰውና በሰነድ ንብረቶቹ የእኔ መሆናቸውን ላስረዳ እያሉ በሰው ማስረጃ ብቻ ማሰረዳት አይቻልም ተብሎ የመወሰኑን አግባብነት በጭብጥነት በመያዝ


    የግራ ቀኙ በቀረበው አቤቱታ ላይ መልስና የመልስ መልስ በፅሑፍ እንዲቀባበሉ ተደርጐ ተከራክረዋል፡፡

     

    1ኛ ተጠሪ የሚሉት 2ኛ ተጠሪ የአመልካች ባል ናቸው በአካሌ ላይ ጉዳት አድርሶብኝ እንዲፈፀምልኝ ያቀረብኩትን ንብረቶች አመልካች ለማስቀረት በማሰብ ነው የእኔ ንብረቶች ናቸው የሚሉት የራሳቸው ለመሆኑ በሰነድ ማቅረብ ባለመቻላቸው እና በሰው ማስረጃ አስረዳለሁ ማለታቸው ውድቅ መደረጉ የሚነቀፍ አይደለም በማለት ነው፡፡የሚከራከሩት አመልካች በበኩላቸው በ2ኛ ተጠሪ ፍቃድ እኔ ንብረቶቹን አቀርቤ ቀጥሬያቸው ነው የሚሰሩት እንጂ የጋብቻ ግንኙነት የለኝም በስር ፍ/ቤት በሰነድና በሰው ማስረጃ ላስረዳ ብዬ እያመለከትኩ ይህ ታልፎ በሰው ማስረጃ ማስረዳት አይቻልም ተብሎ መወሰኑ ንብረቴን የሚያሳጣኝ ውሳኔ በመሆኑ ሊሻር ይገባዋል ሲሉ ክርክራቸውን አጠናክረዋል፡፡

     

    በአጠቃላይ የክርክሩ አመጣጥ ባጭሩ ከላይ የተጠቀሱትን ይመስላል፡፡ በመሆኑም ይህ ችሎት የግራ ቀኙን ክርክር አቤቱታ ከቀረበበት ውሳኔ እና አግባብነት ካላቸው የህግ ድንጋጌዎች አኳያ መርምሯል፡፡

     

    እንግዲህ አመልካች ተጠቃሾቹ ንብረቶች የእኔ ለመሆናቸው “ሰነድ” ማቅረብም እችላለሁ ስል እንዳቀርብ ከተፈቀደልኝ በኋላ ነው፡፡ ይህ ታልፎ በፅሁፍ ማስረጃ ብቻ ነው እንጂ በሰው ማስረጃ ማስረዳት አትችይም የተባልኩት ነው የሚሉት፡፡ በመሰረቱ የፍ/ብ/ህ/ሥ/ሥ/ህ/ቁ. 418 ድንጋጌ አስፈላጊነት የክርክሩ አካል ያልሆኑና ፍርድ ያላረፈባቸው የ3ኛ ወገን ንብረት ሳይረጋገጥ የፍርዱ ማስፈፀሚያነት እንዳይውሉ ለመከላከልና ባንጻሩ ፍርዱን የመፈፀም ለማስተጓጉል (እንዳይፈፀም ለሚቀርቡት በቂ ላልሆኑ አቤቱታዎችም (መቃወሚያ) እልባት የሚሰጥ ነው፡፡ በመሆኑም በተያዙት ንብረቶች ላይ መብት አለኝ የሚል ወገን የሚያቀርበውን መቃወሚያና አቤቱታ ተቀብሎ መመርመር እንዳለበት የተጠቀሰው ድንጋጌም በግልፅ ያሰፈረውነው፡፡ ይህ ከሆነ የዚሁ አንቀጽ 418(3) የአራተኛው ቅጂ ባለይዞታነትን ለማስረዳት የፅሁፍ ማስረጃ መቅረብ እንዳለበትየሚደነግግ ቢሆንም የእንግሊዘኛው ቅጂ የስነ- ስርዓት ህጉደግሞ ይህንኑ  አንቀጽ ሲገልጽ The Claimant or 0bjector Shall adduce evidence to Show that and the date of the attachment he had Some interest in or was possessed of the property attached ይላል፡፡ እንግዲህ ከዚህኛው የእንግሊዘኛ ቅጂ የምንረዳው “ማስረጃ በማቅረብ ለአፈጻጸም የቀረበውን ንብረት ማስረዳት እንደሚቻል የሚገልጽ ነው፡፡ የአማርኛው ቅጂም ቢሆን ከፍ/ህ/ቁ/1193 (1) እና (2) ድንጋጌዎች ጋር ተደምሮ ሲታይ ሌላውን የማስረጃ አይነት በግልጽ እንዳይቀርብ የከለከለው ሆኖ አይታይም፡፡በመሆኑም የስር ፍ/ቤቶች አመልካች አካራካሪውን የሚንቀሳቀስ ንብረት በሰው ማስረጃ ሊያስረዱ አይችሉም ሲሉ ያደረሱበትን ድምዳሜ የፍ/ብ/ስ/ስ/ሕ/ቁ. 418 ድንጋጌ መሰረታዊ አላማና የሚንቀሳቀሱ ግዙፍ ሀብቶችን ባለ ሃብትነት ለማስረዳት የሚጠቅሰውን የማስረጃ ዓይነት ያገናዘበ ሁኖ አልተገኘም በመጨረሻ በስር ፍ/ቤት አመልካች ያቀረቡትን የሰው ማስረጃ ከወዲሁ ሳይሰማ ሰነድ አልቀረበም በማለት ጥያቄያቸውን ውድቅ በማድረጉ የማስረጃ አቀራረብ ስርዓትን ያልተከተለ በመሆኑ መሰረታዊ የህግ ስህተት የተፈጸመበት ሆኖ አግኘተነዋል ፡፡ በመሆኑም ተከታዩ ተወስኗል፡፡


     

     

     ው ሳ ኔ

     

    1. የከፋ ዞን ቦንጋ ከተማ መጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት በመ/ቁ ዐ64ዐ3 በቀን 11/ዐ4/2ዐዐ6 ዓ.ም የሰጠው የዞኑ ከፍተኛ ፍ/ቤት በመ/ቁ 1ዐዐ82 በ3ዐ/ዐ4/2ዐዐ6 ዓ.ም እና የክልሉ ጠቅላይ ፍ/ቤት በመ/ቁ ዐ1555 በቀን ዐ9/ዐ5/2ዐዐ6 ዓ.ም የተሰጡት ውሳኔዎች በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ 348/1/መሰረት ተሽረዋል፡፡

    2. የቦንጋ ከተማ መጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት በጉዳዩ የቀረበውን  የሰው  ማስረጃ በመስማት አግባብነት ያላቸውን ሰነዶች በመመርመር ተገቢነት ያለውን ውሳኔ እንዲሰጥ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ 343/1/ መሰረት መዝገቡን መልሰን ልከናል፡፡ ይፃፍ፡፡

    3.  የወጪ ኪሳራ ግራ ቀኙ ይቻቻሉ፡፡

    መዝገቡ ተዘግቷል፤ ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ፡፡

     

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት::

  • ከአንድ በላይ ሰዎች በወንጀል ተሳታፊ በሚሆኑበት ጊዜ ለወንጀሉ ድርጊት ኃላፊ ናቸው የተባሉት ወንጀለኞች የእያንዳንዳቸውን ተሳትፎ ህጉ ባስቀመጠው የማስረጃ መለኪያ መሰረት መለየት ያለበት ስለመሆኑ-

    የወ/መ/ስ/ስ/ህ/ቁ 141፣ የወ/ህ/ቁ. 40

    የሰ/መ/ቁ 97203

     


     

    ዳኞች፡-አልማው ወሌ ሡልጣን አባተማም መኮንን ገ/ሕይወት

    ሙስጠፋ አህመድ ተኽሊት ይመሰል


    መስከረም 30 ቀን 2007


     

    አመልካች፡-1.አቶ ታምራት ደምሴ

    2.አቶ በሪሁን ደምሴ       የቀረበ የለም

    3.አቶ ታደለ ሽቱ

    ተጠሪ፡-የቤንሻንጉል ጉምዝ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ፍትህ ቢሮ ዐቃቤ ሕግ - የቀረበ የለም፡፡ መዝገቡ ተመርምሮ ተከታዩ ፍርድ ተሰጥቷል፡፡

     

     ፍ  ር ድ

     

    ጉዳዩ የወንጀል ሲሆን ክርክሩ የተጀመረው በመተከል ዞን ከፍተኛ ፍ/ቤት ነው፡፡ በዚህ ፍ/ቤት የአሁኑ ተጠሪ በአሁኑ አመልካቾች እና አቶ አለኽኝ ጋሻው በተባሉት ግለሰብ ላይ የመሰረተው ክስ:- በ1996 ዓ.ም በወጣው የኢ.ፌ.ዲ.ሪፐብሊክ የወንጀል ሕግ አንቀጽ 32(1)(ሀ) እና 539/1/ሀ/ ስር የተመለከተውን በመተላለፍ ታህሳስ 29 ቀን 2002 ዓ.ም በግምት ከምሽቱ 3፡00 በሚሆንበት ጊዜ ግልገል በለስ ከተማ ከወ/ሮ አለምፀሐይ ጌታሁን ሻይ ቤት አረቄ እየጠጡ በፈጠሩት ፀብ ለምንድን ነው የሰደብከን? በማለት የአሁኑ 1ኛ፣2ኛ አመልካቾች እና የስር 3ኛ ተከሳሽ የነበሩት አቶ አለኸኝ ሟች ኤርሚያስ ኃይሉን ሊደበድቡት ሲሉ በገላጋይ ከቤት ከወጡ በኋላ ከስር ሶስተኛ ተከሳሽ ጋር በመሆን ተከታትለው በመሄድ ኤርሚያስ ኃይሉን በአንድ ላይ ተባብረው በዱላና በድንጋይ ግንባሩንና መላ ሰውነቱን ደብድበው በግፍ ገድለዋል የሚል ነው፡፡አመልካቾች ክሱ ተነቦላቸው እንዲረዱት ከተደረገ በኋላ ስለእምነት ክህደት ቃል ሲጠየቁ በክሱ ላይ ተቃውሞ የሌላቸው መሆኑን ገልፀው የድርጊቱ አፈጻጸሙን በተመለከተም ክደዋል፡፡ ተጠሪ በበኩሉ አሉኝ ያላቸውን ማስረጃዎችን ያሰማ ሲሆን የስር ፍ/ቤትም የዐቃቤ ሕግ ማስረጃዎችን መርምሮ አመልካቾች ድርጊቱን መፈፀማቸው በበቂ ሁኔታ ተረጋግጧል በሚል ምክንያት የአሁኑ አመልካቾችን እንዲከላከሉ ብይን ሰጥቶ የስር 3ኛ ተከሳሽ የነበሩትን ግለሰብ ግን በነፃ አሰናብቷል፡፡በዚህ ብይን መሰረትም አመልካቾች የመከላከያ ማስረጃዎችን አቅርበው አሰምተዋል፡፡

     

    ጉዳዩን በመጀመሪያ ደረጃ የተመለከተው የዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤትም ጉዳዩን መርምሮ የአመልካቾችን የመከላከያ ማስረጃነት ቃል ክብደት የማይሰጠው ነው በማለት ውድቅ ከአደረገ በኃላ አመልካቾችን በዓቃቤ ሕጉ በኩል ተጠቅሶ በቀረበው ድንጋጌ ስር ጥፋተኛ በማድረግ እያንዳንዳቸውን በ17 (አስራ ሰባት አመት) ጽኑ እስራት እንዲቀጡ ሲል ወስኗል፡፡ከዚህም በኃላ አመልካች በጥፋተኝነትና በቅጣት ውሣኔው ላይ ቅር በመሰኘት ለክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ይግባኛቸውን፣የሰበር አቤቱታቸውን ደግሞ ለክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት ቢያቀርቡም ተቀባይነት አላገኙም፡፡ የአሁኑ የሰበር አቤቱታ የቀረበውም ይህንኑ  ውሣኔ በመቃወም ለማስቀየር ነው፡፡


    አመልካቾች ህዳር 23 ቀን 2004 ዓ.ም በተፃፈ ሁለት ገጽ የሰበር አቤቱታ በበታች ፍርድ ቤቶች ውሣኔ ላይ መሠረታዊ የሆነ የሕግ ስህተት ተፈጽሟል የሚሉባቸውን ምክንያቶች ዘርዝረው አቅርበዋል፡፡ ይዘቱንም ባጭሩ፡- የበታች ፍርድ ቤቶች በአመልካቾች ላይ የሰጡት የጥፋተኛነት ውሣኔ አግባብነት የሌለውን ማስረጃ መሰረት ያደረገ ከመሆኑም በላይ ማስረጃውም ተገቢውን የማስረጃ ምዘና ስርዓት ተከትሎ ያልተመዘነ መሆኑን፣አድራጎቱ በአመልካቾች ተፈፅሟል ከተባለም አግባብነት ያለው ድንጋጌ ተራ በሆነ የሰው መግደል ወንጀል የሚሸፍን ነው እንጂ በግፍ ሰው መግደልን በሚሸፍነው ድንጋጌ ስር የሚወድቅ ያለመሆኑን፣ እንዲሁም የቅጣት ውሳኔውም የአመልካቾችን የእድሜ ሁኔታ ግንዛቤ ውስጥ ያላስገባና የበዛ መሆኑን በመዘርዝር ውሣኔው ሊለወጥ ይገባል በማለት ዳኝነት መጠየቃቸውን የሚያሣይ ነው፡፡አቤቱታቸው ተመርምሮም አመልካቾች ለወንጀል ድርጊቱ ተጠያቂ የመደረጋቸውን አግባብነት ከወ/ሕ/አንቀጽ 23(2) ድንጋጌ አንፃር ለመመርመር ሲባል ለዚህ ችሎት እንዲቀርብ የተደረገ ሲሆን ተጠሪ ጥሪ ተደርጎለት ባለመቅረቡ በፅሑፍ መልስ የመስጠት መብቱ ታልፏል፡፡

     

    የጉዳዩ አመጣጥ አጠር አጠር ባለመልኩ ከላይ የተገለፀው ሲሆን ይህ ችሎትም የግራ ቀኙን ክርክር ለሰበር አቤቱታው መነሻ ከሆነው ውሣኔ እና አግባብነት ካላቸው ድንጋጌዎች ጋር በማገናዘብ ጉዳዩን በሚከተለው መልኩ መርምሮታል፡፡እንደመረመረውም የዚህን ችሎት ምላሽ የሚያስፈልጉት አበይት ነጥቦች፡-

     

    1. ከአመልካቾች ውስጥ ለሟች ሕልፈት ተጠያቂነት ያለበት የትኛው ነው?፣

     

    2. ተጠያቂነት አለበት ሊባል የሚችለው አመልካች አለ ከተባለ አድራጎቱ የሚሸፈነው በየትኛው አንቀፅ ስር ነው? እና ቅጣቱስ ስንት ሊሆን ይገባል የሚሉት ሁነው ተገኝተዋል፡፡

     

     የ መጀ መሪያ ውን ጭብጥ በተመ ለከተ፡ -ከክርክሩ ሂደት መገንዘብ የተቻለው በዓቃቤ ሕግ የክስ ማመልከቻ ለህልፈት ተዳርገዋል የተባሉት ግለሰብ ለህልፈት የተዳረጉት በአመልካቾችና በስር 3ኛ ተከሳሽ በነበሩት ግለሰብ በግብረአበርነት በተፈፀመባቸው አድራጎት መሆኑን የተጠሪ ክስ የሚገልጸው ጉዳይ ሲሆን ተጠሪ በሟች ላይ ለህልፈተ ሕይወት መድረስ ምክንያት የሆነውን አድራጎት የፈፀሙት አመልካቾች መሆናቸውን ለማስረዳት አሉኝ ያላቸውን ማስረጃዎችን ማቅረቡን የውሳኔው ግልባጭ የሚያስገነዝብ መሆኑን ነው፡፡በዚህ ረገድ የተሰሙት ምስክሮች የሰጡት የምስክርነት ቃል ሲታይም፡-1ኛው ምስክር ድርጊቱ የተፈፀመው በአቃቤ ሕግ የክስ ማመልከቻ በተጠቀሰው ጊዜና ቦታ መሆኑን ጠቅሰው አመልካቾችና ሟች የምስክሩ ጎረቤት በሆኑት በወ/ሮ አለምፀሐይ ጌታሁን ሻይ ቤት ሲጠጡ እንደቆዩና ጎረቤታቸው ወደ ምስክሩ ቤት እራት ሊበሉ ሂደው አመልካቾችና ሟቹ እንደተጣሉና ምስክሩ እንዲያገላግሏቸው ለምስክሩ ሲነግሯቸው ምስክሩም ወደ መጠጥ ቤት ሂደው ሲመለከቱ ሁሉም ቁጭ ብለው እንደአገኟቸው፣ከዚያ በኋላ ሟቹ ቀድሞ ከቤቱ ሲወጣ አለኽኝ ጋሻው የተባለው የስር 3ኛ ተከሳሽ ሟችን ተከታትሎ መውጣቱንና ከአምስት ደቂቃ ቆይታ በኋላም የአሁኑ አመልካቾች ተከታትለው እንደወጡ፣በወቅቱ በመጠጥ ቤት ውስጥ ሟቹና የስር ተከሳሾች ሲጨቃጨቁ ምስክሩ መስማታቸውን፣ተከሳሾች ከቤት ከወጡ በኋላ ምስክሩ ወደ ቤታቸው ተመልሰው ሂደው ከተኙ በኃላ ከምሽቱ 7፡00 አከባቢ ጩኸት እንደሰሙና በበነጋታውም 2፡00 አከባቢ ሟቹ ሞተ ሲባል መስማታቸውን መስክረዋል፡፡አለምጸሐይ ጌታሁን የተባሉት 2ኛ የዓቃቤ ሕግ ምስክር በበኩላቸው ድርጊቱ የተፈፀመው በዐቃቤ ሕግ የክስ ማመልከቻ በተጠቀሰው ጊዜና ቦታ መሆኑን ጠቅሰው በሻይ ቤታቸው ሶስት  ሰዎች ቀድመው  ገብተው  በብርሌ አረቄ  ገዝተዋቸው  እየጠጡ  እያለ


    የእንግሊዝኛ ቋንቋ ማውራት እንደጀመሩና ከቆይታ በኋላ ስድብ ሲጀምሩ ምስክሯ ነገሩ ጠብ መሆኑን በመረዳት ጎረቤታቸው ለሆኑት ለዓቃቤ ህግ አንደኛ ምስክር ከሻይ ቤታቸው ወጥተው በመሄድ ስለጉዳዩ እንደነገሯቸውና ጎረቤታቸውም ወደ ምስክሯ ቤት መጥተው በመጠጥ ቤት የነበሩትን አመልካቾችን "ሌላ ሰው ለምን ትረብሻላችሁ?" በማለት ሲናገሯቸው ከመጠጥ ቤት የነበሩት ሰዎች ተከታትለው እንደወጡና ምስክሯም ከዚህ በኋላ የመጠጥ ቤቱን በር ዘግተው የተኙ መሆናቸውን መስክረዋል፡፡ሦስተኛው የዐቃቤ ሕግ ምስክርም የአቃቤ ሕግ 1ኛ ምስክር ባለቤት መሆናቸውን ጠቅሰው የሰጡት የምስክርነት ቃል በይዘቱ ከ1ኛው ምስክር ጋር ተመሳሳይነት ያለው ነው፡፡4ኛው የአቃቤ ሕግ ምስክር ደግሞ ድርጊቱ ተፈፀመ በተባለበት ጊዜ በግልገል በለስ ከተማ 02 ቀበሌ ግብርና ፅ/ቤት ወደታች ባላቸው የግል ሻይ ቤት የሥር 3ኛ ተከሳሽ አለኽኝ እና ኤርምያስ የተባሉት ሰዎች ሂደው የሚጠጣ ሻይ ከአዘዙ እና ሻሂውን ከጠጡ በኋላ ከምሽቱ 3፡00 አከባቢ ከቤት ወጥተው እንደሄዱ፣ከምሽቱ 4፡30 ሲሆን ደግሞ አለኽኝ የተባለው ተከሳሽ ተመልሶ ወደ ሻሂ ቤታቸው ገብቶ ጅን አረቄ እንዲሰጠው ሲጠይቃቸው ምስክሯ የለኝም የሚል ምላሽ ሲሰጡት ይሄው ግለሰብ ሻሂ ጠጥቶ ለብቻው ተመልሶ መሄዱን መስክረዋል፡፡5ኛው የአቃቤ ህግ ምስክር በሰጡት የምስክርነት ቃል፡-በዓቃቤ ሕግ የክስ ማመልከቻ በተጠቀሰው ጊዜና ቦታ እንዳልነበሩ፣ድርጊቱ ከተፈፀመ በኃላ የወንጀል ክትትሉን እንደጀመሩ፣ከወንጀሉ መፈፀም በኃላ የደምሴ ልጆች መሰወራቸውን፣አባታቸውም ከሁለት ልጆቻቸው ጋር ታስረው እንደነበር፣አቶ ደምሴ የተባሉት ግለሰብም "አይ እኔን ከእስር ቤት ፍቱኝና ሌሎች ልጆች ስላሉ አፈላልጌ ላምጣ!" ብለው ለፖሊስ አቤቱታ እንደአቀረቡ፣ከዚያም ሰውየው ፖሊስ ይሰጠኝ በማለታቸው ፖሊስና ልዩ ኃይል ተሰጥቷቸው ታምራት የተባለው ልጃቸው ከስራ ቦታ ተይዞ እንደመጣ፣በወቅቱ "ድርጊቱን ከወንድሜ በሪሁን ጋር የፈፀምኩት እኔ ነኝ፣ ታደለና አለኽኝም በድብደባው ላይ አሉ፤ድርጊቱን የፈፀምነው እኛ ነን!" በማለት ለፖሊስ መናገሩን፣ድርጊቱን አራት ሁነው የፈፀሙት መሆኑንና ሟቹ ይሞታል በሚል ሃሳብ እንዳልፈፀሙ፤ሟችን የመቱትም ታምራት በዱላ ግንባሩን፣ሌሎች በቡጢ እና በድንጋይየመቱት መሆኑን መግለፁንና ከዚያም እንደሸሹና እንደተበታተኑ እንዲሁም ጥዋት ወደ አዝመራ ቦታ ሂዶ ቆይቶ በልዩ ኃይል መያዙን ሲናገር መስማቱን የመሰከረ ነው፡፡6ኛው ምስክር በበኩሉ በወቅቱ በሟች ለቅሶ ላይ እያሉ "የእናተ ቤተሰብ ነው!" በሚል ምክንያት ተይዘው በፖሊስ ጣቢያ እንደነበሩ፣ምሽት ላይ ታምራት የተባለውን ተከሳሽ ፖሊሶች ይዘው ፖሊስ ጣቢያ ውስጥ እያለ አንድ የፖሊስ አባል ታምራትን "ለምንድነው እንዲህ አድርጋችሁ የምትማቱት?" በማለት ሲጠይቀው ታምራት ጭንቅላቱን አልመታሁትም፤እኔ ጀርባውን ነው የመታሁት፣ጭንቅላቱን የመታው ሰው ሌላ ነው ብሎ ሲመልስለት መስማቱን መስክሯል፡፡

     

    እንግዲህ የበታች ፍርድ ቤቶች አመልካቾችን ጥፋተኛ ለማድረግ በዓቃቤ ሕግ በኩል የቀረቡት ምስክሮች ቃል ይዘት ከላይ የተጠቀሰው መሆኑን በውሳኔው ላይ የገለፁት ጉዳይ ሲሆን የዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት በፍርድ ሐተታው በግልጽ ያስቀመጠው ድምዳሜውም  ከዓቃቤ ሕግ ምስክሮች ቃል አመልካቾች ሟችን ሲመቱትና ሲገድሉት አየሁ በሚል ያልተገለጸ መሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡የዞኑ ከፍተኛ ፍርድ ቤት አመልካቾችን ለወንጀል ድርጊቱ ኃላፊ ያደረጋቸው በክሱ በተጠቀሰው ጊዜና ቦታ በሟቹና በአመልካቾች መካከል ጠብ ተፈጥሮ ሟቹ ከስር ሶስተኛ ተከሳሽ ጋር በአንድ በኩል፣አመልካቾቹ ደግሞ በሌላ በኩል ተቀምጠው ሟቹ ምራቅ ሲተፋ አመልካቾች "ይህች ምራቅ ዛሬ ደም ትሆናለች!" በማለት ተናገረው ወዲያውኑ ሟቹና የስር 3ኛ ተከሳሽ ከአረቄ ቤቱ ወጥተው ሲሄዱ ወዲያውኑ የወንጀል ድርጊቱ መፈፀሙን ተረጋግጧል በሚል ድምዳሜ ነው፡፡


    አመልካቾች ከሚከራከርባቸው ነጥቦች ውስጥ የአመልካቾችን የድርጊት ፈፃሚነት በተገቢው መንገድ አቃቤ ሕግ በማስረጃ ያለማስደገፉንና የአቃቤ ሕግ የአይን ምስክሮች  ድርጊት ፈፃሚዎችን በወቅቱ ስለመለየታቸው ሳይመሰክሩ ሰምተናል በማለታቸው ብቻ ጥፋተኛ መባላችን ያላግባብ ነው የሚለውን በወንጀል ጉዳይ የሚቀርብ ማስረጃ ከሚመዘንበት መርህ ጋር በማጣቀስ ነው፡፡

     

    በመሰረቱ በአንድ የወንጀል ጉዳይ የሚቀርብ ማስረጃ በቂና አሣማኝ በሆነ ሁኔታ የወንጀል ድርጊቱ መፈፀሙንና የወንጀል ድርጊቱን ፈፃሚውን ማንነት በትክክል ለይቶ ማሳየት ያለበት ስለመሆኑ በወ/መ/ሕ/ሥ/ሥ/ቁጥር 141 ድንጋጌ ይዘትንና መንፈስ የምንገነዘበው ጉዳይ ነው፡፡አንድ ሰው ለወንጀል ድርጊት ኃላፊ ተብሎ ቅጣት ሊወሰንበት የሚገባው ወንጀል መስራቱ ወይም መፈፀሙና ተሰራ ወይም ተፈፀመ የተባለው ወንጀል ደግሞ በተከሳሹ መፈፀሙ በበቂና በአሳማኝ ሁኔታ ሲረጋገጥ ስለመሆኑ ከወንጀል ሕጉ አንቀጽ 23(4)፤32፣40፤57፣ 58(1) እና ከወ/መሕ/ሥ/ሥ/ቁጥር 141፣142 እና 149 ድንጋጌዎች አገላለፅና መንፈስ መመልከት የምንችለው ጉዳይ ነው፡፡ማንም ሰው በዋና ወንጀል አድራጊነት ወንጀል እንዳደረገ የሚቆጠረው ወንጀሉን እርሱ ራሱ በቀጥታ ቢያደርግ ወይም በቀጥታ ባያደርግም እንኳን በመላ ሀሳቡና አድራጐቱ በወንጀሉ ድርጊትና በሚሰጠው ውጤት ሙሉ ተከፋይ በመሆን ወንጀሉን  የራሱ ያደረገ ሆኖ ሲገኝ እንደሆነ በወንጀል ሕግ አንቀጽ 32/1/ለ/ በግልጽ ተደንግጓል፡፡ከሳሽ የሆነው አቃቤ ሕጉም ይህንኑ በሕጉ የተጣለበትን ግዴታ መወጣት አለበት፡፡

     

    አመልካቾች ሟችን በቀጥታ መትተው ስለመግደላቸው አይተናል የሚል የአቃቤ ሕግ ምስክር ባይኖርም ሟች ጋር በእለቱ በአረቄ ቤት ሲጨቃጨቁ እንደነበር፣ሟች ምራቅ ሲተፋም ምራቁ ደም እንደሚሆን ተናግረው እንደነበር በአቃቤ ሕግ ምስክሮች ተገልፆአል፡፡ይሁን እንጂ የአቃቤ ሕግ ምስክሮች በወቅቱ ከሟች ጋር ጠብ አስነስተው የነበሩትን ሰዎች ማንነት የገለፁ ቢሆንም ለሟቹ ህልፈተ ሕይወት እያንዳንዱ አመልካች የነበረውን ተሳትፎ ያልተናገሩ ከመሆኑም በላይ የአቃቤ ሕግ ምስክሮች ቃል በሁሉም አመልካቾች ላይ እንደ አከባቢ ማስረጃ የሚወሰድ ነው ቢባልም ማስረጃው በ2ኛ እና 3ኛ አመልካቾች ላይ ግን ጥንካሬ የሌለው ሁኖ ተግኝቷል፡፡በሌላ አነጋገር የተጠሪ ምስክሮች በወቅቱ ስለነበረው አጠቃላይ ሁኔታ /Circumstantial Evidence/ የምስክርነት ቃል ሰጥተው የተመለሱ ቢሆንም ከጠቡ መነሻ ውጪ ከጠቡ በኋላ 2ኛ እና 3ኛ አመልካቾች የነበራቸውን ሚና በግልጽ የሚያሳዩ አይደሉም፡፡ በአገራችን የህግ ሥርዓት ምስክሩ ስለአጠቃላይ ሁኔታዎች በአይኑ የታዘበውን በጆሮው የሰማውንና የሚያውቀውን ፍሬ ጉዳይ ሊመሰክር እንደሚችልና የምስክሩም ቃል ህጋዊ ተቀባይነት ያለው ስለመሆኑ በወንጀለኛ መቅጫ ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 137 ንዑስ አንቀፅ 1 ድንጋጌ ይዘት መንፈስና ዓላማ ለመረዳት ይቻላል፡፡ይሁን እንጂ በ2ኛ እና 3ኛ አመልካቾች ላይ በአቃቤ ምስክሮች የተሰጠው የምስክርነት ቃል በአረቄ ቤት የነበረውን ጠብ እና ሟች ምራቅ ሲተፋ ይህ ምራቅ ደም ሊሆን እንደሚችል አመልካቾች ከመናገራቸው ውጪ በድርጊቱ ወቅት ወይም በኋላ 2ኛ እና 3ኛ አመልካቾች የፈፀሙትን አድራጎት የሚያሳይ አይደለም፡፡ስለሆነም በ2ኛ እና 3ኛ አመልካቾች ላይ የቀረበው የአቃቤ ሕግ ማስረጃ በወንጀል ሕግ የሚቀርብ ማስረጃ ስለጉዳዩ ለማስረዳት በቂና አሳማኝ ማስረጃ ነው ብሎ ለመደመድም የሚያስችል ሊሆን ይገባል የሚለውን መለኪያ ያሟላ ነው ለማለት አልተቻለም፡፡ስለሆነም በእነዚህ አመልካቾች የተሰጠው የጥፋተኛነት ውሳኔ መሰረታዊ የሆነ የሕግ ስህተት ያለበት ሁኖ አግኝተናል፡፡


    1ኛውን አመልካች ታምራት ደምሴን በተመለከተ ግን 1ኛ፣2ኛ እና 3ኛ የአቃቤ ሕግ ምስክሮች አመልካቹ በወቅቱ ስለነበረው አጠቃላይ ሁኔታ ከሰጡት የምስክርነት ቃል በተጨማሪ አመልካቹ ከወንጀል ድርጊቱ በኋላ በፖሊስ ተይዞ ወደ ፖሊስ ጣቢያ ተይዞ ከገባ  በኋላ ወንጀሉን መፈፀሙንና እንዴት እንደፈጸመ ጭምር ሲገልፅ እንደነበር 5ኛ እና 6ኛ የአቃቤ ምስክሮች ከመሰከሩት ቃል መረዳት የሚቻል ሁኖ ስለተገኘ አመልካቹ በሟቹ ህልፈተ ሕይወት ተሳትፎ እንደነበረው በዓቃቤ ሕግ ማስረጃዎች ተደጋጋፊነትና ተመጋጋቢነት ባለው ጠንካራ የአከባቢ ማስረጃ የተረጋገጠ ሁኖ አግኝተናል፡፡በመሆኑም አመልካች ታምራት ደምሴ በቀጥታ የወንጀሉ ተሳታፊ ሁኖ በመላ ሀሳቡ የወንጀሉን ድርጊት እንዲሁም ውጤቱን የራሱ ያደረገ ስለሆነ አመልካቹ ለወንጀል ድርጊቱ ኃላፊ ልባል አይገባም በማለት ያቀረበው ቅሬታ ተቀባይነት ሊሰጠው የሚገባ ሁኖ አልተገኘም፡፡

     

    አንደኛውን ጭብጥ በተመለከተ ስናጠቃልለው 2ኛ እና 3ኛ አመልካቾች ለወንጀሉ ድርጊት ኃላፊ የተባሉት ዓቃቤ ሕግ የወ/መ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 141 በሚያስቀምጠው የማስረጃ መለኪያ መሰረት የአመልካቾችን ተሳትፎ ባላስረዳበትና በሕጉ የተጣለበትን ግዴታ ባልተወጣበት ሁኔታ በመሆኑ በእነዚህ አመልካቾች ላይ የተሰጠው የጥፋተኛነት ውሳኔ መሰረታዊ የሆነ የሕግ ስህተት ያለበት ሲሆን 1ኛ አመልካች ግን ሟች ከመሞቱ በፊትና ሲሞት የነበረው የወንጀሉ ተሳትፎ በሚገባ የተረጋገጠ በመሆኑ በሰው ግድያ ወንጀል ተጠያቂ መደረጉ የሚነቀፍ ሁኖ አይደለም ብለናል፡፡

     

     ሁ ለተ ኛ ውን ጭብጥ በተመለ ከተ፡ -የስር ፍርድ ቤቶች 1ኛ አመልካችን ተጠያቂ ያደረጉት በወንጀል ሕጉ አንቀጽ 539(1(ሀ)) ስር ነው፡፡

     

    በመሰረቱ የሰው ግድያ ወንጀል በወንጀል ሕግ አንቀፅ 539(1(ሀ)) መሰረት ድርጊት ፈጻሚውን ሊያስጠይቅ የሚችለው ድርጊቱ ሆነ ተብሎ አስቀድሞ በማሰብና በመዘጋጀት ሲፈፀም ወይም በአንቀጽ 84 ወይም 86 ስር የተመለከቱት አክባጅ ሁኔታዎች በተገኙበት ሁኔታ የወንጀል አድራጊው በተለይ ጨካኝ፣ነውረኛ ወይም አደገኛ መሆኑን ሲያመለክቱ ስለመሆኑ ተጠቃሹ ድንጋጌ በግልጽ ያሳያል፡፡ከዚህም መገንዘብ የሚቻለው በድንጋጌው ስር የተመለከቱት የወንጀሉ ማቋቋሚያ ነጥቦች በየራሳቸው መቆም የሚችሉ ነጥቦች ስለመሆናቸው ነው፡፡

     

    የወንጀል ህግ አንቀጽ 540 ድንጋጌ ሲታይ ደግሞ፡-

    ”ማንም ሰው አገዳደሉ በአንቀጽ 539 የተመለከተውን ያህል ከባድ ወይም በአንቀጽ 541 የተመለከተውን ያህል ቀላል ባልሆነ ሁኔታ አስቦ ሌላ ሰውን የገደለ እንደሆነ፤ ከአምስት ዓመት እስከ ሃያ ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራት ይቀጣል በሚል አስቀምጧል፡፡

     

    በመሠረቱ በወንጀል ሕጉ አንቀፅ 539 እና 540 መሠረት የሚፈፀሙ ግድያዎች ሆነ ተብሎ ወይም በማወቅ /አስቦ/ የሚሰሩ ናቸው፡፡ በዚህ ረገድ ሁለቱ አንቀፆች ተመሳሳይነት አላቸው፡፡ ነገር ግን ሁለቱን አንቀፆች የተለያዩ የሚያደርጓቸው መሰረታዊ ነጥቦች መኖራቸው የሚታወቅ ነው፡፡ አንድ ሰው በወ.ህ.አንቀጽ 539/1/ሀ/ መሠረት ጥፋተኛ ሆኖ እንዲገኝ በዚሁ አንቀጽ የተጠቀሱት ሁኔታዎች ተሟልተው መገኘት አለባቸው፡፡እነዚህን ሁኔታዎች ደግሞ ሰውየው ድርጊቱን ለመፈፀም ካነሣሣው ሃሣብ እና ከድርጊቱ አፈፃፀም አንፃር በመመርመር የድንጋጌውን ትክክለኛ አፈጻጸም መለየት ይቻላል፡፡በድንጋጌው ስለሃሳብ ሁኔታ የሚገልጹትን ሁኔታዎች ስንመለከትም አስቀድሞ የማሰብ ሁኔታ፤ ቂም በቀል፤ጥላቻ፤ ቅናት ወዘተ----የሚሉ የሚገኙ ሲሆን ከባድ የድርጊት አፈፃፀም መኖርን የሚያመላክቱ ነጥቦች ደግሞ በወንጀል ሕጉ አንቀፅ 84


    ስር የተመለከቱትና በተጨማሪም ፍርድ ቤቱ በአንቀጽ 86 መሠረት ከባድ ምክንያቶች ናቸው ብሎ የሚቀበላቸውን ሁኔታዎች የሚያካትቱ ናቸው፡፡

     

    አንድ ሰው ከእነዚህ ከላይ ከተጠቀሱት የሃሣብ ሁኔታዎች ወይም የድርጊት አፈፃፀም አንዱን እንኳ ፈጽሞ ቢገኝ እና ይህም ሁኔታ ሲታይ ገዳዩ “በተለይ” ጨካኝ፤ ነውረኛ ወይም አደገኛ የሚያሰኝ አይነት ሆኖ ከተገኘ በአንቀጽ 539/1/ሀ/ መሠረት ጥፋተኛ ሊሰኝ እና ለዚሁ አድራጎት በሕጉ የተመለከተው ቅጣት ውሳኔ ሊተላለፍበት ይገባል፡፡

     

    አንቀጽ 539/1/ሀ/ በቅድሚያ እንዲሟላ የሚፈልገው መሰረታዊ ነጥብ የአገዳደሉ ሁኔታ አድራጊው በተለይ ጨካኝ፤ ነውረኛ ወይም አደገኛ መሆኑን የሚገልጽ ሆኖ መገኘትን ነው፡፡በድንጋጌው ስር “በተለይ” የሚለው ቃል የሚያስገነዝበው ከተራ አገዳደል ወይም የሃሣብ ሁኔታ ውጭ በሆነ አድራጐት ወይም ለጥቃት መገልገያ የተደረገው መሣሪያ በሟች ላይ ስቃይና መከራ ማሣደር እንዳለበት፣ ግድያውም ከተራው ሁኔታ የተለየ እንደነበር የሚያመለክት ነው ተብሎ ይታመናል፡፡፡ በህጉ በተለይ ጨካኝ ነውረኛ ወይም አደገኛ መባሉ የአገዳደሉ ሁኔታና የመግደያው መሣሪያ አደገኛነት፣ ፍፁም ጨካኝነትን፤ ነውረኛነትን ወይም የተጋነነ አደገኛነትን ማሳየት እንዳለበት የሚያስገነዝብ ነው፡፡ስለሆነም የወ.ሕ.አንቀፅ 539(1(ሀ)) የማክበጃ ልዩ ሁኔታዎች በመኖራቸው ምክንያት ሆን ተብሎ የተፈፀመው ግድያ “ከባድ የሰው ግድያ” የሚባልበትን ምክንያቶች የያዘ ነው፡፡እነዚህ ልዩ ሁኔታዎች በሌሉበት አንድን ተከሣሽ በዚህ አንቀጽ ስር ጥፋተኛ ሊባል የማይችል መሆኑን የሕጉ ይዘትና መንፈስ ያሳያል፡፡ ከእነዚህ እና በተጠቃሹ አንቀፅ በፊደል "ለ" እንዲሁም "ሐ" ስር ከተመለከቱት የድንጋጌዎቹ ማቋቋሚያዎች ውጪ ሆን ተብሎ የሚደረግ ሰው የመግደል ወንጀል የሚያስቀጣው በአንቀጽ 540 ስር ነው፡፡

     

    ወደ ተያዘው ጉዳይ ስንመጣም አመልካች ሟችን ለመግደል አስቀድሞ ሐሳብ ያልነበረው መሆኑ ግልጽ ሲሆን አፈጻጸሙ ሲታይም በተለይ ጨካኝነት ያለበት ነው ለማለት የሚያስችል ስለመሆኑ የአቃቤ ሕግ ምስክሮች ቃል አያሳይም፡፡እንዲሁም የአገዳደሉ ሁኔታና የመግደያው መሣሪያ አደገኛነት ፍፁም ጨካኝነትን፤ ነውረኛነትን ወይም የተጋነነ አደገኛነትን አያሳይም፡፡እንዲህ ከሆነ ደግሞ አድራጎቱ በእለቱ በተፈጠረው ያለመግባባት በቀላሉ ለህልፈት የሚዳረግ የሰውነት ክፍል በዱላ በመምታት የሆነው ይሁን በማለት የፈፀመውና በተራ የሰው ግድያ ወንጀል ስር የሚሸፈን እንጂ በግፍ ሰው የመግደል ወንጀል በሚያስጠይቅበት የወንጀል ሕግ አንቀፅ 539(1(ሀ)) ድንጋጌ መሰረት የሚጠየቅበትን አግባብ አላገኘንም፡፡ስለሆነም የበታች ፍርድ ቤቶች 1ኛ አመልካችን በወንጀል ሕጉ አንቀጽ 539(1ሀ) ስር ጥፋተኛ ያሉት አጠቃላይ የድርጊቱን አፈፃጸም ከድንጋጌው ይዘትና መንፈስ ጋር ሳያገናዝቡ ሁኖ ስለአገኘነው በዚህ ረገድ የተሰጠውን ውሳኔ በወ/መ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 195(2)(ለ-2) ድንጋጌ መሰረት በመለወጥ 1ኛ አመልካች(ታምራት ደምሴ) የወንጀል ሕግ አንቀጽ 540 ድንጋጌን የተላለፈ ጥፈተኛ ነው በማለት ወስነናል፡፡

     

    ቅጣትን በተመለከተ 1ኛ አመልካች ሊቀጣ የሚገባው በዚህ ችሎት ጥፋተኛ በተባለበት የሕግ ድንጋጌ መሰረት ነው፡፡አመልካች ተራ የሆነ የሠው ግድያ ወንጀል መፈፀሙ በሚገባ ተረጋገጧል፡፡በወንጀል ሕግ አንቀጽ 540 ስር ጥፋተኛ የተባለ አጥፊ ደግሞ ሊቀጣ የሚገባው ከአምስት አመት እስከ ሃያ አመት ጽኑ እስራት ነው፡፡

     

    በመሠረቱ የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፖብሊክ የወንጀል ህግ የአገሪቱን  የወንጀል ህግ ግብ በአዋጅ ቁጥር 414/1996 አንቀጽ 1 ስር ሲደነግግ “የወንጀል ህግ ግብ ወንጀል


    እንዳይፈፀም መከላከል ሲሆን ይህንን የሚያደርገው ስለወንጀሎችና ስለቅጣታቸው በቅድሚያ ማስጠንቀቂያ በመስጠት፣ ማስጠንቀቂያነቱ በቂ ባልሆነበት ጊዜ ወንጀል አድራጊዎቹ ተቀጥተው ሌላ ወንጀል ከመፈፀም እንዲቆጠቡና ለሌሎች ማስተማሪያ እንዲሆኑ ወይም እንዲታረሙ በማድረግ ወይም ተጨማሪ ወንጀሎች እንዳይፈፀሙ እርምጃዎች እንዲወሰዱባቸው በማድረግ ነው” በማለት ያስቀምጣል፡፡ ህጉ በአንቀጽ 87 ላይ ቅጣቶችና የጥንቃቄ እርምጃዎች ህጉ ሊደርስበት ያሠበውን ዓላማ ለማረጋገጥ በሚቻልበት ሁኔታ በህጉ መንፈስ መሠረት መፈፀም እንዳለባቸው በመርህ ደረጃ ይደነግጋል፡፡ይኸው አንቀጽ ቅጣቶችና የጥንቃቄ እርምጃዎቹ ምን ጊዜም ሠብዓዊ ክብርን በሚጠብቅ መንገድ መፈፀም እንደሚኖርባቸው ያስገነዝባል፡፡  የወንጀል ህጉ አንቀጽ 88 ሲታይም የቅጣቶች እና የጥንቃቄ እርምጃዎች አወሣሠንን በተመለከተ ዘርዘር ያሉ ንዑስ ድንጋጌዎችን አካቶ ይዟል፡፡ በዚህ አንቀጽ ስር ያሉ ንዑስ አንቀጾች የሚያሣዩት ፍርድ ቤቱ ቅጣቶችንና የጥንቃቄ እርምጃዎችን የሚወሰነው የወንጀል ህጉን ጠቅላላ ክፍል ድንጋጌዎችን እንዲሁም ስለወንጀሎችና ስለቅጣታቸው የሚደነግጉትን የልዩ ክፍሉ ድንጋጌዎች መሠረት በማድረግ መሆኑን፣ ቅጣት ሊወሰን የሚገባው የወንጀል አድራጊውን ግላዊ የአደገኛነት መጠን ያለፈ የህይወት ታሪኩን ወንጀል ለማድረግ ያነሣሡትን ምክንያቶችና የአሣቡን ዓላማ የግል ኑሮውን ሁኔታ፣ የትምህርቱን ደረጃ፣ እንዲሁም የወንጀሉን ከባድነትና የአፈፃፀሙን ሁኔታዎች በማመዛዘን መሆኑን፣ የወንጀል ህግ ልዩ ክፍል ድንጋጌዎች እንደተጠበቁ ሆኖ ፍርድ ቤቱ እጅግ ቀላል ከሆነው ቅጣት አንስቶ እስከ ከባዱ ድረስ ያለውን በጥንቃቄ በመመርመር ለእያንዳንዱ ጉዳይ ተገቢ የሆነውን ቅጣት እንደሚወስን የቅጣት አወሳሳን ደንቡ በግልፅ ያሳያል፡፡ከላይ እንደተገለጸው የወንጀል ቅጣት የሚወሰነው በወንጀል ሕጉ አንቀጽ 88(2)ስር የተመለከቱትን ሁኔታዎችን ግንዛቤ ውስጥ በማስገባት ነው፡፡ይህ ችሎትም እነዚህ ሁኔታዎችን ተመልክቷል፤አመዛዝኗልም፡፡ አመልካች ጥፋተኛ የተባለበት ድንጋጌ ድርጊቱ በተፈጸመበትና ክርክሩ በስር ፍርድ ቤት ታይቶ ዳኝነት በተሰጠበት ጊዜ በነበረው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ መሰረት ደረጃ ያልወጣለት የነበረ ሲሆን በተሻሻለው የቅጣት አወሳሰን መመሪያ ደግሞ ደረጃ የወጣለት ነው፡፡እኛም ጉዳዩን ከዚሁ ከአዲሱ የቅጣት አወሳሰን መመሪያ አንፃር ተመልክተናል፡፡

     

    ከዚህ አንጻር ጉዳዩን ስንመለከተው አመልካች ከሟች ጋር ለጠብ የተዳረገው በሟቹ ስድብ ምክንያት ሲሆን ይህም ለወንጀል ድርጊቱ መንስኤው ሟቹ መሆናቸውን የሚያሳይ  ሁኖ ለድርጊቱ አፈጻጸም አመልካች የተጠቀመበት መሳሪያም ዱላ የነበረ ሁኖ የዱላው አይነትና አደገኛነትም በማስረጃ ያልተረጋገጠ መሆኑ ሲታይ አፈፃፀሙ የራሱ የሆነ የተለየ ዘዴ የነበረው መሆኑን የማያሳይ በመሆኑ በመመሪያው መሰረት የወንጀሉ ደረጃው 2 ሁኖ ይሄው ደረጃ በእርከን 23 ስር የሚወድቅ ነው፡፡በዚሁ እርከን ደግሞ የፍርድ ቤቱ የፍቃድ ስልጣን ከስድስት አመት እስከ ሰባት አመት ከሁለት ወር ነው፡፡ከዚሁ ፍቅድ ስልጣን ውስጥ የመነሻ ቅጣቱን ይዘን የቅጣት ማክበጃ ምክንያቶችን ባለመኖራቸው እርከኑን ከፍ ማድረግ ያለመቻሉን ተገንዝበናል፡፡በሌላ በኩል አመልካች ጠቅላላ የቅጣት ማቅለያም ሆነ ልዩ የቅጣት ማቅለያ ምክንያቶች ያሉት መሆኑን በስር ፍርድ ቤት በማስረጃ ተደግፎ የተመዘገበለት ያለመሆኑን ከውሳኔው ግልባጭ ተገንዝበናል፡፡በመሆኑም በእርከን 23 ስር ካለው የፍርድ ቤቱ ፍቅድ ስልጣን ውስጥ 1ኛ አመልካችን (ታምራት ደምሴን) ያርማል፣መሰል ወንጀለኞችን ያስጠንቅቃል ያልነው የቅጣት መጠን ሰባት አመት ሁኖ ስለአገኘን አመልካች በጉዳዩ ላይ የታሰረው ካለ የሚታሰብለት ሁኖ በዚሁ የቅጣት መጠን እንዲቀጣ በማለት ከላይ በዝርዝር በተመለከቱት ህጋዊ ምክንያቶች የበታች ፍርድ ቤቶች ውሳኔ መሰረታዊ የሆነ የሕግ ስህተት ያለበት ነው በማለት በማሻሻል ተከታዩን ወስነናል፡፡


     

     

     ው ሣኔ

     

    1. በመተከል ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመ/ቁጥር 04545 ሚያዚያ 5 እና 6 ቀን 2003 ዓ/ም ተሰጥቶ በክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በመ/ቁጥር 02856 ግንቦት 02 ቀን 2003 ዓ/ም፣በክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት በመ/ቁጥር 03200 መስከረም 11 ቀን 2004 ዓ/ም በትዕዛዝ የፀናው የጥፋተኛነትና የቅጣት ውሳኔ በወ/መ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 195(2)(ለ-2) መሰረት ተሻሽሏል፡፡

    2. 2ኛ አመልካች በሪሁን ደምሴ፣3ኛ አመልካች ታደለ ሽቱ ሟች ኤርሚያስ ሃይሉን ስለመግደላቸው በበቂና አሳማኝ ሁኔታ ስላልተመሰከረባቸው በእነዚህ አመልካቾች ላይ የተሰጠውን የጥፋተኛነትና የቅጣት ውሳኔ በወ/መ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 195(2)(ለ-1) መሰረት ሙሉ በሙሉ በመሻር አመልካቾቹን በነጻ እንዲሰናበቱ በማለት ወስነናል፡፡አመልካቾቹ በሌላ ወንጀል የማይፈለጉ መሆኑ ከተረጋገጠ ወዲያውኑ ከእስር እንዲፈቱ ተገልፆ የመፍቻ ትዕዛዝ ለክፍሉ ማረሚያ ቤት ይድረሰው ብለናል፡፡ይጻፍ፡፡

    3. 1ኛ አመልካች ታምራት ደምሴ በሟች ኤርሚያስ ኃይሉ ህልፈት ተጠያቂ መደረጉ በአግባቡ ተመስከሮበት ሲሆን የአመልካቹ አድራጎት የሚሸፈነው ግን በወ/ሕ/አንቀጽ 539(1(ሀ) ሳይሆን በወንጀል ሕጉ አንቀጽ 540 ስር ነው በማለት በዚሁ የሕግ ድንጋጌ ስር ጥፋተኛ በማድረግ በጉዳዩ ላይ የታሰረው ማናቸውም ጊዜ የሚታሰብለት  ሁኖ በሰባት አመት ፅኑ እስራት እንዲቀጣ ወስነናል፡፡

    4. በ1ኛ አመልካች በዚህ ችሎት ተሻሽሎ በተወሰነው የቅጣት ውሳኔ መሰረት ተከታትሎ እንዲያስፈፅም ለክፍሉ ማረሚያ ቤት ይድረስ ብለናል፡፡ይጻፍ፡፡

     

    መዝገቡ ተዘግቷል፤ ወደ መዝገብ ቤት ይመለስ ብለናል፡፡

     

    የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡

  • የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ ያልተወረሰ ቤትን በህገወጥ  መንገድ በመያዝ የተጠቀመበት ከሆነ የኪራይ ገንዘብና ያለአግባብ የበለፀገበትን ያህል ሊከፍል የሚገባ ስለመሆኑ፡-

     

    ያለአግባብ በመንግስት ተይዞ ለቆየ ቤት የታጣ ጥቅም አይከፈልም ሊባል የማይችል ስለመሆኑ፡-

     

    የፍ/ሕ/ቁ 2162

     

    አዋጅ ቁጥር 193/92 አንቀፅ 7(3) አዋጅ ቁጥር 192/92 አንቀፅ 3

    የሰ/መ/ቁ. 97683

     

    መጋቢት 18 ቀን 2007 ዓ.ም

     

    ዳኞች፡-አልማው ወሌ

     

    ዓሊ መሀመድ ሱልጣን አባተማም ሙስጠፋ አህመድ ተኸሊት ይመሰል

    አመልካች፡- አክበር አሊ ካምሩዲን ኩባንያ ተጠሪዎች ፡- 1) የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ

    2) የመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ የቀጠና 4 ጽ/ቤት

     

    3) በመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ የአ/አ ቅ/ጽ ቤት

     

    መዝገቡ ተመርምሮ የሚከተለው ፍርድ ተሰጥቷል፡፡

     

     ፍ ር ድ

     

    ጉዳዩ የተጀመረው በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ሲሆን አመልካች ከሳሽ ተጠሪዎች ተከሳሽ ነበሩ፡፡ አመልካች ባቀረቡት ክስ 1ኛ ተጠሪ የቤት ቁ.868 እና 872 ሁከት በመፍጠር በመያዝ 2ኛ ተጠሪ በቤት ውስጥ የነበሩትን ልዩ ልዩ ዕቃዎች እና ሰነዶች በ3ኛ ተጠሪ መጋዘን የተቀመጠ ሲሆን 2ኛ ተጠሪ ዕቃውን እንዲመልስ ቢጠየቅ ለመመለስ ፍቃደኛ አልሆነም በተጨማሪም 1ኛ እና 2ኛ ተጠሪዎች የአመልካችን ቤት ለተለያዩ ግለሰቦች እያከራዩ ብር 149,294,00 (አንድ መቶ አርባ ዘጠኝ ሺ ሁለት መቶ ዘጠና አራት ብር) ተጠቅመውበታል፡፡ አመልካች ቤቱን ስረከብ 5000 ብር ወጪ አድርጌያለሁ ፡፡1ኛ እና 2ኛ ተጠሪ ቤቱን አከራይተው አለአግባብ የበለጸጉበትን እና ቤቱን ለማሳደስ ያወጣሁትን ወጪ በድምሩ 154,294,00 (አንድ መቶ ሀምሳ አራት ሺ ሁለት መቶ ዘጠና አራት ብር) የስር 4ኛ፣5ኛ ፣6ኛ ተከሳሾች ጭምር የአሁን ተጠሪዎች የአመልካችን ንብረት ይመልሱ ፣ካልሆነ ግምቱን ብር 124,786.(አንድ መቶ ሀያ አራት ሺ ሰባት መቶ ሰማንያ ስድስት ብር) እንዲከፍሉኝ ባጠቃላይ ተጠሪዎች 279,080.00(ሁለት መቶ ሰባ ዘጠኝ ሺ ሰማንያ ብር) ከእነወለዱ እንዲከፍሉ፣ወጪና ኪሳራ እንዲተኩ ተብሎ ይወሰንልኝ ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ በመሆኑም ፍርድ ቤቱ ጉዳዩን በማየት የስር 4ኛ፣5ኛ እና 6ኛ ተከሳሾች ከክሱ በማሰናበት ከ1ኛ እስከ 3ኛ ያሉት ተጠሪዎች በሰጡት መልስ አመልካች ተጠሪዎች ያለአግባብ የበለጸጉበትን ኪራይ ገንዘብ ይከፈለኝ በማለት  መጠየቅ አይችሉም መጠየቅ ቢችሉም በመንግስት እጅ የቆየን ንብረት የሚጠየቅ ጉዳትም ሆነ ኪራይ የለም ተጠሪ ንብረት ተረክቧል ቢባል እንኳ ንብረቶቹ  ያልተመዘገቡና  እርጅና ያልተቀነሰ እንዲሆን ቁሳቁሶቹን በመጋዘን ለማስቀመጥ የፈጀው ጊዜ ከቀረበው ዋጋ በላይ ነው ሌላው አመልካች 5000 ብር ወጪ አደረግኩ የሚሉት ቤቱን ለማበላሸታችን ባለ ማስረዳታቸው ጥያቄው


    ባጠቃላይ ውድቅ ሊሆን ይገቧል በማለት ተከራክረዋል ፡፡ ጉዳዩን የተመለከተው ፍርድ ቤትም ግራቀኙን በማከራከር አመልካች ያቀረቡትን የታጣ ገቢና የኪራይ ጥቅም አስመልክቶ በአዋጅ ቁ.192/92 በአንቀጽ 3 ላይ በመንግስት እጅ በቆየበት ጊዜ ለታጣ ጥቅም(ገቢ) ማናቸውም የጉዳት ካሳ መጠየቅ እንደማይቻል የሚደነግግ በመሆኑ የተጠየቀው የቤት ኪራይ ይከፈለኝ በማለት አመልካች የጠየቁትን ዳኝነት ውድቅ በማድረግ የንብረትን ጥያቄ በተመለከተ ተጠሪ እርጅናቸው አልተቀነሰም በማለት ተከራክረዋል፡፡ ይህ ደግሞ የአመልካችን የንብረት መጠየቅ መብት አያስቀረውም፡፡ሌላው አመልካች ቤቱን ቀለም ለማስቀባት አወጣሁት የሚሉት  5000 ብር ተጠሪዎ በቤቱ ላይ ጉዳት ያድርሱ ወይም በራሱ ጊዜ ቀለም የፈለገ ስለመሆኑ የሚያሳይ አይደለም በማለት አልፎታል፡፡

     

    በአጠቃላይ ንብረትን በተመለከተ በተጠሪ ተዘርዝረው የቀረቡትን የንብረት በአይነቶች እነዲያስረክቡ ካልሆነ ግምቱን 124,786.000(አንድ መቶ ሀያ አራት ሺ ሰባት መቶ ሰማኒያ ስድስት ብር) ከነወለዱ ክስ ከቀረበበት ቀን ጀምሮ ይክፈል በማለት ወስኗል፡፡ በቀጣይነት ጉዳዩን ያየው ከፍተኛው ፍርድ ቤትም መዝገቡን በመመርመር ክርክር የተነሳበት ቤት በተመለከተ የተወረሰ አይደለም ከህግ ውጭ ተይዟል በሚል ምክንያት ሁከት ይወገድ ተብሎ አመልካች ቤታቸውን የተረከቡ መሆኑን የበፊት መዝገብ ያመላክታል ይህ ከሆነ ደግሞ የአዋጅ ቁጥር 193/92 አንቀጽ 7/3 ከአዋጅ ውጭ በመንግስት እጅ የቆየ ንብረት ለታጣ ገቢ ወይም ለደረሰ ጉዳት ካሳ ክፍያ መጠየቅ አይችልም ስለሚል በዚህ ረገድ የተሰጠው ውሳኔ የሚነቀፍ  አይደለም

    ፡፡ ንብረትን አስመልክቶ ግምቱን ወይም በአይነት ያስረክቡ የሚለው የውሳኔ ክፍልም ስህተት የለበትም በማለት ባጠቃላይ አጽንቶታል፡፡

     

    የአመልካች አቤቱታም የቀረበው ይህንኑ ውሳኔ ለማስለወጥ ነው በመሆኑም አመልካች ባቀረቡት የሰበር አቤቱታ ቅሬታቸውን ሲገልጹ፡- የአመልካች ጥያቄ ተጠሪዎች ቤቱን ሁከት በመፍጠር ይዘው አከራይተው የተቀበሉትን ገንዘብ ሊከፍሉኝ ይገባል የሚል ሆኖ ሳለ ለአዋጅ ቁጥር 193/92 የተሳሳተ ትርጉም በመስጠት ሊከፈልህ አይገባም ተብሎ መወሰኑ ሊታረም የሚገባው ነው፡፡ ተጠቃሹ አዋጅ ቁ.193/92 የፕራይቬታይዜሽን ኤጀንሲ ለሚያስተናግደው ክርክር የወጣን ወጪን እንጂ በፍርድ ቤት ክስ ቀርቦበት ውሳኔያገኘ አይነት ባለመሆኑ ውድቅ ሊሆን ይገባል በአጠቃላይ መንግስት (ተጠሪ) ማከራየታቸውን ባልካዱበት የሰበሰቡትን ገንዘብ  ሊመልሱ አይገባም መባሉና ብር 5000 ጥያቄ ውድቅ መደረጉም መሰረታዊ የህግ ስህተት የተፈጸመበት በመሆኑ ሊታረም የሚገባው ነው በማለት አመልክቷል፡፡

     

    በዚህም መሰረት ችሎቱም የአዋጅ ቁጥር 193/92 ተጠቅሶ ተጠሪ የአመልካችን ቤት ሁከት በመፍጠር ይዞ አከራይቶ እየተጠቀመበት ሊመልሱ አይገባም ተብሎ የመወሰኑን አግባብነት በጭብጥነት በመያዝ የግራቀኙን በጹሁፍ በማከራከር መልስ እና የመልስ መልስ በማቀባበል አከራከሯል፡፡

     

    ተጠሪዎች በሰበር መልሱ የሚሉት በአዋጅ 47/67 የተወረሰ ቤት አይደለም ሁከት ፈጥራችው የያዛችሁት ነው ተብሎ ተወስኖ የነበረ መሆኑ የተረጋገጠ ነው፡፡ ስለዚህ መንግስት በእጁ ይዞ ሲያስተዳድር በነበረበት ጊዜ አመልካች ያጣውን ገቢ ወይም ጥቅም በአዋጁ ቁጥር 193/92 አንቀጽ 3 መሰረት ሊጠይቅ አይችልም ተብሎ መወሰኑ የሚነቀፍ አይደለም ሌላው በስር ፍርድ ቤት ሁከት ፈጥሮ መያዝና ወርሶ መያዝ አንድ ናቸው አላለም ስለዚህ በዚህ ረገድ የተነሳው ክርክር ተቀባይነት የለውም፡፡ ባጠቃላይ ተጠቃሹ አዋጅ በአግባቡ የተተረጎመ በመሆኑ የአመልካች


    ጥያቄዬ አግባብነት የለውም፡፡ ሌላው አመልካች ለእድሳት አወጣሁ የሚሉት 5000 ብር(አምስት ሺ) ብር ውድቅ መደረጉ የሚነቀፍ ባለመሆኑ የስር ውሳኔ ሰህተት የለበትም ተብሎ ሊጸና የሚገባው ነው በማለት ተከራክረዋል አመልካች በበኩሉ የስር ክርክሩን በማጠናከር ተጠሪዎች ለ 11 አመታት ቤቶቹን አከራይተው የተጠቀሙበትን እና ያሳደስኩበትን ወጪ ነው የጠየቅኩት እንጂ የጉዳት ካሳ ከገንዘባቸው ክፈሉኝ የሚል ክስ የቀረበበት ሁኔታ የለም ስለዚህ ጉዳይ በማይመለከተው አዋጅ ቁ.193/92 ተጠቅሶ ገንዘብህን ሊከፈልህ አይገባም ተብሎ መወሰኑ መሰረታዊ የህግ ስህተት የተፈጸመበት በመሆኑ ሊታረም ይገባል በማለት ተከራክረዋል፡፡

    በአጠቃላይ የክርክሩ አመጠጥ ባጭሩ ከላይ የተጠቀሰውን ይመስላል፡፡ እኛም የግራቀኙን ክርክር አቤቱታ ከቀረበበት ውሳኔ እና አግባብነት ካለው የህግ ድንጋጌ አንጻር መዝገቡን መርምረናል ፡፡ በመሆኑም ከተያዘው ጭብጥ አንጻር የክርክሩን አመጣጥ አንዳየነው የአመልካች ጥያቄ የነበረው ተጠሪዎች ሁከት ፈጥረው የያዙትን ቤት ለቀው ሁከት ይወገድ በመባሉ ለቀዋልና ያለአግባብ ይዘው በነበሩበት ወቅት ለግለሰቦች ቤቱን በማከራየት የሰበሰቡትን ገንዘብ ይመልሱልኝ በውስጡ የነበረውን ንብረት እና ያሳደስኩበትን ይተኩልኝ የሚል መሆኑን ከመዝገቡ መረዳት የሚቻል ነው፡፡

    እንግዲህ በተያዘው ጉዳይ ያከራከረው ተጠሪ አዋጅቁጥር 193/92 ጠቅሶ በመንግስት የቆየን ንብረት ጥቅም ወይም ጉዳት መጠየቅ ስለማይቻል ልንጠየቅ አይገባም በማለቱ እና የስር ፍርድ ቤቶችም በዚህ ረገድ የቀረበውን የተጠሪን መከራከሪያ በመቀበል በተጠቃሹ አዋጅ መሰረት አመልካች መጠየቅ አይገባውም በማለት በመወሰናቸው እና የእድሳት ገንዘቡን ውድቅ በማድረጋቸው ነው፤ይህ ችሎትም አመልካች በተጠቀሰው አዋጅ መሰረት በኪራይ ተጠሪዎች የሰበሰቡትን ገንዘብ ሊመልሱ ይገባል? ወይስ በተጠቃሹ አዋጅ መሰረት መከፈል የለበትም? የሚለው ነጥብ ምላሽ ሊያገኝ የሚገባው ሆኖ አግኝቷል፡፡ በመሆኑምከስር  ክርክር እንደተገነዘብነው ተጠሪ ያልተወረሰ ቤት በመያዙ ምክንያት በፍርድ ሀይል ሁከት መፍጠሩ ተረጋግጦ ቤቱን መልቀቁ የተረጋገጠና በግራቀኙ ያልተካደ ነው በተጨማሪም  ተጠሪም ተጠቃሹን ቤት አላከራየሁም በማለት የተከራከረው ነገር የለም በስር ፍርድ ቤቶች የፍርድ ሀተታም ቢሆን ቤቱ አልተከራየም በሚል የተጠቀሰ ነገር የለም ፡፡ በመሆኑም መከራየቱ ያላከራከረ ፍሬ ነገር በመሆኑ በዚህ ረገድ ተጠሪም የዚህ ችሎት መከራከሪያው አላደረገም ፡፡ ይልቁንም የተጠየቀውን ገንዘብ ልንከፍል አንገደድም የሚል መሆኑን አጉልቶ የሚከራከረው ጉዳይ ነው፡፡ በመሆኑም ከተጠቃሹ አዋጅ ቁ.193/92 ድንጋጌ በመንግስት እጅ በቆዬ ንብረት ለታጣ ገቢ ወይም ለደረሰ ማንኛውም ጉዳት ካሳ ክፍያ መጠየቅ አይቻልም የሚል ነው፡፡ እንግዲህ ከፍ ሲል ለመጥቀስ እንደተሞከረው ቤቱ በተጠሪ በመያዙ ብቻ ሊያገኙ የነበሩትን ጥቅም በማጣታቸው የደረሰባቸውን ካሳ ከምንም ተነስቶ ተጠሪ እንዲከፈላቸው ሳይሆን በህገወጥ መንገድ ቤቱን ይዞ በእውነቱ ሲያከራየው የነበረውን እና ቤታቸው የፈጠረላቸውን የራሳቸውን ገንዘብ እንጂ ቤቱ ተወርሶ ተይዞ በመቆየቱ በካሳ መልክ ከመንግስት የሚከፈላቸው ማካካሻ አይደለም። ስለዚህ ተጠሪ ያልተወረሰ ቤት በህገወጥ መንገድ በመያዝ የበለጸገበትንና አላከራየሁም በሚል ያላስተባበለውን የኪራይ ገንዘብ ለመክፈል አልገደድም ማለቱ እና ፍርድ ቤቶቹም ተጠሪዎች ያቀረቡትን መቀበላቸው የአዋጁን አላማ እና ሊያሳካ የፈለገውን ግብ ያገናዘበ አይደለም አዋጅ ቁጥር 193/92 ለዚህ ጉዳይ ተፈፃሚ ሊሆን የሚችልበት ምክንያት የለም ፡፡ በመሆኑም ተጠሪዎች ቤቱን ይዘው ለሰበሰቡት ኪራይ በፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 2162 እና ተከታይ ድንጋጌዎች መሰረት ኃላፊ ሊሆኑ ይገባል ብለናል ፡፡ ይህን ካልን በስር ፍርድቤት ተጠሪዎች በምን ያህል እንዳከራዩ፤ቤቱ  ለስንት  አመታት  እንደተከራዬ  ጭብጥ  ተይዞና  በማስረጃ  ተለይቶ ክርክር


    ያልተደረገበት በመሆኑ በዚህ ዙሪያ ያሉት ነጥቦች ተጣርተው ሊወሰኑ የሚገባቸው በመሆኑ ጉዳዩን ወደ ስር ፍርድ ቤት መመለሱ ስነ ስርዓታዊ ሁኖ አግኝተናል ፡፡

    ሌላው የአመልካች ቅሬታ ቤቱ የታደሰበትን 5000 ብር አስመልክቶ የስር ፍርድ ቤቶች ተጠሪ ሊከፍል አይገባም ሲሉ የሰጡትን ውሳኔ ተገቢ አይደለም ብለው አመልካች ያቀረቡትን አቤቱታ በተመለከተ የስር ፍርድ ቤቶች ፍሬ ነገሩን አጣርተውና ማስረጃውን መዝነው ውድቅ ያደረጉት ስለሆነ ይህ ችሎት በኢ.ፌ.ዲ.ሪ.ሕግ መንግስት አንቀጽ 80(3(ሀ)) እና አዋጅ ቁጥር 25/1988 አንቀጽ 10 ከተሰጠው ስልጣን አንፃር የሚታይ ባለመሆኑ በዚህ ረገድ የቀረበውን ቅሬታ አልተቀበልነውም፡፡

    በአጠቃላይ የፌዴራል የመጀመሪያው ደረጃ ፍርድ ቤት እና ከፍተኛ ፍርድ ቤት በአዋጅ ቁጥር 193/92 መሰረት በማድረግ በመንግስት እጅ ለቆዬ ንብረት ተጠሪዎች የሰበሰቡትን ኪራይ ሊከፍሉ አይገባም በማለት የደረሱበት ድምዳሜ መሰረታዊ የህግ ስህተት የተፈጸመበት ነው ብለናል ፡፡ በመሆኑም የሚከተለው ውሳኔ ተሰጥተዋል፡፡

     

     ው ሳ ኔ

    1. የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በመ.ቁ 175802 በቀን 04/08/2004 ዓ/ም እና የከፍተኛ ፍርድ ቤት በ125972 በቀን 25/03/2006 ዓ.ም የተሰጠው ውሳኔ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 348(1) መሰረት ተሻሽሏል፡፡

    -   አመልካች ያቀረቡት የ 5000 ብር የእድሣት ክፍያ እና ንብረትን አስመልክቶ የተሰጠው የውሳኔ ክፍል ፀንቷል፡፡

    2. ተጠሪዎች ከአከራካሪው ቤት ላይ የሰበሰቡትን የኪራይ ገንዘብ የመመለስ ሀላፊነት አለባቸው ብለናል ፡፡ በመሆኑም የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አከራካሪው ቤት በምን ያህል የኪራይ ገንዘብ ሲከራይ እንደነበር ፤ እና ከመቼ ጀምሮ ሲከራይ እንደነበር በጭብጥነት ይዞ የግራ ቀኙን ማስረጃዎችን በመስማትና እና አስፈላጊ ነው ብሎ ካመነም ፍርድቤቱ በራሱ አነሳሽነት በሚያስቀርባቸው ማስረጃዎች አጣርቶ በጉዳዩ ላይ ተገቢውን ውሳኔ እነዲሰጥበት ጉዳዩን በፍ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ.343(1) መሰረት መልሰን ልከንለታል ፡፡ ይፃፍ፡፡

    3.  የግራቀኙ የወጪኪሳራቸውን ይቻቻሉ ብለናል፡፡  መዝገቡ ውሳኔ በማግኘቱ ተዘግቷል፡፡

     

     

     

     

    ት/ጌ                               የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡

  • Family law

    Contract of marriage

    Interpretation of contract of marriage

    አንድ ወንድና ሴት ሲጋቡ በጋብቻ ውላቸው ንብረትን በተመለከተ ካደረጉት ስምምነት ላይ “ከወለደች የግል የለባትም” ፣ “ ሀብትሽ ሀብቴ ነው “ ተብሎ የተፈጸመው የውል ሀረግ ካለና ልጅ ከወለዱ ከጋብቻ በፊት የነበራቸውን የግል ንብረት የጋራ ለማድረግ እንደተስማሙ የሚቆጠር ስለመሆኑ፣

    98029