98541 Diplomatic immunity/ jurisdiction of court/ labor law dispute/ Ethiopian employees of UN organizations

የዲፕሎማቲክ ግንኙነቶችን ስምምነት ልምድን ለማክበር ሲባል የውጭ ዲፕሎማቲክ ሚሲዮኖችና ኢትዮጲያዊያን ሠራተኞቻቸው የሚያደርጉት የቅጥር ግንኙነት ላይ የአሠሪና ሠራተኛ ሕግ ተፈፃሚ የማይሆን ስለመሆኑ፡-

 

የተባበሩት መንግስታት አካል የሆነ ድርጅት የተባበሩት መንግስታት ጥቅምና የተለየ ከለላን በተመለከተ በተደነገገ ሥምምነት በማንኛውም የመንግስት ፍ/ቤቶች ተከሶ መቅረብ የሌለበት ሥለመሆኑ፡-

 

አፈፃፀም በፍርድ ቤት የተሰጠ ውሳኔ ትርጉም እንዲኖረው በማድረግ ውጤት ያለውና በተገቢው መንገድ መፈፀም ያለበት መሆኑ የሚታወቅ ቢሆንም ለማንኛውም ጉዳዮች ይሰራል ተብሎ ድምዳሜ ላይ መድረስ የማይቻል ስለመሆኑ፡-

 

አዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀፅ 3/3(ሀ) የተባበሩት መንግስታት ቻርተር አንቀፅ 105

ከተባበሩት መንግስት ጥቅምና የተለየ ከለላን በተመለከተ የተደነገገው ሥምምነት አንቀፅ 2/2/ እና 3

 

የፍ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ 212

የሰ/መ/ቁ/ 98541

 

ህዳር 10 ቀን 2007 ዓ.ም

 

ዳኞች፡- አልማው ወሌ

 

ዓሊ መሐመድ ሡልጣን አባተማም መስጠፋ አህመድ ተኽሊት ይመሰል

አመልካች፡- አቶ አለማየሁ ኦላና - ቀረቡ

 

ተጠሪ፡-የተባበሩት መንግስታት የልማት ድርጅት (UNDP) ታልፏል ፡፡

 

መዝገቡ ተመርምሮ ተከታዩ ፍርድ ተሰጥቷል፡፡

 

 ፍ ርድ

 

ይህ የሰበር ጉዳይ የቀረበው አመልካች በተጠሪ ላይ የአሠሪና ሰራተኛ ጉዳይ አዋጅ ቁጥር 377/1996 ድንጋጌዎችን መሰረት አድርገው ያቀረቡት ክስ ተጠሪ በሌለበት ታይቶ በክርክሩ ከተረጋገጠበት የፍሬ ነገር ጉዳዮች በመነሳት የአሁኑ አመልካች የተለያዩ ክፍያዎች በተጠሪ እንዲከፍሏቸው በወረዳው ፍርድ ቤት በተወሰነው መሰረት የአፈጻጸም መዝገብ ከፍተው ክርክሩ በመታየት ላይ እያለ ተጠሪ የመከሰስ መብት የለውም ተብሎ የአፈጻጸም መዝገቡ በሁሉም የበታች ፍርድ ቤቶች መዘጋቱ ተገቢ መሆን ያለመሆኑን ለመመርመር ተብሎ ነው፡፡

 

የአሁን አመልካች ተጠሪ ከህግ ውጪ ከስራ አሰናብቶኛል በማለት ካሳና የተለያዩ ክፍያዎች እንዲከፍሏቸው ይወሰን ዘንድ በያበሎ ወረዳ ፍርድ ቤት በአሁኑ ተጠሪ ላይ ክስ መስርተው የአሁኑ ተጠሪ በሌለበት ጉዳዩ እንዲታይ ተደርጎ ፍርድ ቤቱ ጉዳዩን መርምሮ ስንብቱ ሕገ ወጥ መሆኑን በመደምደም ለአመልካች ካሳና የተለያዩ ክፍያዎች እንዲከፈሉ በማለት ወስኗል፡፡አመልካች ይህንኑ ውሳኔ ለማስፈፀም በወረዳው ፍርድ ቤት የአፈጻጸም ክስ ከፍተው ጉዳዩ መታየት ከጀመረ በኋላ የወረዳው ፍርድ ቤት ጉዳዩን መርምሮ የተባበሩት መንግስታት ኮንቬንሽንን አንቀፅ 2(3) በዋቢነት ጠቅሶ ፍርድ ቤቱ ጉዳዩን ለማየት ስልጣን የለውም በማለት የአፈጻጸም መዝገቡን ዘግቶታል። በዚህ ትዕዛዝ አመልካች ቅር በመሰኘት ይግባኛቸውን  ለቦረና ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቢያቀርቡም ተቀባይነት አላገኙም፡፡አመልካች ለክልሉ ሰበር ሰሚ ችሎት አቤቱታቸውን አቅርበውም ችሎቱ ጉዳዩን መርምሮ ተጠሪን ያስቀርባል የሚል ትዕዛዝ ሰጥቶ


ተጠሪ ሊቀርብ ባለመቻሉ መልስ መስጠቱ የታለፈ ሲሆን ችሎቱ ጉዳዩን መርምሮ ጉዳዩ የአሰሪና ሰራተኛ ጉዳይ ሁኖ አመልካች የሚከራከሩት የተባበሩት መንግስታት አካል ከሆነው ድርጅት ጋር መሆኑን፣ ከእንደዚህ አይነት ድርጅቶች ጋር የሚደረግ ግንኙነት በአዋጅ ቁጥር 377/1996 የማይገዛ መሆኑ በተጠቃሹ አዋጅ አንቀጽ 3(ሀ) ስር መመልከቱን፣ተጠሪና መሠል አካላት በሕግ የተለየ ከለላ ያላቸው መሆኑ በተባበሩት መንግስታት ቻርተር አንቀጽ105፣በተባበሩት መንግስታት ጥቅምና የተለየ ከለላን በተመለከተ ለመንደንገግ በወጣው ስምምነት አንቀጽ 2(2) እና 3 ስር መደንገጉን፣ኢትዩጵያም ይህንኑ ስምምነት መፈረሟን በዋቢነት ጠቅሶ ከመነሻውም ተጠሪ በወረዳው ፍርድ ቤት መከሰሱ ተገቢነት እንደሌለው፣አመልካች ያላቸው መፍትሔም በ"United Nations Commission on International Trade Law (UNCITRAL)" ደንቦች  መሰረት ከተጠሪ ጋር ባላቸው ስምምነት መሰረት በእርቅ መጨረስ መሆኑን፣በዋናው ጉዳይ ስልጣን የሌለው ፍርድ ቤት ጉዳዩን አይቶ መወሰኑን ከተጠሪ ጥቅምና ከባለ መብቶች አንፃር ሲታይ ዋናውን ውሳኔ ሕጋዊ የማያደርገው መሆኑን ዘርዝሮ የበታች ፍርድ ቤቶች ጉዳዩን የማየት ስልጣን የለንም በማለት የአፈጻጸም መዝገብ መዝጋታቸውን በመቀበል የአመልካችን የሰበር አቤቱታ ውድቅ አድርጎታል፡፡የአሁኑ የሰበር አቤቱታ የቀረበውም ይህንኑ ውሳኔ በመቃወም ለማስለወጥ ነው፡፡የአመልካች የሰበር አቤቱታ መሰረታዊ ይዘትም በዋናው ጉዳይ ላይ ተጠሪ ቀርቦ ባልተከራከረበት ሁኔታ በአፈጻጸም መዝገብ የተጠሪን ያለመከሰስ ከለላ በመጥቅስ ዋናውን ውሳኔ ውድቅ ማድረግ ሥነ ሥርዓታዊና የሕግ የበላይነት እንዲሁም አመልካች እንደ ዜጋ ፍትህ የማግኘት መብት ያላቸው መሆኑን ያላገናዘበ ነው በማለት መከራከራቸውን የሚያሳይ ነው፡፡አቤቱታው ተመርምሮም በዚህ ችሎት እንዲታይ በመደረጉ ለተጠሪ ጥሪ ተደርጎለት ባለመቅረቡ በጽሑፍ መልስ መስጠቱ ታልፏል፡፡

 

የጉዳዩ አመጣጥ አጠር አጠር ባለመልኩ ከላይ የተገለፀው ሲሆን ይህ ችሎት ጉዳዩን ከበታች ፍርድ ቤቶች ውሳኔ እና አግባብነት ካላቸው ድንጋጌዎች ጋር በማገናዘብ እንደሚከተለው መርምሮታል፡፡

 

በመሰረቱ በአመልካችና በተጠሪ መካከል የተነሳው ግንኙነት የቅጥር ውልን መሰረት  ያደረገ ሲሆን ዋናው ክርክር በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አግባብ ታይቶ ዳኝነት ማግኘቱን የክርክሩ ሂደት ያሳያል፡፡ የተለያዩ ዓይነት በቅጥር ላይ የተመሰረቱ የስራ ግንኙነቶች የሚኖሩ ሲሆን ግንኙነቶቹ የሚገዙበት የሕግ አግባብም ይለያያል፡፡ አዋጅ ቁጥር 377/1996 ተፈፃሚ የማይሆንባቸው ግንኙነቶች ያሉ ሲሆን ከነዚህ ውስጥ ይህ አዋጅ በየትኞቹ ላይ ተፈጻሚነት ሊኖረው እንደሚችል በዋነኝነት የሚመራው የአዋጁን የተፈጻሚነት ወሰን የደነገገው አንቀጽ 3 ነው፡፡ለዚህ ጉዳይ ቀጥተኛ አግባብነት ያለው የአንቀጹ ድንጋጌ በንዑስ ቁጥር ሶስት በፊደል "ሀ" ስር የተመለከተው ሲሆን በዚህ ንዑስ ድንጋጌ ስር የስራ ግንኙነቱ በንዑስ አንቀጽ ሁለት ስር የሚወድቁ ባለመሆናቸዉ በአዋጁ አንቀጽ 1 መሰረት በቀጥታ ሊፈጸምባቸው የሚችል ቢሆንም በንኡስ አንቀጽ 3 ስር በተገለጹት ሁኔታዎች መሰረት ከአዋጁ ሽፋን ውጭ ሊደረጉ የሚችሉ የስራ ግንኙነቶችን የሚመለከት ነው፡፡በዚሁ መሰረት ኢትዮጰያ ውስጥ የሚሰሩ የዲፕሎማቲክ ሚሲዮኖች ወይም አለም አቀፍ ድርጅቶች ከኢትዮጵያውያን ጋር የሚመሰርቱት የስራግንኙነት የሚኒስትሮች ምክር ቤት በሚያወጣው ደንብ መሰረት ወይም ኢትዮጵያ በምትፈርማቸው አለምዓቀፍ ስምምነቶች መሰረት በአዋጁ ሊሸፈኑ እንደማይችሉ ተመልክቷል፡፡በመሆኑም በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጽ 3 ድንጋጌዎች ሲታዩ አዋጁ በአጠቃላይ በአሰሪና ሰራተኛ መካካል በሚቋቋም በቅጥር ላይ በተመሰረተ የስራ ግንኙነት ላይ ተፈጻሚነት የሚኖረው ቢሆንም በአዋጁ


በግልጽ በተደነገጉ ሌላ ህግ በሚገዛቸው ግንኙነቶች ላይ ተፈጻሚነት  እንደማይኖረው ያስገነዝባሉ፡፡ በተጨማሪም አሁንም አዋጁ የሚሸፍናቸው የስራ ግንኙነቶች ሊሆኑ ቢችሉም ነገርግን የሚኒስትሮች ምክርቤት ወይም ኢትዮጵያ የምትፈርማቸው አለምአቀፍ ስምምነቶች በሚወስኑት መሰረት ከአዋጁ ሽፋን ውጭ ሊደረጉ የሚችሉ መሆኑን ተመልክቷል፡፡ከእነዚህ ድንጋጌዎች ይዘትና መንፈስ የምንረዳው ሕግ አውጪው የዲፕሎማቲክ ግንኙነቶችን ስምምነትና ልምድን ለማክበር ሲባል የውጭ ዲፕሎማቲክ ሚስዮኖቹና ኢትዩጵያውን ሠራተኞቻቸው የሚያደርጉት የቅጥር ግኙነት ላይ የአሰሪና ሰራተኛ ሕግ ተፈጻሚ እንዳይሆን ያደረገ መሆኑን ነው፡፡በመሆኑም በሕጉ በተሰጠው ስልጣን መሰረት የሚኒስትሮች ምክር ቤት በሚያወጣው ደንብ ወይም ኢትዩጵያ ከውጭ ድርጅቶች ጋር በምትፈራረምባቸው አለም አቀፍ ስምምነቶች መሰረት አዋጅ ቁጥር 377/1996 ተፈፃሚ እንዳይሆን የሚደረግበት አግባብ መኖሩን ሕግ አውጪ በግልፅ ያስቀመጠው ጉዳይ ነው፡፡የአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጽ 3(3((ሀ)) መሰረታዊ አላማ የውጭ አገር መንግሥታት ተወካዮችን ሉአላዊነት እና አለምአቀፍ ስምምነቶችን ለማክበር ተብሎ ነው ተብሎ የሚታሰብ ሲሆን በተጨባጭ ባለው ሁኔታ ደግሞ የውጪ ዲፕሎማቲክ ሚሲዮኖችና አለም አቀፍ ድርጅቶች ከኢትዩጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር መስሪያ ቤት ጋር ስምምነት ተፈራርመው ይኼው የመንግስት አካል በእነዚህ ተቋሞች ተቀጥረው የሚሰሩት ኢትዩጵያውንን መብትና ጥቅም ለማስከበር የሚያስችል ስርዓት ዘርግቶ በአለም አቀፍ ስምምነቶች በተካተተው አግባብ የተፈጠረው አለመግባብት ሰላማዊ በሆነ መንገድ በማግባባትና በድርድር እንዲፈታ በማድረግ ላይ እንደሚገኝ የሚታወቅ ነው፡፡

 

ወደተያዘው ጉዳይ ስንመለስም አመልካች ክርክር ያቀረቡት ግንኙነቱ በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጽ 3(3(ሀ)) መሰረት ሊገዛ ከማይችል አካል ጋር ነው፡፡ተጠሪ የተባበሩት መንግስታት አካል ሲሆን የተባበሩት መንግስታት ጥቅምና የተለየ  ከለላን በተመለከተ በተደነገገ ስምምነትም በማንኛውም መንግስት ፍርድ ቤቶች ተከሶ መቅረብ የሌለበት መሆኑን በተባበሩት መንግስታት ቻርተር አንቀፅ 105 እንዲሁም ከተባበሩት መንግስታት ጥቅምና የተለየ ከለላን በተመለከተ በተደነገገው ስምምነት አንቀጽ 2(2) እና 3 ስር በግልጽ ተመልክቷል፡፡አመልካች በዚህ ረገድ የሚያቀርቡት ክርክር የሌለ ቢሆንም አሁን አጥብቀው የሚከራከሩት በዋናው ጉዳይ ውሳኔ ከአረፈ በውሳኔው መሰረት ከሚፈጸም በስተቀር የተጠሪ በሕግ ያለው የተለየ ከለላ እንደ አቢይ ምክንያት ተወስዶ አፈፃጸሙ ሊቆም የሚችልበት አግባብ የለም በሚል ነው፡፡በሕግ አግባብ የተሰጠ ፍርድ ዋጋ እንዳይኖረው የሚደረገው የአፈጻጸም ትዕዛዝ ተገቢነት እንደሌለው ከፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 378 ድንጋጌዎች ይዘትና መንፈስ የምንገነዘበው ጉዳይ ነው፡፡በሕግ አግባብ ታይቶ የተሰጠን ውሳኔ በሕጉ አግባብ ማስፈፀም በኢ.ፌ.ዲ.ሪፐብሊክ ሕገ መንግስት አንቀጽ 78(1) እና 79(1) እና (4) ስር የተረጋገጠውንና የተከበረውን የነጻ ፍርድ ቤት መኖርንና የዳኝነት ስልጣን በአግባቡ ተግባራዊ የሚያደርገው እና በሕገ መንግስቱ አንቀጽ 37 ስር የተረጋገጠው የዜጎች ፍትህ የማግኘት መብትም ውጤት ባለው መልኩ ተግባራዊ የሚሆንበት መንገድ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡አፈጻጸም በፍርድ ቤት የተሰጠ ውሳኔ ትርጉም እንዲኖረው የማድረግ ውጤት ያለውና በተገቢው መንገድም መፈፀም ያለበት መሆኑ የሚታወቅ ነው፡፡ይህ ግን ለማንኛውም ጉዳዮች ሁሉ ይሰራል ብሎ ድምዳሜ ላይ መድረስ ተገቢ ያልሆነ ሕጋዊ ውጤት የሚያስከትል መሆኑ እሙን ነው፡፡በእርግጥ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 212 ድንጋጌ ስር በስነ ስርዓት ጉድለት አንድ ፍርድ ውድቅ ሊሆን እንደማይችል የተመለከተ ሲሆን ይህ ግን የሚሰራው የፍትሓ  ብሔር ስነ ስርዓት ሕጉ ተፈፃሚነት ወስንን መሰረት በማድረግ በሌላ አኳኃን እንዲፈፀም በሕግ


ባልተደነገገበት ሁኔታ መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡በመሆኑም ከመነሻውም ኢትዩጵያ በፈረመችው አለም አቀፍ ስምምነት መሰረት በኢትዩጵያ ፍርድ ቤቶች ላለመዳኘት ነገር ግን ከኢትዩጵያ ዜጎች ጋር ለመሰረተው ግንኙነት በሌላ አግባብ ጉዳዩን ለመጨረስ የሚያስችል ስርዓት ያለው ወገን በዋናው ክርክር ጊዜ ቀርቦ ባለመከራከሩና በይግባኝ ጉዳዩን ባለማሳረሙ ምክንያት ብቻ ስልጣን የሌለው ፍርድ ቤት የሰጠውን ውሳኔ እንዲፈጽም የሚገደድበት አግባብ የለም፡፡ስለዚህ ከዚህ ጉዳይ የተለየ ባሕርይ ስንነሳ የፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 212 እና 4 ድንጋጌዎች አንድ ላይ ተጣምረው ሲታዩ አፈፃጸሙ ዋጋ ያለውን ፍርድ መሰረት ያደረገ ነው፣ጉዳዩ ከስነ ስርዓት ጉድለት ጋር የተያያዘ ነው ለማለት የሚቻል ሁኖ አላገኘነም፡፡ተጠሪ በሕግ የተጠበቀለት የከለላ መብትና ጥቅም እያለው ስልጣን የሌለው ፍርድ ቤት የሰጠውን ውሳኔ እንዲፈጽም ማድረግ ሕግ አውጪው የዲፕሎማቲክ ግንኙነቶችን ልምድን ለማክበር ሲባል በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጽ 3(3(ሀ)) ስር ያስቀመጠውን ድንጋጌ  ዋጋ የሚያሳጣው እና በዲፕሎማቲክ ግንኙነቱም አሉታዊ ውጤት የሚያስከትል በመሆኑ ተመራጭ ሁኖ አላገኘነውም፡፡ሲጠቃለልም የጉዳዩ ልዩ ባህርይ ሲታይ የፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 212 ድንጋጌን ጠቅሶ አፈፃጸሙን ማስቀጠል የሚቻልበት አግባብ ስለሌለና አመልካችም እንደዜጋ መንግስት በውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር መስሪያ ቤት በኩል በዘረጋው ስርዓት መሰረት መብትና ጥቅማቸውን የሚያስከበሩበት ሁኔታ ያለ በመሆኑ የሕግ የበላይነት አልተከበረም፣ የዜጋ ፍትህ የማግኘት ሕገ መንግስታዊ መብት ተጥሷል ለማለት ስላልተቻለ የክልሉ ፍርድ ቤቶች የሰጡት ውሳኔ መሰረታዊ የሆነ የሕግ ስህተት የለበትም በማለት ተከታዩን ወስናል፡፡

 

 ው ሣኔ

 

1.  በኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት በመ/ቁጥር

163639 ታህሳስ 07 ቀን 2006 ዓ/ም የበታች ፍርድ ቤቶችን ትዕዛዝ በማፅናት የተሰጠው ውሳኔ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 348(1) መሰረት ፀንቷል፡፡

2. የአመልካች የአፈጻጸም ክስ መዘጋቱ ተገቢ ነው ብለናል፡፡አመልካች አለኝ የሚሉትን መብትና ጥቅም በሌላ አግባብ ከመጠየቅ ይህ ውሳኔ አያግዳቸውም ብለናል፡፡

3. በዚህ ችሎት ለተደረገው ክርክር የወጣውን ወጪና ኪሳራ አመልካች የራሳቸውን ይቻሉ ብለናል፡፡

መዝገቡ ተዘግቷል፤ወደ መዝገብ ቤተ ይመለስ ብለናል፡፡

 

የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት::

 

 

 

 

መ/ብ