104351 Civil service dispute Unlawful termination of contract of employment Back payment of salary Amhara region civil service proclamation

Civil service dispute

Unlawful termination of contract of employment

Back payment of salary

Amhara region civil service proclamation no. 171/2009

አንድ የመንግስት ሠራተኛ በአሠሪው የመንግስት መ/ቤት ጥፋት በሆነ ምክንያት የስራ ውሉ ተቋርጦ ቆይቶ በኋላ በፍርድ ሠራተኛው ወደ ስራው ሲመለስ ውሉ ተቋርጦ በቆየበት ጊዜ ያለው ደሞዝ ጭምር ሊከፈለው የሚገባ ስለመሆኑ፣ 

 

የተሻሻለው የአ/ብ/ክ/መ/የመግስት ሠራተኞች አዋጅ ቁጥር 171/2002 አንቀጽ 81/2/፣87/1

 

የሰ//.104351 

ሰኔ 9 ቀን 2007 .ም

ዳኞች፡- አልማው ወሌ

ዓሊ መሐመድ

ሡልጣን አባተማም

ሙስጠፋ አህመድ

ተኽሊት ይመሰል

አመልካች፡- ወ/ት ክምክም እማኛው - የቀረበ የለም

ተጠሪ፡- የደቡብ አቸፈር ወረዳ ሲቪል ሰርቪስ ጽ/ቤት - ዐ/ሕግ ዘላለም ተስፋዬ ቀረቡ

መዝገቡ ተመርምሮ የሚከተለው ፍርድ ተሰጥቷል፡፡

ፍ  ር  ድ

ጉዳዩ የስራ ቅጥር ውሉ የተሰረዘው አላግባብ ነው ተብሎ ወደ ስራው እንዲመለስ የተወሰነ የሲቪል ሰርቪስ ሰራተኛ ውዝፍ ደመወዝ ክፍያ ጥያቄን የሚመለከት ክርክር ሲሆን የጉዳዩን አመጣጥ በተመለከተ፡-አመልካች በደቡብ አቸፈር ገ/ኢ/ል/ጽ/ቤት በ10/02/2004 ዓ.ም ተቀጥረው ሲያገለግሉ ከቆዩ በኃላ በቅጥር ውድድሩ ጊዜ ያቀረቡት የስራ ልምድ ማስረጃ ለተቀጠሩበት ፕሳ-3 የስራ ደረጃ የሚጠየቀውን አግባብነት ያለው የስምንት ዓመት የስራ ልምድ መስፈርት የሚያሟላ አይደለም በሚል የክልሉ ሲቪል ሰርቪስ ቢሮ በ04/12/2004 ዓ.ም. የአመልካችን ቅጥር መሰረዙን፣አመልካች በዚህ የስረዛ ውሳኔ ቅር ተሰኝተው ለክልሉ ሲቪል ሰርቪስ ቢሮ የአስተዳደር ፍርድ ቤት ያቀረቡት ይግባኝ ተቀባይነት ማጣቱን፣ ይግባኙ ቀጥሎ የቀረበለት የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ቅጥሩን የሰረዘው የክልሉ ሲቪል ሰርቪስ ቢሮ መጥሪያ ደርሶት መልስ ባለማቅረቡ በሌለበት ጉዳዩን  መርምሮ  ቅጥሩ ከተፈጸመ ከዘጠኝ ወራት በኃላ ቢሮው የቅጥር ፎርማሊቲ አልተሟላም በሚል ምክንያት ቅጥሩን በመሰረዝ የወሰደው እርምጃ ከክልሉ አዋጅ ቁጥር 171/2002 ውጭ መሆኑን፣ አመልካች ያቀረቡት የስራ ልምድ ማስረጃ ሀሰተኛ ነው ያልተባለ በመሆኑ በአዋጁ አንቀጽ 23 የተመለከተው ድንጋጌም ለጉዳዩ አግባብነት የሌለው መሆኑን ገልጾ ውሳኔውን በመሻር አመልካች ወደ ስራቸው እንዲመለሱ ውሳኔ መስጠቱን የመዝገቡ ግልባጭ ያመለክታል፡፡

ይዘቱ ከላይ የተመለከተው የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ይግባኝ ሰሚ ችሎት ውሳኔ መሰረታዊ የሕግ ስህተት የተፈጸመበት በመሆኑ ሊታረም ይገባል በማለት አቤቱታቸውን ለጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ሰበር ችሎት ያቀረቡት አመልካቿ ሲሆኑ የአቤቱታቸው ይዘትም ቅጥሩ የተሰረዘው ከሕግ አግባብ ውጭ መሆኑ ተረጋግጦ ወደ ስራዬ እንድመለስ ተወስኖልኝ እያለ ቅጥሩ ከተሰረዘበት ጊዜ ጀምሮ ወደ ስራ እንድመለስ ውሳኔ እስከተሰጠበት ጊዜ ድረስ ያለው ውዝፍ ደመወዝ እንዲከፈለኝ ሳይወሰን የታለፈው አላግባብ ነው የሚል ነው፡፡ የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ችሎትም የግራ ቀኙን ክርክር ከሰማ በኃላ አመልካች ለሲቪል ሰርቪስ ቢሮ የአስተዳደር ፍርድ ቤት ይግባኝ ባቀረቡበት ጊዜ ያልተከፈላቸው ደመወዝ ጭምር እንዲከፈላቸው አለመጠየቃቸውን፣ ይግባኙ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት የሚቀርበውም በአስተዳደር ፍርድ ቤቱ የተሰጠው ውሳኔ የሕግ ስህተት የተፈጸመበት መሆን አለመሆኑን ለመመርመር ብቻ መሆኑን እና በዚህም ምክንያት ለአስተዳደር ፍርድ ቤት በቀረበው የይግባኝ ቅሬታ ላይ ዳኝነት ያልተጠየቀበትን ጉዳይ የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ይግባኝ ሰሚ ችሎትም ሆነ ሰበር ችሎቱ ተቀብለው ውሳኔ ሊያሳርፉ የሚችሉበት የሕግ አግባብ አለመኖሩን ገልጾ አቤቱታውን ባለመቀበል ውሳኔ ሰጥቷል፡፡አመልካች ለዚህ ችሎት ያቀረቡት አቤቱታ ተመርምሮ አመልካች ለሲቪል ሰርቪስ ቢሮ የአስተዳደር ፍርድ ቤት ባቀረቡት ይግባኝ ቅጥራቸው ፀንቶ እንዲቀጥል ከመጠየቃቸውም በተጨማሪ ለክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ባቀረቡት ይግባኝ ላይ በክርክር ላይ ለነበሩበት ጊዜ ያለው ደመወዝ ይከፈለኝ በማለት ጥያቄ አቅርበው እያለ ዳኝነት አልተጠየቀበትም ተብሎ የውዝፍ ደመወዝ ጥያቄው ውድቅ የመደረጉን አግባብነት ተጠሪው ባለበት ለማጣራት ይቻል ዘንድ ጉዳዩ ለሰበር ክርክር እንዲቀርብ በመደረጉ ግራ ቀኙ የጽሁፍ ክርክር ተለዋውጠዋል፡፡ የጉዳዩ አመጣጥ እና የክርክሩ ይዘት ከላይ የተመለከተው ሲሆን እኛም በክርክሩ እልባት ማግኘት የሚገባቸው፡-

1.    አመልካች ለክልሉ የሲቪል ሰርቪስ ቢሮ የአስተዳደር ፍርድ ቤት ይግባኝ ባቀረቡበት ጊዜ ያልተከፈላቸው ደመወዝ ጭምር እንዲከፈላቸው ያቀረቡት የዳኝነት ጥያቄ የለም በማለት በክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ችሎት የተሰጠው ውሳኔ  የመዝገቡን ግልባጭ መሰረት ያደረገ ነው ወይስ አይደለም?

2.    ቅጥራቸው ከተሰረዘበት ቀን ጀምሮ ወደስራቸው እንዲመለሱ ውሳኔ እስከተሰጠበት ቀን ድረስ ያለው የአመልካች ደመወዝ ሊከፈላቸው የማይችልበት ሕጋዊ ምክንያት አለ ወይስ የለም?

የሚሉ ነጥቦች መሆናቸውን በመገንዘብ  አቤቱታ የቀረበበት ውሳኔ መሰረታዊ የሕግ ስህተት የተፈጸመበት መሆን አለመሆኑን ከእነዚሁ ነጥቦች አንፃር መርምረናል፡፡

በዚህም መሰረት የመጀመሪያውን ነጥብ በተመለከተ ቀደም ሲል እንደተገለጸው ቅጥሩ አላግባብ ከተሰረዘበት ቀን ጀምሮ ወደ ስራ እንዲመለስ ውሳኔ እስከተሰጠበት ቀን ድረስ ያለው ደመወዝ እንዲከፈለኝ ያቀረብኩትን ጥያቄ የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ያለፈብኝ አላግባብ ነው በማለት አመልካች ያቀረቡትን አቤቱታ የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ሰበር ችሎት ሳይቀበል የቀረው ደመወዙ ሊከፈል የማይችልበት ሕጋዊ ምክንያት መኖሩን መሰረት በማድረግ ሳይሆን ይልቁንም አመልካች ለክልሉ የሲቪል ሰርቪስ ቢሮ የአስተዳደር ፍርድ ቤት ይግባኝ ባቀረቡበት ጊዜ ያልተከፈላቸው ደመወዝ እንዲከፈላቸው ጭምር ያቀረቡት የዳኝነት ጥያቄ የለም በማለት መሆኑን የውሳኔው ይዘት ያመለክታል፡፡ ይሁን እንጂ አመልካች ቅጥሩ የተሰረዘባቸው አላግባብ መሆኑን ገልጸው ወደ ስራቸው እንዲመለሱ እንዲወሰንላቸው ካቀረቡት ጥያቄ በተጨማሪ ቅጥራቸው ከተሰረዘበት ጊዜ ጀምሮ ያለው ደመወዝ እንዲከፈላቸው ጭምር ለክልሉ የሲቪል ሰርቪስ ቢሮ የአስተዳደር ፍርድ ቤት በ24/12/2004 ዓ.ም አዘጋጅተው ባቀረቡት የይግባኝ ማመልከቻ በተራ ቁጥር ስምንት ላይ ጠቅሰው መጠየቃቸውን እና ለክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በ19/02/2005 ዓ.ም አዘጋጅተው ባቀረቡት የይግባኝ ማመልከቻ በተራ ቁጥር አስራ ሁለት ላይም ተመሳሳይ ዳኝነት መጠየቃቸውን በመግለጽ ለዚህ ችሎት ባቀረቡት የሰበር አቤቱታ ላይ ላቀረቡት ክርክር ተጠሪው በመልሱ የሰጠው ግልጽ ማስተባበያ ካለመኖሩም በላይ በአጣሪው ችሎት በኩል ከዚህ መዝገብ ጋር እንዲያያዙ የተደረጉት ለአስተዳደር ፍርድ ቤቱ እና ለጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ይግባኝ ሰሚ ችሎት የቀረቡት የሁለቱ የይግባኝ ማመልከቻዎች ይዘትም የአመልካቿን የክርክር ነጥብ የሚያረጋግጥ መሆኑን ተገንዝበናል፡፡ በመሆኑም አመልካች ለክልሉ የሲቪል ሰርቪስ ቢሮ የአስተዳደር ፍርድ ቤት ይግባኝ ባቀረቡበት ጊዜ ያልተከፈላቸው ደመወዝ እንዲከፈላቸው ጭምር ያቀረቡት የዳኝነት ጥያቄ የለም በማለት በክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ችሎት የተሰጠው ውሳኔ  የመዝገቡን ግልባጭ መሰረት ያደረገ ነው ለማለት የሚቻል ሆኖ አልተገኘም፡፡

ሁለተኛውን ነጥብ በተመለከተ ከላይ በመጀመሪያው ጭብጥ ትችት ላይ እንደተገለጸው አመልካች ቅጥሩ የተሰረዘባቸው አላግባብ መሆኑን ገልጸው ወደ ስራቸው እንዲመለሱ እንዲወሰንላቸው ካቀረቡት ጥያቄ በተጨማሪ ቅጥራቸው ከተሰረዘበት ጊዜ ጀምሮ ያለው ደመወዝ እንዲከፈላቸው ጭምር በአስተዳደር ፍርድ ቤትም ሆነ በጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ይግባኝ ሰሚ ችሎት ዳኝነት መጠየቃቸው የተረጋገጠ ሲሆን የአስተዳደር ፍርድ ቤት ውሳኔን ሽሮ ቅጥሩ የተሰረዘው አላግባብ መሆኑን በመግለጽ አመልካች ወደ ስራቸው እንዲመለሱ ውሳኔ የሰጠው የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ይግባኝ ሰሚ ችሎት አመልካች ቅጥራቸው ከተሰረዘበት ጊዜ ጀምሮ ያለው ደመወዝ እንዲከፈላቸው ጥያቄ አቅርበው የነበረ ስለመሆኑም ሆነ ጥያቄውን አቅርበው ነበረ ከተባለም ውሳኔ ሳያሳርፍበት የቀረው በምን ምክንያት እንደሆነ በውሳኔው ላይ የገለጸው ነገር አለመኖሩን ከውሳኔው ይዘት ተገንዝበናል፡፡ተጠሪ በዚህ ሰበር ችሎት በሰጠው መልስ የስራ ቅጥሩ የተሰረዘበት ሰራተኛ በፍርድ ቤት ወደ ስራው እንዲመለስ ቢወሰንለት ቅጥሩ ከተሰረዘበት ጊዜ ጀምሮ ያለው ደመወዝ ሊከፈለው የሚገባ ስለመሆኑ በተሻሻለው የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ሠራተኞች አዋጅ ቁጥር 171/2002 ላይ የተደነገገ ነገር አለመኖሩ ሕግ አውጭው የዚህ ዓይነቱ ውዝፍ ደመወዝ እንዳይከፈል መፈለጉን የሚያሳይ ነው በማለት ተከራክሯል፡፡ እንደተባለው ቅጥሩ ለተሰረዘበት እና በፍርድ ቤት ውሳኔ ወደ ስራው እንዲመለስ ለተወሰነለት ሰራተኛ ውዝፍ ደመወዝ ሊከፈል የሚገባ ስለመሆኑ በአዋጁ በግልጽ የተቀመጠ ፈቃጅ ድንጋጌ የሌለ ሲሆን በአንጻሩ የዚህ ዓይነቱ ደመወዝ ሊከፈል የማይገባው ስለመሆኑም በአዋጁ በግልጽ የተቀመጠ ከልካይ ድንጋጌም የለም፡፡ይልቁንም ከዲሲፕሊን ጉዳዮች ጋር በተያያዘ ሁኔታ የመንግስት ሰራተኛው የተላለፈበት ውሳኔ በይግባኝ ከተሻሻለለት ወይም ከተሰረዘለት ውሳኔው ከተላለፈበት ጊዜ ጀምሮ ሳይከፈለው የቀረው ደመወዝ ታስቦ ያለወለድ የሚከፈለው ስለመሆኑ በአዋጁ አንቀጽ 81 (2) ስር የተመለከተው ድንጋጌ የሠራተኛው የስራ ውል ተቋርጦ የቆየው የሠራተኛው ባልሆነ እና ይልቁንም የመንግስት መስሪያ ቤት በሆነ ጥፋት ምክንያት መሆኑ በፍርድ ተረጋግጦ ሰራተኛው ወደ ስራው እንዲመለስ ሲወሰን የስራ ውሉ ተቋርጦ በቆየበት ጊዜ ያለው ደመወዝ ጭምር ሊከፈለው የሚገባ ስለመሆኑ በአዋጁ ተቀባይነት ያገኘ መርህ መሆኑን መገንዘብ የሚያስችል ነው፡፡ በአዋጁ መሰረት የቅጥር፣ የደረጃ ዕድገት፣ የደመወዝ ጭማሪ ወይም ሌላ ጥቅም የተሰረዘበት የመንግስት ሠራተኛ በማታለል ወይም በማጭበርበር ያገኘው ካልሆነ በቀር የስረዛው እርምጃ እስከተወሰደበት ጊዜ ድረስ የተከፈለውን ደመወዝ እና ጥቅማጥቅሞች እንዲመልስ የማይጠየቅ ስለመሆኑ በአዋጁ አንቀጽ 87 (1) የተመለከተው ድንጋጌም ይህንኑ የሚያጠናክር ነው፡፡ቅጥሩ የተሰረዘበት ሠራተኛ ወደስራው እንዲመለስ በፍርድ ቤት ሲወሰን ውዝፍ ደመወዙ ጭምር እንዲከፈል ሕግ አውጭው አለመፈለጉን አዋጁ ያመለክታል በማለት በደፈናው ከመከራከር በቀር የዚህ ዓይነት ትርጉም የሚሰጠው ወይም የዚህ ዓይነት ግምት ለመውሰድ የሚያስችለው የአዋጁ ድንጋጌ የትኛው እንደሆነ ተጠሪው በግልጽ ለይቶ ያቀረበው ክርክር የለም፡፡በመሆኑም ቅጥራቸው ከተሰረዘበት ቀን ጀምሮ ወደስራቸው እንዲመለሱ ውሳኔ እስከተሰጠበት ቀን ድረስ ያለው የአመልካች ደመወዝ ሊከፈላቸው የማይችልበት ሕጋዊ ምክንያት አልተገኘም፡፡

ሲጠቃለል ከላይ በዝርዝር በተገለጹት ምክንያቶች ቅጥራቸው ከተሰረዘበት ጊዜ ጀምሮ ወደ ስራቸው እስኪመለሱ ደረስ ያለው ደመወዝ እንዲከፈላቸው አመልካች ያቀረቡትን የዳኝነት ጥያቄ በዝምታ በማለፍ የተሰጠው የውሳኔ ክፍል መሰረታዊ የሕግ ስህተት የተፈጸመበት ሆኖ በመገኘቱ የሚከተለው ውሳኔ ተሰጥቷል፡፡

ው  ሳ  ኔ

1.    አመልካች ለክልሉ የሲቪል ሰርቪስ ቢሮ የአስተዳደር ፍርድ ቤት ይግባኝ ባቀረቡበት ጊዜ ያልተከፈላቸው ደመወዝ ጭምር እንዲከፈላቸው ያቀረቡት የዳኝነት ጥያቄ የለም በማለት የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ችሎት በመዝገብ ቁጥር 30581 በ21/09/2006 ዓ.ም. የተሰጠው ውሳኔ  በፍትሐብሔር ስነ ስርዓት ሕግ ቁጥር 348 (1) መሰረት ተሽሯል፡፡

2.    አመልካች ለክልሉ ሲቪል ሰርቪስ ቢሮ የአስተዳደር ፍርድ ቤትም ሆነ ለክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት ባቀረቡት የይግባኝ ማመልከቻ ላይ ቅጥራቸው ከተሰረዘበት ጊዜ ጀምሮ ያለው ደመወዝ እንዲከፈላቸው ጭምር የዳኝነት ጥያቄ አቅርበዋል በማለት ወስነናል፡፡

3.    የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሰሚ ችሎት በመዝገብ ቁጥር 34488 በ05/06/2005 ዓ.ም. የሰጠው ውሳኔ ተሻሽሏል፡፡

4.    በተራ ቁጥር ሶስት ከተጠቀሰው ውሳኔ ውስጥ ቅጥራቸው የተሰረዘው አላግባብ በመሆኑ አመልካች ወደስራ ሊመለሱ ይገባል በማለት የተሰጠው የውሳኔ ክፍል ፀንቷል፡፡

5.    በተራ ቁጥር ሶስት ከተጠቀሰው ውሳኔ ውስጥ ቅጥራቸው ከተሰረዘበት ቀን ጀምሮ ያለው ደመወዝ እንዲከፈላቸው አመልካች ያቀረቡትን የዳኝነት ጥያቄ በዝምታ በማለፍ የተሰጠው የውሳኔ ክፍል ተሽሯል፡፡

6.    ቅጥራቸው ከተሰረዘበት ከ04/12/2004 ዓ.ም. ጀምሮ ወደ ስራቸው እንዲመለሱ እስከተወሰነበት 05/06/2005 ዓ.ም. ድረስ ያለው የአመልካች ደመወዝ ያለወለድ ሊከፈላቸው ይገባል በማለት ወስነናል፡፡

7.    የውሳኔው ግልባጭ በውሳኔው መሰረት ማስፈጸም ያስችለው ዘንድ ለክልሉ ሲቪል ሰርቪስ ቢሮ የአስተዳደር ፍርድ ቤት፣ እንዲያውቁት ደግሞ ለክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት እና አመልካች ለሚሰሩበት የመንግስት መስሪያ ቤት ይላክ፡፡

8.    የሰበር ክርክሩ ያስከተለውን ወጪና ኪሳራ ግራ ቀኙ የየራሳቸውን ይቻሉ፡፡

9.    ውሳኔ ያገኘ ስለሆነ መዝገቡ ተዘግቷል፡፡

 

የማይነበብ የአምስት ዳኞች ፊርማ አለበት፡፡