Fire Arms Administration and Control Draft Proclamation

Amharic

English

መግቢያ 
በሀገራችን በተለይ በገጠሩ አካባቢ የጦር መሳሪያ መታጠቅ በጣም የተለመደ እና በበርካታ የህብረተሰብ ክፍል የሚከናወን ተግባር ሲሆን፣ እንደ አንድ የሀብት አይነትም ይቆጠራል፡፡ ሆኖም የጦር መሳሪያን አላግባብ የመጠቀም ዝንባሌ አልፎ አልፎ የሚታይ ሲሆን በተለይም ፀረ-ሰላም ሀይሎች በህብረተሰቡ ውስጥ የሚገኘውን የጦር መሳሪያ ለሁከትና ብጥብጥ እና መሰል  ህገ-ወጥ ተግባር ሲጠቀሙበት ይስተዋላል፡፡ ስለዚህ ማህበረሰቡ ውስጥ የሚገኘውን የጦር መሳሪያ ማህበረሰቡ ባለቤትነቱን ሳያጣ ግን ደግሞ ህብረተሰቡ አውቆት የህብረተሰቡ የጋራ ንብረት ሆኖ፣ ለህበረተሰቡ የጋራ ሰላምና ደህንነት መጠበቂ እንዲሆን ማድረግ አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ   ይህ አዋጅ  ተዘጋጅቷል፡፡ በመሆኑም ይህ ማብራሪያ  የዚህ የጦር መሳሪያ ቁጥጥር አዋጅ አጭር ማብራሪያ ሲሆን፣ አዋጁ ያስፈለገበትን ምክያት፣ የአዋጁን ቅርፅና አደረጃጀት፣ የአዋጁን ዋናዋና ይዘቶች አጠር አጠር አድርጎ ያብራራል፡፡
 
የአዋጁ አስፈላጊነት
ከላይ እንደተገለፀው በበርካታ የኢትዮጵያ ማህበረሰብ የጦር መሳሪያ እንደ አንድ የንብረት አይነት የሚቆጠር ሲሆን፣ ከህብረተሰቡ ባህልና የአኗኗር ዘይቤ ጋርም ቀጥተኛ ቁርኝት አለው፡፡ ከዚህ በፊት ጠንካራ መንግስታዊና የፀጥታ መዋቅር ያልነበረ በመሆኑ በገጠር አካባቢ የሚኖረው ማህበረሰብ እራሱን ለመጠበቅ እንዲሁም የአርብቶ አደር ማህበረሰብ ከቦታ ቦታ ሲንቀሳቀስ እራሱንና ንብረቱን ከዘረፋ ለመጠበቅ የጦር መሳሪያ የመታጠቅ ልማድ በስፋት ይታያል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በአሁኑ ሰአት በሀገራችን ከፍተኛ የሆነ ህገ-ወጥ የጦር መሳሪያ ዝውውር የሚታይ ሲሆን ነገሩን ይበልጥ የሚያወሳስበው፣ ከሀገራችን የጦርነት ታሪክ እንዲሁም የቀድሞ ስርአት ይከተል ከነበረው የጦርነት ፖሊሲ አንፃር ተገንብቶ የነበረው ግዙፍ ወታደራዊ ሀይልና ከነበረው ስፋት ያለው ትጥቅ እና ይህ መዋቅር  ሲፈርስ ሰፊ የጦር መሳሪያ ወደ ህብረተሰቡ ሊገባ መቻሉ ሲሆን፣ በዚህም ምክንያት ህብረተሰቡ ከሞላ ጎደል በአሁኑ ሰአት የጦር መሳሪያ ባለቤት ሆኗል፡፡ 
 
በህገ-መንግስቱ አንቀፅ 55/2/ሸ/ ላይ የጦር መሳሪያ አያያዝን በተመለከተ የፌዴራል መንግስቱ ህግ እንደሚያወጣ ተመልክቷል፡፡ ሆኖም በወንጀል ህጉ አንቀፅ 481 ላይ በጦር መሳሪያ መነገድን ከሚደነግገው ድንጋጌ ውጪ እስከ አሁን የወጣ ህግ ባለመኖሩ በህብረተሰቡ ውስጥ ያለው መሳሪያ ፀረ-ሰላም ሀይሎች ለህገ-ወጥ ተግባራቸው ሲያውሉት የሚስተዋል ሲሆን፣ ከውጪ ሀገርም ሰፊ ቁጥር ያለው የጦር መሳሪያ በህ-ወጥ መንገድ እየገባ ይገኛል፡፡ የጦር መሳሪያ፣ አያያዝ፣ አጠቃቅ፣ ምርትና ዝውውርም ስርአት ባለው መንገድ እየተመራ አይደለም፡፡  
 
ስለሆነም የጦር መሳሪያ አያያዝ ወይም አጠቃቀም፣ ምርትና ዝውውር በህግ ካልተመራ በሀገራችንና በአካባቢያችን ፀጥታ፣ በህዝብ ደህንነት፣ በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት እንዲሁም የዜጎች በሰላም የመኖር መብት ላይ የሚያስከትለውን ጉዳት ከፍተኛ በመሆኑ ይህንን ጉዳት ለመከላልና ለመቆጣጠር የህግ ስርአት ማበጀት እና ተግባራዊ ማድረግ አስፈላጊ ነው፡፡
 
ከላይ እንደተገለፀው በህብረተሰቡ ውስጥ ያለው የጦር መሳሪያ ከቀድሞው ወታደራዊ መንግስት መፍረስ ጋር ተያይዞ የተበተነ እና በህገወጥ መንገድ በጎረቤት ሀገሮች በኩል የገባ ነው፡፡ የነዚህን የጦር መሳሪያዎች አጠቃቀማቸውንና ዝውውራቸውን በህግ አግባብ መቆጣጠርና ህብረተሰቡ ውስጥ ያለውን የጦር መሳሪያ የህብረተሰቡን ሰላምና ፀጥታ ለማስጠበቅ ተግባር ሊውል ወደሚችልበት ሁኔታ መቀየር አስፈላጊ ነው፡፡ ስለሆነም በህግ ያልተሸፈኑ ጉዳዮችን በዝርዝር ህግ መደንገግ እና ወጥነት ያለው ስርአት መፍጠር አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል፡፡
 
በሌላ በኩል የህገወጥ የጦር መሳሪያ ቁጥጥር አካባቢያዊና አለማቀፋዊ ትብብር ስለሚጠይቅ እንዲሁም ሀገራችን ያፀደቀቻቸውን ህገወጥ የጦር መሳሪያ ቁጥጥርን የሚመለከቱ አለም አቀፍ ስምምነቶች ለማስፈፀም የሚያስችል ስርዓትን መዘርጋት አስፈላጊ በመሆኑ አዋጁ ሊወጣ ችሏል፡፡
የአዋጁ አደረጃጀት
አዋጁ ስድስት ክፍሎች  እና ሰላሳ  አንቀፆች ያሉት  ሲሆን  ክፍል አንድ ስር፣ስለ አጭር ርዕስ፣ ትርጓሜ  እና  የተፈፃሚነት ወሰንን የሚመለከቱ ድንጋጌዎችን የያዘ ሲሆን፣ ክፍል ሁለት የተከለከሉ ተግባራት ምንምን እንደሆኑ በዝርዝር እና የጦር መሳሪያ ፈቃድ የማይሰጣቸው ተቋማት እነማን እንደሆኑ አካቷል፡፡  በክፍል ሶስት ውስጥ የጦር መሳሪያ ፈቃድ የሚሰጥበት ሁኔታ፣ የጦር መሳሪያ ፈቃድ የሚሰጥባቸው መስፈርቶች ፣ በልማድ ለታጠቁ የህብረተሰብ ክፍሎች የጦር መሳሪያ ፈቃድ የሚሰጥበትን ስርአት፣ ስለአለም አቀፍ ድርጅቶችና የውጪ ሀገር ተወካዮች ስለሚሰጥ ፈቃድ፣ የጦር መሳሪያ ፈቃድ ይዘት ፣ የጦር መሳሪያ የውግ ቁጥር፣ ለልዩ ልዩ ተግባር ስለሚሰጥ የጦር መሳሪያ ፈቃድ ስርአት፣ የጦር መሳሪያ ፈቃድ ስለሚታደስበት ስርአት፣ የጦር መሳሪያ ፈቃድ ስለሚታገድበት፣ ስለሚሰረዝበትና ስለሚወረስበት ስርአት፣ ለጦር መሳሪያ ፈቃድና እድሳት የሚከፈል ክፍያን አስመልክቶ እና የጦር መሳሪያ ምዝገባ ስርአት  ምን መምሰል እንዳለበት በዝርዝር ደንግጓ፡፡  በክፍል አራት ላይ ፍቃድ የተሰጠው ሰው ፣ ድርጅቶች  ግዴታዎች ምን ምን እንደሆኑ እና በፍቃድ የተያዘ የጦር መሳሪያ ለሌላ ሰው ሊተላለፍ ስለሚችልበት ሁኔታ ተመልክቷል፡፡  በክፍል  አምስት ላይ ስለ ተቆጣጣሪ ተቋም  ስልጣንና ተግባር እና ስለ ወንጀል ተጠያቂነት የተመለከተ ሲሆን፣ በመጨረሻው ክፍል ማለትም በክፍል ስድስት የመሸጋገሪያ ድንጋጌዎች፣ ስለ መተባበር ግዴታ፣ ለፀጥታ አስከባሪ አካላት የሚፈቀድ የጦር መሳሪያ አይነትና ብዛትን አስመልክቶ፣ የፀጥታ አስከባሪ አካላት የጦር መሳሪያ አጠቃቀም ምን መምሰል እንዳለበት በደንብ እንደሚወሰን እና የመከላከያ ሰራዊት እና ብሔራዊ የመረጃና ደህንነት አገልግሎትን የራሳቸውን የአስራር ስርዓት መዝረጋት እንዳለባቸው  ተደንግጓል፣ ሌላው ደንብና መመሪያ የማውጣት ስልጣን የሚመለከት እና  የተሻሩና ተፈፃሚነት ስለሌላቸው ህጎችና፣ አዋጁ ስለሚፀናበት ጊዜም በዚሁ ክፍል ስር ተመልክቷል፡፡
የአዋጁ ዝርዝር ይዘት
ትርጉም ክፍል ላይ በአዋጁ ውስጥ በተደጋጋሚ የተጠቀምንባቸውን ቃላት ለመተርጎም የተሞከረ ሲሆን፣ ለምሳሌ የጦር መሳሪያ፣ ቀላል የጦር መሳሪያ፣ ትናንሽ የጦር መሳሪያ፣ ሙሉ አውቶማቲክ፣ ግማሽ አውቶማቲክና አውቶማቲክ ያልሆነ የጦር መሳሪያ ምን ማለት እንደሆነ የተተረጎሙ ሲሆን ትርጉሙ ለዚህ አዋጅ በሚመች መልኩ አንዳንዶቹም ከአለማማፍ ትርጉማቸው ለየት ባለመልኩ ለመተርጎም ጥረት ተደርጓል፡፡ የጦር መሳሪያ ባይሆኑም የጦር መሳሪያን ያክል አደገኛ በመሆናቸው አጠቃቃቸውን፣ ስርጭታቸውን እና የአመራረት ሂደቱን መቆጣጠርና በህግ አግባብ መግዛት አስፈላጊ በመሆኑ "ጉዳት ማድረሻ ዕቃዎች"ን በህጉ ውስጥ ለማካተት የተሞከረ ሲሆን፣ በዚሁ መሰረት፣ በስለታማነታቸው ምክንያት ወይም የኤሌክትሪክ ሀይል በመጠቀም ወይም መርዛማ በመሆናቸው በሰው አካልና ህይወት ላይ ከፍተኛ ጉዳት ለማድረስ የሚችሉ እንደ ሳንጃ፣ ገጀራ፣ ጎራዴ፣ ሴንጢና ተመሳሳይ መሳሪያዎችን እንዲሁም  በእጅ የሚያዙ ቴዘር መሳሪያዎች፣ አስለቃሽ ጢስ፣ እና ተመሳሳይነት ያላቸውን ኬሚካሎች ንጉዳት ማድረሻ እቃዎች በሚል ትርጉም ተሰጥቷል፡፡
 
ሌላው ትርጉም የተሰጠው ቃል “ተያያዥነት ያለው እቃ” የሚለው ሲሆን ይህም ማለት የጦር መሳሪያ መያዣ ወይም ማንገቻን ጨምሮ የማንኛውም የጦር መሳሪያ አካል፣ ክፍል፣ መለዋወጫ፣ የጥይት መያዣ መጋዘን፣ እና የጦር መሳሪያውን ለማፅዳትና ለመጠገን የሚያገለግሉ እቃዎችን ይጨምራል በሚል የተተረጎመ ሲሆን፣ መተርጎም ያስፈለገበት ዋናው ምክንያት የጦር መሳሪያው አካል ስለሆነ አብሮ ስርአት እንዲበጅለት ማድረግ አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ነው፡፡
የወግ ቁጥር ማለት የጦር መሳሪያውን ያመረተው ፋብሪካ ቁጥሮች ወይም ቁጥሮችንና ፊደላት በመጠቀም የሚሰጠውና ከጥይት ካዝናው በስተቀር በሁሉም የጦር መሳሪያው አካላት ላይ በቀላሉ ለመልቀቅ በማይችል መልኩ አንድን የጦር መሳሪያ ከሌላ የጦር መሳሪያ ለመለየት የሚያስችል ልዩ ምልክት ነው በሚል ተተርጉሟል፡፡
 
ሌላው በህጉ ውስጥ የተካተተው የተፈፃሚነት ወሰን ሲሆን፣ አዋጁ ህገወጥ የጦር መሳሪያን ለመቆጣጠር ሁሉንም በሀገሪቱ ውስጥ የሚገኙ የጦር መሳሪያ ተጠቃሚዎችን መሸፈኑ አስፈላጊ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት አዋጁ የጦር መሳሪያን በተመለከተ በኢትዮጵያ ውስጥ በሚገኝ ማንኛውም ግለሰብ፣ ድርጅት እንዲሁም ተቋማት ላይ ተፈፃሚ እንዲሆን ተደርጎ የተዘጋጀ ነው፡፡ ሆኖም ካለው ተቋማዊ ባህርይ በመነሳት አዋጁ በመከላከያ ሰራዊት እና በብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ላይ ሙሉ በሙሉ ተፈፃሚ እንዳይሆን የተደረገ ሲሆን፣ እነዚህ ተቋማት  ግን የሚያመርቷቸውን፣ የሚያስመጧቸውን እና የሚጠቀሙባቸውንቸውን የጦር መሳሪያዎች የራቸውንን የቁጥጥር ስርአት ዘርግተው እንዲያስተዳድሩ በአንቀፅ 27 ላይ ሀላፊነት ይጥልባቸዋል፡፡
በክፍል ሁለት ስለ ጦር መሳሪያና አጠቃቀምን የሚመለከቱ ጉዳዮች የተደነገጉ ሲሆን፣ የተከለከሉ ተግባራትን አስመልክቶ በአጠቃላይ አነጋገር ማንኛውም ሰው በዚህ አዋጅ እና በሚሰጠው ፈቃድ መሰረት ካልሆነ በስተቀር የጦር መሳሪያ፣ የጉዳት ማድረሻ እቃ፣ የጦር ሜዳ መነፅር፣ በጦር መሳሪያ ላይ ሊገጠም የሚችል ማንኛውም አይነት መነፅር ወይም የጦር መሳሪያ ሲተኮስ ድምፅ ለማስወገድ የሚያገለግል መሳሪያ ወደ ሀገር ማስገባት፣ ከሀገር ማስወጣት፣ መያዝ፣ ማስቀመጥ፣ ማከማቸት፣ መገልገል፣ ማሳየት፣ መደለል፣ መሸጥ፣ መግዛት፣ ማስተላለፍ፣ ማዘዋወር፣ ማጓጓዝ፣ ማምረት፣ ማሰልጠን፣ መጠገን ወይም ማስወገድ ክልክል ተደርጓል፡፡  ስለዚህ በዚህ ድንጋጌ መሰረት ማንኛውም ሰው የጦር መሳሪያዎችን መያዝን ጨምሮ በድንጋጌው ላይ የተመለከቱ ተግባራትን ለማከናወን ፍቃድ ያስፈልገዋል ማለት ነው፡፡ የህጉ መንፈስ እነዚህ ተግባራት እንዳይከናወኑ ሙሉ ለሙሉ መከልከል ሳይሆን፣ በህግ ስርአት የተፈቀደላቸው አካላት ብቻ እንዲያከናወኑ ማድረግ ነው፡፡ የጉዳት ማድረሻ እቃዎችን ማለትም በአዋጁ ትርጉም ክፍል ላይ እንደተመለከተው በስለታማነታቸው ምክንያት ወይም መርዛማ በመሆናቸው በሰው አካልና ህይወት ላይ ከፍተኛ ጉዳት ለማድረስ የሚችሉ እንደ ሳንጃ፣ ገጀራ፣ ጎራዴ፣ ሴንጢ እና መሰል መሳሪያዎች ማለት ሲሆን፣ አስለቃሽ ጢስ እና መሰል ኬሚካሎችን በተመለከተ፣ እንደሚታወቀው አንዳንዶቹ መሳሪያዎች ህብረተሰቡ የእለት ተእለት ኑሮውን ለማከናወን የተለያዩ ስራዎችን ለመስራት የሚጠቀምባቸው መሳሪያዎች ሲሆኑ፣ በማህበረሰቡም ዘንድ በነዚህ መሳሪያዎች የመገለገል ሁኔታ በጣም የተለመደ ነው፡፡ ስለዚህ በነዚህ እቃዎች መገልገል ለመከልከል አልተፈለገም፡፡ ሆኖም ግለሰቦች በነዚህ እቃዎች ሲገለገሉ፣ ሲያስገቡ ሲሸጡና ወደ ሀገር ሲያስገቡ ወይም ሲያስወጡ ለህብረተሰቡ አደገኛ በሆነ ሁኔታ ከሆነ ተከልክሏል፡፡ ስለዚህ እንዚህን መሳሪዎች ከግል ፍጆታ በዘለለ  በብዛት ወደ ሀገር ማስገባት፣ ከሀገር ማስወጣት፣ በብዛት መያዝ ወይም ማስቀመጥ፣ ማከማቸት፣ መደለል፣ መሸጥ ወይም መግዛት፣ ማዘዋወር፣ ማጓጓዝ፣ ማምረት፣ የተከለከሉ ተግባራት ተደርገዋል፡፡
 
ከዚህም በተጨማሪ የጦር መሳሪያ ላይ ቁጥጥር ለማድረግ የሚቻለው ለእያንዳንዱ የጦር መሳሪያ መለያ ምልክት ወይም ቁጥር በሚታይና ወጥነት ባለው መልኩ ሲኖራቸው መሆኑን በመገንዘብ ማናቸውም የጦር መሳሪያ ወደ ህጋዊ አጠቃቀም ለማስገባት እንደ ቅድመ ሁኔታ ልዩ ምልክት ሊኖረው እንደሚገባ በአስገዳጅነት ተመልክቷል፡፡ ለዚህም ሲባል ወደ ሀገር መገባት የሚችለው በዚህ መልክ ሊለይ የሚችል መለያ ያለው የጦር መሳሪያ ብቻ መሆኑን፣ ተገቢነት የሌለው መለያ ያለው ከሆነ ደግሞ በተቆጣጣሪው አካል መለያ ሊደረግለት እንደሚገባ ተመልክቷል፡፡ ከዚህ ውጪ መለያውን በሙሉ ወይም በከፊል መቀየር፣ ማጥፋት ወይም በማናቸውም አይነት ሁኔታ ተለይተው እንዳይታወቁ ማድረግ፣ ወይም እንደዚህ አይነት የጦር መሳሪያ ወደ ሀገር ማስገባት፣ ከሀገር ማስወጣት፣ መያዝ፣ ማስቀመጥ፣ ማከማቸት፣ መገልገል፣ ማሳየት፣ መደለል፣ መሸጥ፣ መግዛት፣ ማስተላለፍ፣ ማዘዋወር፣ ማጓጓዝ፣ ማምረት፣ ማሰልጠን፣ መጠገን ወይም ማስወገድ የተከለከለ ሆኗል፡፡ የጦር መሳሪያ አጠቃቀምን ለመገደብ ሲባል የጦር መሳሪያን ወይም የጦር መሳሪያን የተመለከተ አገልግሎት እንደ ስልጠናም የሆነ ጥገና ማስተዋወቅ የተከለከለ ነው፡፡
 
ከጦር መሳሪያ የፀዱ አካባቢዎችን በመፍጠር የህብረተሰቡን ስጋ በመቀነስ ደህንነትን ለማረጋገጥ ሲባል የጦር መሳሪያ ለመያዝ የፀና ፍቃድ ያለው ሰውም ቢሆን የጦር መሳሪይ መያዝ የማይችልባቸው ቦታዎች በአዋጁ ተመልክቷል፡፡  እነዚህም፡-

  • ሰላማዊ ሰልፍ ወይም አድማ በሚደረግባቸው ስፍራዎች፣

  • በምርጫ ህግ ወይም በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በሚወሰኑ ስፍራዎች፣ 

  • በሆቴሎች፣ በሲኒማና ትያትር ቤቶች፣ በሙዚየሞችና ተመሳሳይ በሆኑ የህዝብ መዝናኛ ስፍራዎች፣

  • የተኩስ ስፖርት በሚካሄድበት ስፍራ ከተፈቃደ የመወዳደሪያ የጦር መሳሪያ ውጪ በስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች፣

  • በትምህርት ቤቶች፣ በሀይማኖትና እምነት ተቋማት ግቢ ውስጥ ወይም የሀይማኖትና እምነት ተግባራት በሚከናወንባቸው ማንኛውም ስፍራዎች፣ የገበያ ቦታዎች፣

  • በሆስፒታልና ክሊኒኮች፣ በመንግስት መስሪያ ቤቶች እና በሌሎች ተመሳሳይ ለህዘብ አገልግሎት በሚሰጥባቸው ስፍራዎች፣ እና

  • ወደፊት ተቆጣጣሪ ተቋሙ የሚወስናቸው ተመሳሳይ የህዝብ መገልገያ ስፍራዎች ናቸው፡፡

ስለሆነም ማናቸውም ሰው ወደ እነዚህ ህዝብ ሰላማዊ እንቅስቃሴ ብቻ እንዲያደርግ የሚጠበቅባቸው ቦታዎች ወይም ሁሉም ተገልጋይ ከጦር መሳሪያ ነፃ ሆኖ በመግባት በሰላም እንዲገለገልባቸው የሚጠበቁ ተቋማት የጦር መሳሪያ ይዞ እንዳይሄድ ወይም የጦር መሳሪያ ከያዘ በቅድሚያ ለተቋማቱ የጥበቃ ሰራተኞች አስረክቦ መግባት እንዲችል ሆኖ ተቀርጿል፡፡ ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ ግን በስፍራው በስራ ላይ ያሉ ህግ አስከባሪዎች ወይም ተቋማቱን እንዲጠብቁ የተቀጠሩ የጥበቃ ሰራተኞች የተፈቀደላቸውን የጦር መሳሪያ በመያዝ ስራቸውን ለማከናወን እንደሚችሉ ተፈቅዷል፡፡
 
የጦር መሳሪያ ፈቃድ ገደብ የተደረገባቸው ተቋማትም በአዋጁ ተመልክቷል፡፡  እነዚህም የፖለቲካ ፓርቲ፣ የሀይማኖትና የእምነት ተቋም፣ የበጎ አድራጎት ድርጅትና ማህበር፣ እና የትምህርት ተቋም ናቸው፡፡ ሆኖም ተቋማቱን ለመጠበቅ የጦር መሳሪያ አስፈላጊ በመሆኑ ለዚህ አገልግሎት የጦር መሳሪያ ይሰጣቸዋል፡፡ ይህ ማለት በነዚህ ተቋማት ውስጥ ላሉ ግለሰቦች የጦር መሳሪያ እንዲሰጣቸው ተቋማቱ መጠየቅ አይችሉም ማለት ነው እንጂ ተቋማቱን ለመጠበቂያ የሚሆን የጦር መሳሪያ ይጣቸዋል፡፡
 
የጦር መሳሪያ ፈቃድ የሚሰጥበት ሁኔታን በተመለከተ ለግለሰቦችና ለድርጅቶች የሚፈቀደው የጦር መሳሪያ አይነት በህጉ ላይ የተመለከተ ሲሆን፣ የሚሰጣቸውን የጥይት ብዛት ግን በቀጣይ ተቆጣጣሪው ተቋም በሚያወጣው መመሪያ የሚወሰን መሆኑ ተመልክቷል፡፡ መሳሪያውን ለሌላ አካል በፈቃድ ለመስጠት አንዱ መሰፍረት፣ ፍቃድ የተጠየቀበት የጦር መሳሪያ ከዚህ ቀደም በሌላ ሰው ስም ፈቃድ ያልወጣበት መሆኑ አንዱ ሲሆን፣ በሌላ በኩል የፀና ፈቃድ የወጣበት ቢሆንም እንኳንነ ባለፈቃዱ የጦር መሳሪያው ለአመልካቹ ቢሰጥ ፈቃደኛ መሆኑን የሚገልጽ ከሆነ፣  መሳሪያው ለአመልካቹ እንደሚሰጥ ተመልክቷል፡፡ እዚህ ላይ ፍቃድ የወጣበት ቢሆንም፣ ፍቃድ ያወጣበት ግለሰብ ከፈቀደ የሚለው ከላይ እንደገለፅነው በእኛ ሀገር የጦር መሳሪያ እንደ ንብረት ስለሚቆጠር በቤተሰቦች መካከል ያለን የጦር መሳሪያ ከአንዱ ወደ ሌላው ለማስተላለፍ እንዲቻል የህግ መሰረት ለማስያዝ በማሰብ ነው፡፡
 
የጦር መሳሪያ ፈቃድ የሚሰጥባቸው መስፈርቶችን በተመለከተ  ለግለሰብ የጦር መሳሪያ ለመያዝና በህጋዊ መንገድ ለመገልገል ፈቃድ የሚሰጠው ግለሰብ ማሟላት ያለበትን መስፈርት ህጉ በዝርዝር አመልክቷል፡፡ ከነዚህ መስፈርቶች መካከል አንዱ በተቆጣጣሪው ተቋም በሚዘጋጅ ወጥነት ያለው መስፈርት መሰረት የጦር መሳሪያ ለመያዝ በቂ እና አሳማኝ ምክንያት ያለው ስለመሆኑ የታመነበት፣ ሲሆን ነው የሚል ሲሆን፣ ይህ ድንጋጌ ሁለት ነገሮችን ያመለክተናል፡፡ አንዱ የሚመለከተው ተቆጣጣሪ አካል የጦር መሳሪያ የሚሰጥባቸውን መስፈርቶች እንደሚያዘጋጅ የሚያመለክት ሲሆን፣ ሁለተኛው የጦር መሳሪያ እንዲሰጠው የሚጠይቅ አካል የጦር መሳሪያውን የሚታጠቅበት ምክንያት ምን እንደሆነ ማስረዳት ይኖርበታል፡፡ ይህ ማለት ይህ አዋጅ ከመውጣ በፊት ያሉ ሁኔታዎች እንደተጠበቁ ሆነው ይህ አዋጅ ከወጣ በኋላ ግን የጦር መሳሪያ ፍቃድ የሚጠይቁ ሰዎች ምክንያታቸውን ማስረዳት ይኖርባቸዋል፡፡ በመሆኑም የጦር መሳሪያ ትጥቅ ለጠየቀ ሰው ሁሉ የጦር መሳሪያ አይሰጥም ማለት ነው፡፡ የጦር መሳሪያ መታጠቅ ሁሉም ሰው መብት ሳይሆን አስፈላጊ በሆነ ጊዜ ተቆጣጣሪውን ባለስልጣን ሚያሳምን ነገር ሲቀርብና መስፈርቶቹ ሲሟሉ የሚሰጥ ነው፡         
በአዋጁ አንቀፅ 9 ላይ በልማድ የታጠቁ የህብረተሰብ ክፍሎች የጦር መሳሪያ ፈቃድ አሰጣጠን በተመለከተ የተደነገገ ሲሆን፣ ከላይ በአዋጁ አስፈላጊነት ላይ እንደገለፅነው የዚህ አዋጅ አላማ ከዚህ በፊት ታጥቀው የነበሩ የህብረተሰብ ክፍሎችን የጦር መሳሪያ ማስፈታት ሳይሆነ፣ ለነዚህ አካላት ህጋዊ እውና ሰጥቶ የጦር መሳሪያው የህብረተሰቡ የጋራ የጦር መሳሪያ እንዲሆን ማደረግና ህብረተሰቡ በጋራ ሰላምና ደህንነቱን እንዲጠብቅበት ማድረግ ነው፡፡ ስለዚህ በርካታ የሀገራችን አካባቢዎች የሚኖሩ አርሶ አደሮች እና አርብቶ አደሮች ራሳቸውን ለመጠበቅ እና ንብረታቸውን በተለይም ለግጦሽና ውሃ ፍለጋ ከቦታ ቦታ ሲንቀሳቀሱ ከብቶቻቸውን ከዘረፋ እና ከአውሬ ለመጠበቅ የጦር መሳሪያ የመታጠቅ ልማድ አላቸው፡፡ ይህን በመገንዘብ እነዚህ የህብረተሰብ ክፍሎች የታጠቁት የጦር መሳሪያ ያልተከለከለ አይነት እስከሆነ ድረስ በአንድ አመት የሽግግር ጊዜ ውስጥ ተቆጣጣሪው ተቋም በአካባቢያቸው ተገኝቶ በሚያወጣው የጊዜ ሰሌዳ በአካል ቀርበው ፈቃድ መጠየቅና ህጋዊ ማድረግ ይኖርባቸዋል፡፡ አዋጁ እነዚህን የህብረተሰብ ክፍሎች ፈቃድ ጠይቆ ለመውሰድ እንደሚችሉ ፈቃጅ ሆኖ ተቀርጿል፡፡ ሆኖም በጊዜ ገደቡ ውስጥ ፈቃድ ያልወጣበት የጦር መሳሪያ ለተቆጣጣሪው ተቋም ገቢ መደረግ አለበት፣ በቁጥጥር በተገኘም ጊዜ ይወረሳል፡፡ በሌላ በኩል ከሽግግር ጊዜው በኋላ በሂደት በነዚህ አካባቢዎች የሚኖር ሰው የጦር መሳሪያ ፈቃድ ሲጠይቅ እንደማንኛውም የጦር መሳሪያ ፈቃድ ጠያቂ ይስተናገዳል ማለት ነው፡፡
 
ሌላው መብራራት ያለበት ጉዳይ አለም አቀፍ ድርጅቶችና የውጪ ሀገር ተወካዮች ስለሚሰጥ ፈቃድን በተመለከተ ነው፡፡ የአለማቀፍ ድርጅቶች ወይም የውጪ ሀገር ተወካዮች የጦር መሳሪያ ለመጠቀም ፈቃድ የሚሰጣቸው ከውጭ ግንኙነት፣ ከአስፈላጊነት እና ተመሳሳይ ጉዳዮች ያለውን ነገር ከግምት በማስገባት በመሆኑ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስተያየት መቀበል አስፈላጊ ሆኗል፡፡  ለዚህ ምክንያቱ ስለድርጅቶቹ እና ግለቦቹ በቂ መረጃ ያለው የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ስለሆነ ነው፡፡ የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር የሚሰጠው አስተያየት እንደተጠበቀ ሆኖ ተቆጣጣሪው አካል ወይም ተቋም ለነዚህ አካላት የጦር መሳሪያ የሚሰጥበትን  መስፈርት ማውጣት እንዳለበት ተቀምጧል፡፡ ለነዚህ አካላት ፈቃድ የሚሰጥበት የጦር መሳሪያ የተፈቀደው አይነት ሆኖ መሳሪያው ወደ ሀገር ሲገባ መለያውን ይመዘግባል፣ ፈቃዱ ሲያበቃም የጦር መሳሪያው ለተቆጣጣሪው ተቋም ገቢ እንዲሆን ይደርጋል፡፡
 
በአዋጁ ላይ ለልዩ ልዩ ተግባር ስለሚሰጥ የጦር መሳሪያን አስመልክቶ የተደነገገ ሲሆን፣ ለልዩ ልዩ ተግባር የሚሰጥ መሳሪያ ማለት ለስፖርት ውድድር የሚሰጥ ሽጉጥ ወይም ግማሽ አውቶማቲክ ጠመንጃ፣ ህጋዊ የእንስሳት አደን ለሚያድኑ ወይም ለሚያሳድኑ ሰዎች የሚሰጥ የጦር መሳሪያ፣ ለቲያትርና ፊልም ስራ እንዲሁም በኤግዚቢሽን ለማሳየት እና ከተሰሩ ሀምሳ አመት ያለፋቸው የጦር መሳሪያዎችን በቅርስነት ለመያዝ የሚሆን የጦር መሳሪያን የሚያካትት ሲሆን፣ ይህም በምን አግባብ ፈቃድ ሊሰጥ እንደሚችል ህጉ አስቀምጧል፡፡
ሌላው የጦር መሳሪያ ፈቃድ የሚታደስበት ስርአትን በተመለከተ በአዋጁ አንቀፅ 7/3/ መሰረት ለግለሰብ የሚሰጥ ፈቃድ ለሁለት አመት፣ ለድርጅት የሚሰጥ ፈቃድ ደግሞ ለአምስት አመት ፀንቶ እንደሚቆይ ተመልክቷል፡፡ በዚህ ድንጋጌ ላይ የተመለከተው የሁለትትና የአምስት አመት ጊዜ ሲያበቃ፣ ፈቃዱ መታደስ ይኖርበታል፡፡ ስለዚህ የጦር መሳሪያ ፈቃድ የሚታደስበትን ስርአት በተመለከተ በአንቀፅ 14 ላይ የተመለከተ ሲሆን፣ በዚሁ መሰረት የጦር መሳሪያ ፈቃድ የተሰጠው ማንኛውም ሰው የፈቃዱ አገልግሎት ጊዜ ከማብቃቱ ከ60 ቀናት በፊት የእድሳት ጥያቄውን ለተቆጣጣሪው ተቋም ማቅረብ እንዳለበት የተመለከተ ሲሆን፣ ተቆጣጣሪው ተቋምም ጥያቄው በቀረበለት በ60 ቀናት ውስጥ የፈቃድ መስጫ መስፈርቶቹ መሟላታቸውን አረጋግጦ ፈቃዱን እንደሚያድስ፣ ውሳኔ ሳይሰጥ ከዘገየ ግን ፈቃዱ ለጊዜ ውሳኔ እስኪሰጥ ድረስ እንደፀና እንደሚቆይ ተመልክቷል፡፡
በአንቀፅ 15 እና 16 ላይ የጦር መሳሪያ ፈቃድ የሚታገድበት፣ የሚሰረዝበትና የሚወረስበት ሁኔታ በዝርዝር የተመለከተ ሲሆን፣ ፈቃዱ የተሰረዘበት የጦር መሳሪያ እንደሚወረስም እንዲሁ ተደንግጓል፣ እንዲሁም ፈቃዱ በዚህ አዋጅ መሰረት የአገልግሎትና የእድሳት ጊዜው ያበቃ እንደሆነ እና ባለፈቃዱ በቂና አሳማኝ ምክንያት ያለው መሆኑ ካልታወቀ በቀር ፈቃዱ እንደሚወረስ፣ የጦር መሳሪያውም እንደሚወረስ ተደንግጓል፡፡ ሆኖም የጦር መሳሪያው ባለቤት ያላሳደሰበትን በቂ ምክንያት ካቀረበ የማይወረስበት ሁኔታ መኖሩን መገንዘብ ይቻላል፡፡
ሌላው በአዋጁ ከተመለከቱት ጉዳዮች መካከል አንዱ በአንቀፅ 18 ላይ የተመለከተው፣ የጦር መሳሪያ ምዝገባ ስርአትን የሚመለከት ሲሆን፣ ተቆጣጣሪ ተቋም በሀገሪቱ የሚገኙ የጦር መሳሪያዎችን በሙሉ በውግ ቁጥራቸው መሰረት በመረጃ ቴክኖሎጂ ስርአት መዝግቦ እንደሚያስተዳደር ተመልክቷል፡፡ የዚህ ድንጋጌ ዋና አላማ በሀገሪቱ ውስጥ ያሉትን መሳሪያዎች ለማወቅ፣ ለማስተዳደርና ለመቆጣጠር እንዲቻል ማድረግ ነው፡፡
በአንቀፅ 19 ላይ የጦር መሳሪያ ፈቃድ የተሰጠው ሰው ግዴታዎችን በዝርዝር ለማመልከት ተሞክሯል፡፡ እነዚህን ግዴታዎችን ለማስቀመጥ የተመፈለገበት ዋናው ምክንያት ይህ አዋጅ ከወጣ በኋላ በሀገሪቱ ያለው የመሳሪያ አያያዝና አጠቃቀም ሁኔታ በዘፈቀደ ሳይሆን፣ በስርአትና በህግ የሚመራ እንዲሆን በማሰብ ነው፡፡ ስለዚህ ግለሰቦችእነዚህን ግዴታዎች የማክበር ሀላፊነት ያለባቸው ሲሆን፣ እነዚህ ግዴታዎች የማይከበሩ ከሆኑ በህጉ አግባብ ተቆጠጣሪው አካል እርምጃ ይወስዳል ማለት ነው፡፡ 
ሌላው የጦር መሳሪያ ፈቃድ የተሰጠው ድርጅት ግዴታ በአንቀፅ 20 ላይ የተመለከተ ሲሆን፣ በዚህም መሰረት፣ አንድ ድርጅት ድርጅቱን ለመጠበቅ አላማ ፈቃድ ጠይቆ የተሰጠው እንደሆነ የጦር መሳሪያውን ማስታጠቅ ወይም ማስያዝ የሚችለው በራሱ ምዘና አድርጎ በአዋጁ የተመለከቱ መስፈርቶችን የሚያሟላ ሆኖ ለሚያገኘው ወይም ለሚያምነው ሰው ብቻ ይሆናል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ድርጅቱ የጦር መሳሪያው ጥቅም ላይ ሲውል ማን እንደያዘው የሚገልፅ እና የጦር መሳሪያውን የጥበቃ ሰራተኞች በመቀያየር የሚይዙት በሚሆንበት ግዜ ርክክብ የሚፈፀምበት ቋሚ ስርአት መዘርጋትና መጠበቁን ማረጋገጥ፣ የጦር መሳሪያው ለተፈቀደለት አላማ ብቻ ጥቅም ላይ መዋሉን፣ ፈቃድ ካገኘበት የጥይት መጠን በላይ በአንድ ጊዜ አለመያዝ፣ ፍቃዱን ለማግኘት መሰረት የሆኑት ሁኔታዎች እና መረጃዎች ላይ ማንኛውም ለውጥ ሲኖር ለተቆጣጣሪው ተቋም ወዲያውኑ ማሳወቅ፣ ፍቃድ የወሰደበት የጦር መሳሪያ ሲበላሽ፣ ሲጠፋ፤ ሲሰረቅ፣ ሲቀማ፣ የመለያ ምልክቱ ሲደበዝዝ ወይም በማንኛውም ምክንያት ከቁጥጥሩ ውጪ ሲሆን ለተቆጣጣሪው ባለስልጣን ወዲያውኑ ማሳወቅ፣ የፍቃዱ ጊዜ ከማለቁ በፊት የጦር መሳሪያውን በአካል ይዞ በመቅረብ እና ስለ አጠቃቀሙ ሪፖርት በማቅረብ ፈቃዱን ማሳደስ፣ የጦር መሳሪያውን ከሰራተኞቹ ውጪ ለሌላ ሰው በማናቸውም መልኩ አሳልፎ ያለመስጠት፣ ያለማዋስ፣ እንዲጠቀምበት አለማድረግ እና በሌላ ሰው እጅ እንዳይገባ ማድረግ፣ የጦር መሳሪያው ጥቅም ላይ በማይውልበት ወቅት በጥንቃቄ ተጠብቆ እንዲቀመጥ ማድረግ፣ የጦር መሳሪያውን አገልግሎት ያልፈለገ ወይም ፈቃዱ የማይታደስለት እንደሆነ ለተቆጣጣሪ ተቋም የጦር መሳሪያውን መስጠት ወይም በዚህ አዋጅ በተመለከተው መሰረት መስፈርቶችን አሟልቶ ፈቃድ ለሚሰጠው ሰው ማስተላለፍ፣ የጦር መሳሪያ በሚያዝበት እና ጥቅም ላይ በሚያውልበት ወቅት የወጡ የጥንቃቄ ደንቦችን ተግባራዊ ማድረግ ግዴታ እንዳለበት ተመልክቷል፡፡
የጦር መሳሪያ ፈቃድ የሚሰጠው መስፈርት ለሚያማላ እና ለሚታወቅ ሰው ብቻ እንደመሆኑ ይህ ፈቃድ የተሰጠው ሰው የጦር መሳሪያውን ለሌላ ሶስተኛ ወገን ወይም ሰው በማናቸውም መልኩ አሳልፎ እንዲሰጥ አይጠበቅም፡፡ ሆኖም የጦር መሳሪያውን አገልግሎት ሳይፈልገው የቀረ  እንደሆነ ለተቆጣጣሪው ተቋም ማስረከብ አለበት፡፡
ባለፍቃዱ የሞተ እንደሆነ በፍርድ ቤት የመውረስ መብት ያረጋገጠ ወራሽ የጦር መሳሪያው እንዲተላለፍለት ለመጠየቅ ይችላል፣ ሆኖም ወራሹ መስፈርቶችን የማያሟላ እና ፈቃድ ሊሰጠው ያልቻለ ከሆነ መስፈርቶችን ለሚያሟላ ለሌላ ወራሽ እንዲተላለፍለት ሊያደርግ ይችላል፡፡ ይህ እንዲሆን የተፈለገበት ዋናው ምክንያት በማህበረሰቡ ዘንድ የጦር መሳሪያ አንደ አንድ የሀብት አይነት ስለሚቆጠር፣ በቤተሰቦች መካከል የጦር መሳሪያው ልክ እንድ ውርስ ሀብት ተቆጥሮ የሚወረስበትን ስርአት ለመፍጠር ስለተፈለገ ነው፡፡ ሆኖም የጦር መሳሪያውን የሚወረስ አካል መስፈርቶቹን መሟላት ይኖርበታል፡፡ የመውረስ ስርአቱም የሚከናወነው ይህንን ስራ እንዲሰራ ሀላፊነት የተሰጠው ተቆጣጣሪው አካል ነው፡፡ ስለዚህ  በቤተሰቦች መካከል የሚደረገውን የጦር መሳሪያ ዝውውር በህግና በስርአት እንዲመራ ለማድረግም ያግዛል ማለት ነው፡፡
 
ተቆጣጣሪው አካልን በተመለከተ በአዋጁ አንቀፅ 2/1/  ትርጉም ክፍል ላይ ፌዴራል ፖሊስ መሆኑ የተመለከተ ሲሆን፣ ራሱን የቻለ  ብሔራዊ የጦር መሳሪያ ቁጥጥር የስራ ክፍል አደራጅቶ የጦር ፣መሳሪያን በተመለከተ በሀላፊነት እንዲመራ ተወስኗል፡፡ በመሆኑም ተቆጣጣሪው አካል ከፌዴራል ጀምሮ እስከ ክልል ድረሰ ያለውን የጦር መሳሪያ፣ አያያዝ፣ አጠቃቀም፣ ስርጭትና የማምረት ሂደት የመምራት ሀላፊነት የተሰጠው ሲሆን፣ ተደራሽነትን በተመለከተ ህብረተሰቡ ይህን አገልግሎት በአካባቢው እንዲያገኝ ከማድረግ አንፃር አንድም አግባብ ነው ብሎ እስከ አመነው የሀገሪቱ አደረጃጀት  ደረስ በመውረድ ፅህፈት ቤት በመክፈት አገልግሎቱን ሊሰጥ ይችላል፣ ካልሆነም አግባብ ነው ብሎ ላመነው አካል ውክልና በመስጠት አግልግሎቱን ሊሰጥ ይችላል፡፡
ዋናው ጉዳይ ይህ አካል የጦር መሳሪያ አያያዝ፣ አጠቃቀም፣ ስርጭትና ምርትን በተመለከተ ስርአት የማስያዝ ሀላፊነት የተሰጠው ሲሆን፣ በተለይም  በሀገሪቱ ውስጥ የሚገኙ የጦር መሳሪዎችን በሙሉ በመረጃ ቴክኖሎጂ ታግዞ መመዝገብ፣ የጦር መሳሪያ ለመጠቀም ፈቃድ መስጠትና ህገወጥ የጦር መሳሪያ አጠቃቀምን የመቆጣጠር፣ ጉዳት ማድረሻ ዕቃዎች ወደ ሀገር ማስገባት፣ ማምረት፣ ማዘዋወር፣ ማከማቸት፣ መሸጥ ብቃት ማረጋገጫ ደረጃዎችን አውጥቶ ፈቃድ መስጠት፣ መቆጣጠር፣ ፈቃድ የሰጠበት ቅድመ ሁኔታ ተለውጧል ብሎ ሲያምን የሰጠውን ፈቃድ ማገድ፣ መሰረዝ፣ ለህዝብ ሰላምና ደህንነት አስጊ ሆኖ የተገኘን ማንኛውንም ፍቃድ ያለውንም ሆነ ህገወጥ የጦር መሳሪያ የታጠቀን ሰው የማስፈታትና የመውረስ፣ በህገወጥ መንገድ የተያዘን የጦር መሳሪያ በጥናት በመለየትና ከህብረተሰቡ ጋር በመተባበርና በመተማመን ወደ ህጋዊ ስርአት ማስገባት ወይም ማስፈታትና መውረስ፣ በፍርድ ቤት ትእዛዝ በመንግስት እንዲወረስ ውሳኔ የተሰጠበትን፣ ፈቃድ የሌለውን፣ ባለቤቱ ያልታወቀ ወይም አገልግሎት ሊሰጥ የማይችልን የጦር መሳሪያ መውረስ፣ መወገድ ያለባቸውን ማስወገድና ጥቅም ሊሰጡ የሚችሉትን ጥቅም ላይ እንዲውሉ ማድረግ፣ የጦር መሳሪያዎችን ከውጪ ሀገር ማስገባት፣ ከሀገር ማስወጣት፣ መያዝ፣ በጥንቃቄ ማከማቸት፣ ማዘዋወር፣ ማስተላለፍ፣ ከሃገር ውስጥ መግዛት፣ መሸጥ፣ ስለአጠቃቀም ማሰልጠን፣ መጠገንና ማስወገድ፣ የጦር መሳሪያ ቁጥጥርን የሚመለከቱ ጥናትና ምርምሮችን ማድረግ፣ የጦር መሳሪያን ጎጂነት እና ህጋዊ አጠቃቀም በተመለከተ የህብረተሰቡን ግንዛቤ ሊያሳድጉ የሚችሉ ተግባራትን ማከናወን፣ የጦር መሳሪያን በተመለከተ አካባያዊና አለም አቀፍ ትብብር ማድረግ፣ ተጠሪ ተቋም ሆኖ ማገልገል፣ ለሚሰጠው አገልግሎት ተመጣጣኝ ክፍያ ማስከፈል፣ እና እንደ አስፈላጊነቱ የተሰጠውን ሀላፊነት እንዲያከናውኑለት ለክልል ፖሊስ ኮሚሽኖች ውክልና መስጠት፣ በሚዘረጋው ስርአት መሰረት አፈፃፀማቸውን የመከታተላልእና መቆጣጠር ሀላፊነት አለበት፡፡
የወንጀል ተጠያቂነትን በተመለከተ  በ1996 ዓ.ም የወጣው የወንጀል ህግ አንቀፅ 481 ላይ በጦር መሳሪያ መነገድን አስመልክቶ የወንጀል ድንጋጌ ያለው ሲሆን፣ ይህን የወንጀል ህግ ማሻሻል ወይም መሻር አስፈላጊ ስላልሆነ፣ የአዋጁን የወንጀል ድንጋጌዎች ከወንጀል ህጉ ጋር ተናባቢ እንዲሆኑ ተደርጓል፡፡ ስለዚህ የወንጀል ህጉ አንቀፅ 481 ለአዋጁም ተፈፃሚ እንዲሆን የተደረገ ሲሆን፣ ሌሎች በወንጀል ህጉ ያልተሸፈኑ የወንጀል ድንጋጌዎች  በአዋጁ አንቀፅ 23 ላይ የተመለከቱ ሲሆን የእስራትና የገንዘብ ቅጣቱም የወንጀል ህግ የቅጣት ድንጋጌዎቸን አረቃቀቅ መርህ በመከተል ለጥፋቱ ተመጣጣኝ የሆነ የእስራትና የገንዘብ መቀጮ ተቀምጧል፡፡ በዚህ አንቀፅ ንዑስ አንቀፅ 2 ላይ የተመለከተው ብዛት በሌለው አኳኋን ሲፈጸም ሲሆን፣ በንዑስ አንቀፅ 3 ላይ የተመለከተው ድርጊቱ ብዛት ባለው ሁኔታ ሲፈጸም ነው፡፡ ብዛት ያለው ማለት ምን ማለት እንደሆነ በትርጉም ክፍል ላይ ትርጓሜ ተሰጥቶታል፡፡ የጉዳት ማድረሻ መሳሪያዎችን በተመለከተ ለግል ፍጆታ በሚሆን መልኩ መገልገል፣ መሸጥ፣ መግዛት ወዘተ በወንጀል ተጠያቂ አያደርግም፡፡ ሆኖም እነዚህን መሳሪያዎች ለህብረተሰቡ አስጊ በመሆነ አግባብ በብዛት መገልገል፣ መሸጥ፣ማስቀመጥ ወዘተ የወንጀል ተጠያቂነትን ያስከትላል፡፡
የችግሩን አስከፊነት ከግምት ውስጥ በማስገባት የጦር መሳሪያ ማዘዋወር ተግባሩ የተፈጸመው በተሸከርካሪ አማካኝነት ከሆነ ተሸከርካሪው በጉምሩክ ኮሚሽን ውሳኔ እንደሚወረስ ተመልክቷል፡፡
ሌላው የመሸጋገሪያ ድንጋጌዎችን የሚመለከት ሲሆን፣ አዋጅ ሙሉ ለሙሉ ተግባራዊ የሚሆንበት አንድ  አመት የሽግግር ጊዜ ተሰጥቷል፡፡ በዚህም መሰረት አስቀድሞ ተመዝገበው ወይም ፍቃድ ተሰጥቷቸው የነበሩ የጦር መሳሪያ የመያዝና የመጠቀም ፍቃዶች በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ ተቆጣጣሪው ተቋም በሚያወጣው የጊዜ ሰሌዳ በአካል ቀርበው ድጋሚ ፍቃድ መጠየቅ እና በዚህ አዋጅ መሰረት የተመለከቱ መስፈርቶችን አሟልተው ወይም የሚያሟሉ ከሆነ በተቆጣጣሪ ተቋሙ ፈቃድ መውሰድ ይኖርባቸዋል፡፡
አስቀድሞ ሳይመዘገቡ ወይም ፍቃድ ሳይሰጣቸው የጦር መሳሪያ የያዙ ወይም የሚጠቀሙ ሰዎች በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ ተቆጣጣሪው ተቋም በሚያወጣው የጊዜ ሰሌዳ መሰረት በአካል ቀርበው ፈቃድ መጠየቅ እና በዚህ አዋጅ መሰረት የተመለከቱ መስፈርቶችን የሚያሟሉ ከሆነ ፈቃድ መውሰድ ይኖርባቸዋል፡፡ የዚህ ድንጋጌ አላማ ህብረተሰቡ በእጁ ያለውን የጦር መሳሪያ ህጋዊ እንዲያደርግ ለማድረግ ነው፡፡ ሆኖም መስፈርቶች አሟልተው ፈቃድ ማግኘት ካልቻሉ ግን በይዞታቸው ያለን የጦር መሳሪያ ማስረከብ ይኖርባቸዋል፡፡ ከሽግግር ጊዜው በኋላ ፈቃድ የሌለው የጦር መሳሪያ ይዘው ከተገኙ ግን ህጋዊ ተጠያቂነት ያስከትላል ማለት ነው፡፡
የአዋጁ አላማ በሀገሪቱ ያለውን የጦር መሳሪያ በጠቅላላ ወደ ህጋዊ ማእቀፍ ማስገባ በመሆኑ ህብረተሰቡ የታጠቋቸውን የጦር መሳሪያዎች በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ በዚህ አዋጅ መሰረት ለተቆጣጣሪው ተቋም ያየማስመዝገብ ግዴታ የተጣለባቸው ሲሆን፣ ከተፈቀደላቸው አይነትና መጠን በላይ ሆነው የሚገኙ የጦር መሳሪያዎችን ተቆጣጣሪው ተቋም ወርሶ ጥቅም ላይ እንዲውሉ ወይም እንዲወገዱ ያደርጋል፡፡
ሌላው በአንቀፅ 26 ላይ ለፀጥታ አስከባሪ አካላት የሚፈቀድ የጦር መሳሪያ አይነትና ብዛትን በተመለከተ የሚኒስትሮች ምክር ቤት በሚያወጣው ደንብ እንደሚወሰን ተመልክቷል፡፡ ይህ ማለት የዚህ አዋጅ ዋና አለማ ግለሰቦችን አስመልክቶ የጦር መሳሪያ ስለሚተዳደርበት ስርአት መደንገግ ሲሆን የህግ አስከባሪ አካላትን በተመለከተ ግን በዝርዝር ጥናት ተደርጎ በደንብ መወሰን ይገባዋል፡፡ በፌዴራልና በክልል የሚገኙ የህግ አስከባሪ አካላትን ተልእኮ እና ሌሎች ጉዳዮችን ከግምት ውስጥ በማስገባት የሚኒስትሮች ምክር ቤት በድንብ የሚወስን ይሆናል፡፡
የመከላከያ ሰራዊት እና ብሔራዊ የመረጃና ደህንነት አገልግሎትን በተመለከተ፣ ህጉ ተፈፃሚ እንዳይሆንባቸው ተደርጓል፡፡ ሁለቱ ተቋማት በዚህ ህግ ይገዙ የሚባል ከሆነ የጦር መሳሪያን አስመልክቶ የሚያከናውኑት ተግባር ለሶስተኛ አካላ ግልፅ እንዲሆን ያስገድዳል፡፡ ይህ ደግሞ ተቋማቱ ካላቸው  ሚስጥራዊነት ባህርይ ጋር አብሮ የሚሄድ አይሆንም፡፡ ስለዚህ አዋጂ በነዚህ ሁለት ተቋማት ላይ ተፈፃሚ አይሆንም፡፡ ሆኖም አዋጁ እነዚህ ተቋማት የሚታጠቁትን የጦር መሳሪያ አይነት፣ ብዛት እና የአጠቃቀሙንም ሁኔታ በራሳቸው እንደሚወስኑ ያስቀምጣል፣  ፡ ከዚህ በተጨማሪ በአዋጁ ከተቆጣጣሪው ተቋም ጋር በጋራ አስፈላጊ ሆነው በሚያገኟቸው ጉዳዮች ላይ ተባብረው መስራት እንዳለባቸው ተመልክቷል፡፡ 
የተሸሩ ህጎችን በተመለከተ በወንጀል ህጉ አንቀፅ 808 ላይ የተመለከተው ደንብ መተላለፍ ወንጅል ሲሆን ቅጣቱ በጣም አነስተኛ እና አስተማሪ ያልሆነ እንዲሁም አሁን ያለውን ነባራዊ ሁኔታ ከግምት ውስጥ ያላስገባ በመሆኑ እንዲሻር ተደርጓል፡፡