family law

  • ኚዳኝነት ስራ ጋር ያልተያያዙ እና ዚአስተዳደር ስራ ሲያኚናውኑ ዹሚፈፀሙ ዹወንጀል ጥፋቶቜ ዳኛውን ኚተጠያቂነት ዚማያስቀሩ ስለመሆኑ፣

    ዹወ/ህ/ቁ. 402(1) እና (2)

    በትግራይ ክልል ዳኞቜ እና ሬጂስትራሮቜን ለማስተዳደር ተሻሜሎ ዚወጣው ደንብ ቁጥር 1/2003

    ዹሰ/መ/ቁ. 98283

     

    መስኚሚም 26 ቀን 2007 ዓ.ም

     

    ዳኞቜ፡-አልማው ወሌ

     

    መኮንን ገ/ህይወት ሙስጠፋ አህመድ ተፈሪ ገብሩ ተኞሊት ይመስል

    አመልካቜ፡- አቶ ሐጐስ ገ/ሄር መኮንን

     

    ተጠሪ፡- ዚትግራይ ክልል ዚስነ/ፀ/ሙ/ኮ - ዐ/ሕግ መዝገቡን መርምሹን ተኚታዩን ወስነናል፡፡

     ፍ ርድ

     

    ዹአሁኑ አመልካቜ በወንጀል ህጉ አንቀጜ 407(2) ዹተመለኹተውን በመተላለፍ ዚማይገባውን ብልፅግና ለራሱ ወይም ለሌላ ሰው ለማስገኘት በማሰብ በትግራይ ክልል በደቡብ ዞን አሰላ ወሚዳ ፍ/ቀት ዳኛ ሆኖ ሲሰራ ሥልጣኑን አላግባብ በመጠቀም ዚመንግስት ዹአበል አኹፋፈል ሥርዓት በመጣስ ለራሱና ለሥራ ባልደሚቊቜ ሊኹፈል ዚማይገባውን ብር 7653.4 እንዲኚፈል በማድሚጉ በፈፀመው በሥልጣን ያለአግባብ መጠቀም ወንጀል ተኚሷል ሲል ዹአሁን ተጠሪ  ክስ አቅርቊበታል፡፡

     

    ጉዳዩን በቅድሚያ ዹተመለኹተው ዚአላማጣ ማዕኹላዊ ፍ/ቀት ዚግራ ቀኙን ክርክር እና ማስሚጃ ኹሰማ በኋላ አመልካቜ በተዘዋዋሪ ቜሎት ስም ኚሥራ ቊታዬ ወደ ቀበሌዎቜ ሄጃለው በማለት በተሞክሮ ልውውጥ ስምፀ በመሀበራዊ ፍ/ቀትና ዚመሬት ዳኞቜ ሥልጠና ስም አበል አላግባብ መውሰዱ ፀዳኞቜ ስልጠና ሰጥተዋል በማለት በፔሮል ወደ ቀበሌ እንደወጡ አሰመስሎ አበል መክፈሉ ፀ ዚሂሳብ መደብ በማይፈቅድበት ሁኔታ በራሱ ስም አበል ወጪ በማድሚግ ዚፅሕፈት መሣሪያ መግዛት እና ኚፋይናንስ ደንብ እና መመሪያ ውጭ ስለመስራቱ በራሱ በዝርዝር ዹተመለኹተውን እና ዚቀሚበበትን ዹሰውም ሆነ ዚሰነድ ማስሚጃ ማስተባበል ባለመቻሉ እንደ ክሱ አቀራሚብ ጥፋተኛ ነው በማለት ዚቅጣት ማቅለያ ምክንያቶቜን ተቀብሎ በ1(አንድ) ዓመት ፅኑ እስራት እና በብር 2000 /ሁለት ሺህ /መቀጮ እንዲቀጣ ወስኗል፡፡

     

    ጉዳዩ በይግባኝ ዚቀሚበለት ዹክልሉ ጠቅላይ ፍ/ቀትም ሆነ ዹሰበር አቀቱታ ዚቀሚበለት ዹክልሉ ሰበር ሰሚ ቜሎት ውሳኔው ዚሚነቀፍበት ምክንያት ዹለም በማለት ቅሬታውን ውድቅ አድርገዋል፡፡


    ዹሰበር አቀቱታው ለዚህ ፍ/ቀት ዹቀሹበው ይህን ውሳኔ በመቃወም ነው፡፡ አመልካቹ ዚካቲት 24 ቀን 2ዐዐ6 ዓ.ም በተፃፈ 5 (አምስት) ገጜ ዝርዝር ቅሬታ ያቀሚቡ ሲሆን ተጠቃሎ ሲታይ ዚፍርድ ቀቱ ሥራ እንዳይጐዳ ብሎ ዚፈፀምኩት መሆኑ እዚታወቀፀበአግባቡም ሣይጣራ ተድበስብሶ ዚታለፈ በመሆኑፀዚቀሚቡት ማስሚጃዎቜ ኚሚመለኚታ቞ው ህጐቜ ሳይገናዘብ ዹተሰጠ ውሳኔ በመሆኑና ፀ ዚፌዎራሉ ጠቅላይ ፍ/ቀት በሰበር መዝገብ ቁጥር 33075 ባሳለፈው ውሳኔ ዚዳኝነት ሥራ በሚያኚውኑበት ጊዜ ዹሚፈፅሙ ጥፋቶቜ እና ስህተቶቜ ዳኞቜ በስልጣን ያለ አግባብ መጠቀም በሚል ወንጀል ሊኚሠሱ አይገባም በማለት ዹሰጠው ውሳኔ ተሻሜሎ ተተርጉሞ ዚሥር ፍ/ቀቶቜ ውሣኔ ተሜሮ በነፃ ልሰናበት ብለዋል፡፡

     

    ቅሬታ቞ው ተመርምሮ ፈፀሙት ዚተባለው ድርጊት ጥፋተኛ በተባሉበት ዹህግ አንቀጜ ሥር ዚሚወድቅ መሆኑን ወይም ጉዳዩ ኚዳኝነት ሥነ ምግባርና ዲሲፕሊን አኳያ ዚሚታይ መሆኑን ለማጣራት ተብሎ ተጠሪ መልስ እንዲሠጡበት ተደርጓል፡፡

     

    ተጠሪ ሚያዚያ 9/2ዐዐ6 ዓ.ም በተፃፈ መልስ በወ/ህ/ቁ.407(2) መኚሰሱ እና ጥፋተኛ መባሉ ዹህግ ስህተት ዚሌለበት በመሆኑፀአስቀድሞ በሰ/መ/ቁ. 33075 ዹተሰጠው ውሳኔም ዚዳኝነት ሥራ በመኹናወን ላይ እያለ ዹሚፈፀሙ ጥፋትና ሥህተትን እንጅ መሠል ተግባርን ዚሚመለኚት ባለመሆኑ ዚሥር ፍ/ቀቶቜ ያሳለፉት ውሳኔ መሠሚታዊ ዹህግ ስህተት አልተፈፀመበትም ተብሎ እንዲፀና ጠይቀዋል፡፡ አመልካቹም ግንቊት 2/2006 ዓ.ም ዹተፃፈ ክርክራ቞ውን ዚሚያጠናክር ዹመ/መልስ አቅርበዋል፡፡

     

    ኹላይ ባጭሩ ለመግለፅ ዹሞኹርነው ዚጉዳዩን አመጣጥ ሲሆን ዹሰበር አቀቱታው ያስቀርባል ዚተባለበትን ጭብጥ ይዘን መዝገቡን መርምሚናል፡፡

     

    እንደመሚመርነው ፍሬ ነገሩን ዚማጣራት እና ማስሚጃ ለመመዘን ሥልጣኑ ዹተሰጠው ዚሥር ፍ/ቀት አመልካቹ መንግስት ዚፋይናንስ ህጐቜ እና ደንቊቜ ኹተፈቀደው ውጭ በአጠቃላይ ብር 7,650.40 እንዲወጣ በማድሚግ ለራሱም ሆነ ለሥራ ባልደሚቊቹ መጠቀሚያ በማድሚግ በኃላፊነቱ አላግባብ መገልገሉን አሚጋግጧል፡፡

     

    ይኾው በማስሚጃ ተሹጋግጧል ዚተባለው አድራጐት በመንግስት ሥራ ላይ ዹተፈፀመ ኚዳኝነት ሥራ ጋር ተቀላቅሎ ሊታይ ዚማይገባ ዹወንጀል ጥፋት ነው፡፡

     

    አመልካቹ በዳኝነት ተሹመው በቋሚት ዚዳኝነት ዚመንግሰት ሥራን ዚሚሰሩ ዚመንግስት ሠራተኛ በመሆናቾው እና ይሠሩበት ዹነበሹው ዚወሚዳ ፍ/ቀትም በመንግስት በጀት ተመድቊለት ዚዳኝነት መንግስታዊ ሥራ ዚሚኚናወንበት መስሪያ ቀት በመሆኑ በመንግስት ሥራ ላይ ዹሚፈፀሙ ወንጀሎቜን ዚሚመለኚቱ ዹወንጀል ህጉ ድንጋጌዎቜ በመሠል ጥፋቶቜ ላይም በተመሳሳይ ተፈፃሚነት ዹሚሆኑ ና቞ው፡፡ /ዹወ/ህ/ቁ. 402(1) እና (2) ይመለኚታል፡፡

     

    ሌላው መኚራኚሪያ እና ዹሰበር አቀቱታው ያስቀርባል ለመባሉ ምክንያት ዹሆነው ጉዳዩን ኚዳኝነት ሥነ ምግባር እና ዲሲፕሊን አኳያ ዚሚታይ መሆኑን ዹተመለኹተ ነው ፡፡

     

    በትግራይ ክልል ዳኞቜ እና ሬጅስትራሮቜን ለማስተዳደር ተሻሜሎ ዚወጣው ደንብ ቁጥር 1/2003 በመንግስት  ገንዘብ  ወይም  ንብሚት  በዳኞቜ  ዹሚፈፀምን  ያላግባብ  መጠቀም  እና መውሰድ


    ዚዲስፒሊን ጥፋት አድርጐ ይዟል፡፡ ነገር ግን ዚዲስፒሊን ደንቡ መሠል ድንጋጌ መያዙ በወንጀል ገሚድ ዹሚኖሹን ኃላፊነት ዚሚያስቀር አይደለም፡፡

     

    ዚዲስፕሊን ጉዳዩቜ ዚሚቋቋሙበት፣ ዚሚመሩበት ሥርዓት እና ኹሚሠጠው ውሳኔ ዹወንጀል ጥፋቶቜ ኚሚቋቋሙበት፣ኚሚመሩበት ሥርዓት እና ኹሚሰጠው ውሣኔ ተለይቶ ሊታይ ይገባል፡፡ ስለሆነም ዹተፈፀመው ጥፋት ዹወንጀል ተጠያቂነት ዚሚያስኚትል መሆን አለመሆኑ ኚዲስፒሊን ጉዳዩ ጋር ሊያታይ አይገባም፡፡

     

    ዚፌዎራሉ ጠቅላይ ፍ/ቀት ሰበር ቜሎት በሰበር መዝገብ ቁጥር 33075 ዳኛ ብርቁ ባላዬ እና ዚአማራ ክልል ስነ ምግባር እና ፀሹ ሙስና ኮሚሜን በተኚራኚሩበት ጉዳይ ጥር 13/2001 ዓ.ም ባሳለፈው ውሳኔ ዚዳኝነት ሥራን በሚያኚናውኑበት ወቅት ዹሚፈፅሙ ስህተቶቜ እና ጥፋቶቜ ሁሉ ዳኛን በሥልጣን አላግባብ መገልገል ወንጀል ሊያስጠይቁ  ዚማይቜሉ ስለመሆና቞ው መወሠኑ ዚዳኞቜን ህገ መንግስታዊ ዚውሳኔ ነፃነት ለማጠናኹር እንጅ በእጃቜን እንዳለው ጉዳይ ኚዳኝነት ሥራ ጋር ያልተያያዙ እና ዚአስተዳደር ስራ ሲያኚናውኑ ዹሚፈፀሙ ዹወንጀል ጥፋቶቜ ሁሉ ተጠያቂነትን ዚሚያስቀር ትርጉም ዹሚሠጠው ባለመሆኑ አመልካ቟ቜ ይኾው ውሳኔ በማመሳሰል ለተያዘው ጉዳይ ተፈፃሚ እንዲሆን ያቀሚቡት ጥያቄ በህጉ ተቀባይነት ዹለውም ብለናል፡፡

     

    በአጠቃላይ አመልካ቟ቜ በነበራ቞ው ዚሥራ ኃላፊነት ምክንያት ሊጠብቅ እና ሊኚላኚሉት ዚሚገባን ዚህዝብ እና ዚመንግስት ንብሚት ኹህግ ውጭ ሥልጣና቞ውን አላግባብ በመጠቀም ለፈፀሙት ጥፋት በስር ፍ/ቀቶቜ ዚተላለፈባ቞ው ውሣኔ ዹህግ ሥህተት ዚተፈፀመበት አይደለም ብለናል ተኚታዩንም ወስነናል፡፡

     

     ው ሳኔ

    ዚትግራይ ክልል ጠቅላይ ፍ/ቀት ሰበር ቜሎት በሰጠው መ/ቁ. 6111/06 ታህሳስ 3 ቀን 2006 ዓ.ም ያሳለፈው ትዕዛዝ ፀዚጠቅላይ ፍ/ቀቱ ይግባኝ ሰሚ ቜሎት በመ/ቁ.58434 ግንቊት 13 ቀን 2005 ዓ.ም ያሳለፈው ትዕዛዝ እና በደቡባዊ ዞን ማዕኹላዊ ፍ/ቀት ዚአላማጣ ምድብ ቜሎት በወ/መ/ቁ.02867/05 ዚካቲት 26/2005 ዓ.ም ዹሰጠው ፍርድ በወ/መ/ሥ/ሥ/ህ/ቁ.195(2)(ለ)(2) መሠሚት ፀንቷል፡፡

    መዝገቡ ተዘግቷል ወደ መ/ቀት ይመለስ፡፡

     


     

    ብ/ግ


    ዚማይነበብ ዚአምስት ዳኞቜ ፊርማ አለበት፡፡

  • ዚባህር ላይ ዚእቃ ማጓጓዝ ውልን በተመለኹተ ዹዕቃው ርክክብ ኚተፈፀመበት ወይም ዚማስሚኚቡ ጉዳይ ሳይፈፀም ቀርቶ እንደሆነ እቃውን ማስሚኚብ ኚሚገባበት ቀን አንስቶ በአንድ አመት ውስጥ ክስካልቀሚበ በይርጋ ዚሚታገድ ስለመሆኑ፡-

     

    ዚባህር ህግ ቁጥር 203ፀ180ፀ162

    ዹሰ/መ/ቁ. 98358

     

    ጥር 05 ቀን 2007 ዓ.ም

     

    ዳኞቜ፡-አልማው ወሌ

     

    ዓሊ መሐመድ ሱልጣን አባተማም ሙስጠፋ አህመድ ተኜሊት ይመሰል

    አመልካቜ፡- አንበሳ ኢንሹራንስ ኩባንያ -ነገሹ ፈጅ ኃይሉ ተሰማ ቀሚቡ

     

    ተጠሪ፡- ዚኢትዩጵያ ዚባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎት ድርጅት ጠበቃ ማሹን ወንዮ

    - ቀሚቡ

     

    መዝገቡ ተመርምሮ ተኚታዩ ፍርድ ተሰጥቷል፡፡

     

     ፍ      ር      ድ

     

    ጉዳዩ ዚመድን ውልን መሠሚት አድርጎ ዹቀሹበውን ዚገንዘብ ይተካልኝ ጥያቄ ዚሚመለኚት ሲሆን ክርክሩ ዹተጀመሹው ዹአሁኑ አመልካቜ በአሁኑ ተጠሪ ላይ በፌዎራሉ መጀመሪያ ደሹጃ ፍርድ ቀት በመሰሹተው ክስ መነሻ ነው፡፡ዚክሱ ይዘትም ባጭሩ፡- ዹአሁኑ አመልካቜ ለደንበኛው ለነፃ ኃላፊነቱ ዹተ.ዹግል ማህበር ኚቱርክ ሀገር ለሚያስመጣ቞ው 246 ጥቅል ብሚቶቜ ኚተጫኑበት ሀገር ተጓጉዞ እስኪመጣ ድሚስ ለሚያጋጥም ጉዳት በፖሊሲ ውል ቁጥር 01/ኀም አር ኊኀ/00001/07 ዚባህር ላይ ዹጉዞ መድን ሜፋን መስጠቱን፣ተጠሪ ዚመድን ሜፋን ዚተሰጣ቞ውን 246 ጥቅል ብሚቶቜን ተሹክቩ ሆውማ ቀሊ ቪ.ኢኀስቲአር53  በሚባለው  መርኚብ ኹሊአጋ ኢዝሚር ቱርክ አጓጉዞ ጅቡቲ ለማድሚስ በባህር እቃ መጫኛ ሰነድ ቁጥር 305/ኀስሲ ግዎታ መግባቱን፣ተጠሪ ጅቡቲ ለማድሚስ ግዎታ ኚገባባ቞ው 246 ጥቅል ብሚቶቜ ውስጥ እቃው ጅቡቲ ወደብ ደርሶ ሲራገፍ 11(አስራ አንድ) ጥቅል ብሚቶቜ መጥፋታ቞ውን፣ ኹተጓጓዘው 246 ጥቅል ብሚቶቜ ውስጥ ዚአመልካቜ ደንበኛ በ11/04/2004 ዓ/ም 226 ጥቅል አዲስ አበባ ላይ በእቃ መሚኚቢያ ሰነድ ቁጥር 10431 መሚኚቡን፣ቀሪው 20 ጥቅል ብሚት ውስጥ 9 ጥቅል ደግሞ ዘግይቶ በ05/06/2004 ዓ/ም በእቃ መሚኚቢያ ሰነድ ቁጥር 10999 መሚኚቡን፣ይህ ዚተጫነ እቃ መጥፋትና መጉደሉ በጅቡቲ ዚሰርቬዚር ስራ በሚሰራው ገልፍ ኀጄንሲ አገልግሎት ዚሚባል ሰኔ 24 ቀን 2004 ዓ/ም ማሚጋገጡን ገልጟ አመልካቜ ለደንበኛው ዹኹፈለውን ካሳ ብር 289,527.23 ተጠሪ እንዲተካለት ይወሰን ዘንድ ዳኝነት መጠዹቁን ዚሚያሳይ ነው፡፡ዚአሁኑ ተጠሪ ለክሱ በሰጠው መልስም፡-ዚመጀመሪያ ደሹጃ መቃወሚያዎቜን ያስቀደመ ሲሆን በዚህም መሰሚት ዚአመልካቜ ክስ እቃው በጅቡቲ ወደብ ላይ መራገፉ ኚተሚጋገጠበት ኚጳጉሜ 03 ቀን 2003 ዓ/ም ጀምሮ በሚታሰብ በአንድ አመት ይርጋ ጊዜ ውስጥ ዚሚታገድ መሆኑን ዚባህር ሕግ ቁጥር 203(1) ድንጋጌ እንደሚያሳይ እንዲሁም አመልካቜ ክስ ለማቅሚብ መብት ወይም ጥቅም ዹሌለው መሆኑን ገልፆ ክሱ ውድቅ ሊሆን ይገባል ሲል ተኚራክሯል፡፡


    ዚስር ፍርድ ቀትም በዚህ መልክ ዹቀሹበውን ዹይርጋ ክርክር በጭብጥነት ይዞ ጉዳዩን በመመርመር እቃው በጅቡቲ ወደብ ዚተራገፈው ጳጉሜ 03 ቀን 2003 ዓ/ም መሆኑን መነሻ አድርጎ ይርጋውን በመቁጠር ዚካቲት 05 ቀን 2005 ዓ/ም ዹቀሹበው ዚአመልካቜ ክስ በባህር ሕግ ቁጥር 203(1) መሰሚት በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ ያልቀሚበ በመሆኑ በይርጋ ዚታገደ ነው በማለት መዝገቡን ዘግቶታል፡፡በዚህ ብይን ዹአሁኑ አመልካቜ ቅር በመሰኘት ይግባኙን ለፌዎራሉ ኹፍተኛ ፍርድ ቀት ቢያቀርብም ተቀባይነት አላገኘም፡፡ዚአሁኑ ዹሠበር አቀቱታ ዹቀሹበውም ይህንኑ ብይን በመቃወም ለማስቀዚር ነው፡፡ዚአመልካቜ ዹሰበር አቀቱታ መሰሚታዊ ይዘትም፡- ዚመጚሚሻ ርክክብ ዹተደሹገው ዚካቲት 05 ቀን 2004 ዓ/ም ሁኖ እያለና ዹደንበኛው እቃ መጉደሉም ዹተገለጾው ሰኔ 24 ቀን 2004 ዓ/ም ሁኖ እያለ ዚእቃው ርክክብ ኚተጀመሚበት ጊዜ ጀምሮ ይርጋው ሊቆጠር ይገባል ተብሎ ዚአመልካቜ ክስ ውድቅ መደሹጉ ያላግባብ ነው ዹሚል ሲሆን አቀቱታው ተመርምሮም በዚህ ቜሎት ሊታይ ይገባዋል ተብሎ ተጠሪ ቀርቩ ግራ ቀኙ በፅሁፍ እንዲኚራኚሩ ተደርጓል፡፡

     

    ዚጉዳዩ አመጣጥ አጠር ባለመልኩ ኹላይ ዹተገለፀው ሲሆን ይህ ቜሎትም ዚግራ ቀኙን ክርክር ለሰበር አቀቱታው መነሻ ኹሆነው ውሳኔ እና አግባብነት ካላ቞ው ድንጋጌዎቜ ጋር በማገናዘብ በሚኹተለው መልኩ መርምሮታል፡፡እንደመሚመሚውም ዹዚህን ቜሎት ምላሜ ዚሚያስፈልገው ነጥብ ዚአመልካቜ ክስ በይርጋ ዚታገደ ነው ተብሎ ውድቅ መደሹጉ ባግባቡ ነው? ወይስ አይደለም? ዹሚለው ነው፡፡

     

    አመልካቜ በተጠሪ ላይ ክስ ሊመስርት ዚቻለው ለደንበኛው ለነፃ ኃላፊነቱ ዹተ.ዹግል ማህበር ኚቱርክ ሀገር ለሚያስመጣ቞ው 246 ጥቅል ብሚቶቜ ኚተጫኑበት ሀገር ተጓጉዞ እስኪመጣ ድሚስ ለሚያጋጥም ጉዳት በፖሊሲ ውል ቁጥር 01/ኀም አር ኊኀ/00001/07 ዚባህር ላይ ዹጉዞ መድን ሜፋን መስጠቱን መሰሚት አድርጎ ሲሆን በዚህ ጉዞ ሂደት ጠፉ ለተባሉት 11 ጥቅል ብሚቶቜ ለደንበኛው ኚፈልኩ ዹሚለውን ገንዘብ እቃዎቹን ዹማጓጓዝ ግዎታ አለበት ዹሚለው ተጠሪ እንዲተካለት ነው፡፡ስለሆነም ለጉዳዩ ቀጥተኛ አግባብነት ያለው ሕግ ዚባህር ህግ ሲሆን ለተያዘው ጉዳይ ተፈፃሚነት ያለውን ዹይርጋ ጊዜ ዚሚያስቀምጠው ዹህጉ ድንጋጌ ቁጥር 203 ሲሆን ድንጋጌው ሁለት ንዑስ ቁጥሮቜን ዚያዘ ሁኖ ዚመጀመሪያው ንዑስ ቁጥር ኚማመላለሻው ውል ውስጥ ዹተገኙ መብቶቜ በይርጋ ዚሚታገዱት ዚንግድ እቃውን ኚተሚኚበበት ቀን ጀምሮ ወይም ዚማስሚኚቡ ጉዳይ ሳይፈፀም ቀርቶ እንደሆነ እቃውን ማስሚኚብ ኚሚገባበት ቀን አንስቶ ዚአንድ አመት ጊዜ ካለፈ በኋላ ነው በማለት አስገዳጅነት ባለው ሁኔታ አስቀምጧል፡፡ዚተጠቃሹ ቁጥር ንዑስ ቁጥር ሁለት ድንጋጌ ደግሞ ኚሂሳብ አኹፋፋል ጋር ተያይዞ ዚሚነሳው ክርክር ዚሚታገድበትን አግባብ ዚሚያስቀምጥ ነው፡፡ ዚባህር ህግ ቁጥር 203 ድንጋጌ ዹሚገኘው በጭነት ማስታወቂያ ዹተሹጋገጠ ደሹሰኝ ዚማመላለሻ ውልን ዚሚመለኚቱ ልዩ ድንጋጌዎቜ በሚገዛው ክፍል ሲሆን ዚድንጋጌዎቜን ወሰን በተመለኹተ በቁጥር 180 ስር ሕግ አውጪ  አስቀምጧል፡፡ይህ ድንጋጌ በንዑስ ቁጥር አንድ ስር በክፍሉ ላይ ዚተመለኚቱት ድንጋጌዎቜ ዚሚፀኑት በተለይ በመርኚብ ላይ በተጫኑት ዚንግድ እቃዎቜ ዚጭነት ማስታወቂያ ደሹሰኝ ወይም ይህን በመሰለ ሌላ አይነት ሰነድ በተሚጋገጡ ዚጭነት ማመላለሻ ውሎቜ ላይ ብቻ መሆኑን ሲያስቀምጥ ዚድንጋጌው ንዑስ ቁጥር ሁለት እና ሶስት ደንጋጌዎቜ ደግሞ እንደቅደም ተኹተላቾው ዚመርኚብ መኚራዚት ውል ሰነድ ባለው ጉዳይ ላይ ተፈፃሚ ሊሆኑ እንደማይቜሉና በዚህ ጊዜም ድንጋጌዎቹ ተፈፃሚ ሊሆኑ ዚሚቜሉበትን ልዩ ሁኔታዎቜን ዚሚያስቀምጡ ና቞ው፡፡


    ወደ ተያዘው ጉዳይ ስንመለስም ተጠሪ ጅቡቲ ለማድሚስ ግዎታ ኚገባባ቞ው 246 ጥቅል ብሚቶቜ ውስጥ እቃው ጅቡቲ ወደብ ደርሶ ዚተራገፈው ጳጉሜ 03 ቀን 2003 ዓ/ም ሁኖ በዚህ ጊዜ ኹተጓጓዘው 246 ጥቅል ብሚቶቜ ውስጥ ዚአመልካቜ ደንበኛ በ11/04/2004 ዓ/ም 226 ጥቅል አዲስ አበባ ላይ በእቃ መሚኚቢያ ሰነድ ቁጥር 10431 መሚኚቡን፣ቀሪው 20 ጥቅል ብሚት  ውስጥ 9 ጥቅል ደግሞ ዘግይቶ በ05/06/2004 ዓ/ም በእቃ መሚኚቢያ ሰነድ ቁጥር 10999 መሚኚቡን

    ፣ይህ ዚተጫነ እቃ መጥፋትና መጉደሉ በጅቢቲ ዚሰርቬዚር ስራ በሚሰራው ገልፍ ኀጄንሲ አገልግሎት ዚሚባል ሰኔ 24 ቀን 2004 ዓ/ም ማሚጋገጡንና አመልካቜ ክስ ዹመሰሹተው ዚካቲት 05 ቀን 2005 መሆኑን ዚክርክሩ ሂደት ያሳያል፡፡አሁን ግራ ቀኙን እያኚራኚሚ ያለው ጉዳይ በባህር ህጉ ቁጥር 203(1) ዹተመለኹተው ዚአንድ አመት ዹይርጋው ጊዜ መቆጠር ዹሚጀምሹው ኚመቌ ጀምሮ ነው? ዹሚለው ነው፡፡አመልካቜ ዚበታቜ ፍርድ ቀቶቜ ዹይርጋ ጊዜ አቆጣጠር ስህተት ነው በማለት ዚሚኚራኚሚው ዚእቃዎቹ ርክክብ ጊዜ በማስጫኛ ውሉ ላይ አልተገለፀም፣በመጀመሪያው ዙር 226፣ቀጥሎ ደግሞ 9 ጥቅል ብሚቶቜ ዚተላኩ መሆኑንና ለክሱ መነሻ ዚሆኑት ቀሪዎቹ 11 ጥቅል ብሚቶቜ መጥፋታ቞ው ዹተሹጋገጠው ሰኔ 24 ቀን 2004 ዓ/ም ነው በሚል ነው፡፡እንግዲህ ኚክርክሩ ይዘት በግልጜ መሚዳት ዚሚቻለው እቃው በባህር ላይ ተጉዞ ጅቡቲ ዚተራገፈበት አግባብ በአንድ ዚማስጫኛ ሰነድ ያለመሆኑን ነው ፡፡በአንድ ዚማስጫኛ ሰነድ እቃዎቹን ተጠሪ ባልተሚኚበበት ሁኔታ ዚመጀመሪያው ዚማራገፊያ ቀን ማለትም ጳጉሜ 03 ቀን 2003 ዓ/ም ኹይርጋው መቆጠር መነሻ ቀን ዚሚሆንበት አግባብ ዚለም፡፡እንዲሁም ይግባኝ ሰሚው ፍርድ ቀት ዚመጀመሪያ ዚርክክብ ቀን ዹሆነው ታህሳስ 11 ቀን 2004 ዓ/ም ለይርጋው መነሻ ተደርጎ ሊወሰድ ይገባል ማለቱ እቃው በሙሉ አንድ አይነት፣በአንድ ዚጭነት ሰነድ በአንድ ዚማጓጓዣ ውል ዹተጓጓዘ መሆኑን ኚክሱ መሚዳት ይቻላል በሚል ነው፡፡ይሁን እንጂ ኹዚሁ ኚመጀመሪያው ርክክብ በኋላ 9 ጥቅል ብሚትን ዚአመልካቜ ደንበኛ ዚካቲት 05 ቀን 2004 ዓ/ም መሚኚቡ ያልተካደ ፍሬ ነገር ነው፡፡ስለሆነም ርክክቡ ዹቆመው ኹዚህ ኚዚካቲት 05 ቀን 2004 ዓ/ም በኋላ በመሆኑ ዚአመልካቜ ደንበኛ እቃዎቹ መጥፋታ቞ውን እርግጠኛ ሊሆኑ ይቜላሉ ተብሎ ዚሚታሰበው ኹዚህ ቀን በኋላ እንጂ ዚመጀመሪያው ርክክብ ኚተደሚገበት ጊዜ ጀምሮ አይደለም፡፡ተጠሪ ዚባህር ህግ ቁጥር 180(2) ድንጋጌን መሰሚት አድርጎ ዚሚያቀርበው ክርክርም እቃዎቹ ኚመርኚቡ ላይ ኚተጫኑበት አንስቶ አስኚሚራገፉበት ጊዜ ብቻ ዹበህር ህግ ቁጥር 203 ድንጋጌ ተፈፃሚ መሆኑን ዚሚያስቀምጥ ሲሆን ይህም እቃዎቹ ሙሉ በሙሉ ተጭነው ባልተቆራሚጠ ሁኔታ ርክክቡ ዚሚፈፀምበትን አግባብ ግንዛቀ ውስጥ በማስገባት ዹተቀመጠ ድንጋጌ ነው ኚሚባል በስተቀር በመርኚብ ላይ ዚተጫኑት እቃዎቜ በተግባር በተለያዩ ጊዜያት እዚተራገፉ ርክክቡም በተለያዩ ጊዜያት ሲደሚግ ዚነበሚበትን ሁኔታ ለመግዛት ታስቊ ዹተቀመጠ ነው ለማለት ዚሚቻል አይደለም፡፡ዚአመልካቜ ደንበኛ እቃዎቹን በተለያዩ ጊዜያት ሲሚኚቡ ዚነበሩ መሆኑ በፍሬ ነገር ደሹጃ ኹተሹጋገጠ እቃዎቹ ዚተራገፉበትን ቀን ወይም ዚመጀመሪያ ርክክብ ዚተደሚገበትን ቀን መነሻ አድርጎ ክሳ቞ው በይርጋ እንዲታገድ ማድሚግ ኹይርጋ ፅንሰ ሃሳብም ውጪ መሆኑ ዚሚታመን ነው፡፡

     

    ዹይርጋ ህግ መሰሚታዊ አላማ ተገቢውን ጥሚት ዚሚያደርጉ ገንዘብ ጠያቂዎቜን ወይም መብት አስኚባሪዎቜን መቅጣት ሳይሆን መብታ቞ውን በተገቢው ጊዜ ለመጠዹቅ ጥሚት ዚማያደርጉትን ሰዎቜ መቅጣት መሆኑ ይታመናል፡፡ስለሆነም ዚአመልካቜ ደንበኛ መብታ቞ውን ማስኚበር ሲቜሉ ያላግባብ ዚዘገዬበት ሁኔታ መኖሩን ዚክርክሩ ሂደት አያሳይም፡፡በባህር ህግ ቁጥር 162  ድንጋጌ ስር ዹይርጋ አቆጣጠር ጊዜ ዚሚጀምርበትን አግባብ ያስቀመጠ ሲሆን ለተያዘው ጉዳይ ግን ድንጋጌው ሙሉ በሙሉ አግባብነት አለው ለማለት ዚሚቻል ሁኖ አልተገኘም፡፡ምክንያቱም


    ድንጋጌው በንኡስ ቁጥር አንድ ስር ለመጫን ወይም ለማራገፍ ዹተወሰነው ጊዜ መቆጠር ዹሚጀምሹው ካፒ቎ኑ መርኚቡን ሊጫን ወይም ሊራገፍ ተዘጋጅቷል ብሎ ካስታወቀበት  ጊዜ ጀምሮ መሆኑን ሲያስቀምጥ ዚድንጋጌው ንዑስ ቁጥር ሁለት ደግሞ ጊዜም ዚሚታሰበው ካፒ቎ኑ ማስታወቂያውን ሰጥቶ ስራው ኚተጀመሚበት ጊዜ አንስቶ መሆኑን ያሳያል፡፡በሌላ አገላለፅ ይህ ድንጋጌ ተፈጻሚ ዹሚሆነው ዚመጫኛና ዚማራገፊያ ጊዜ ዚሚጀምርበት ጊዜ በግልጜ በታወቀበት ሁኔታ ነው እንጂ እቃዎቹ በተለያዩ ጊዜያት በተጫኑበትና በተራገፉበት ግንኙነት ውስጥ አይደለም፡፡ዚአመልካቜ ደንበኛ እቃዎቜ ሙሉ በሙሉ ዚተጫኑበት ቀንም ሆነ ዚሚራገፉበት ቀን ያለመታወቁን ዚክርክሩ ሂደት ያሳያል፡፡

     

    አመልካቜ በእርግጥም መብቱን ማስኚበር ዚሚቜልበት ጊዜ ዚካቲት 05 ቀን 2004 ዓ/ም ኚተባለ ይኌው ጊዜ በፍ/ብ/ሕ/ቁጥር 1848(1) ድንጋጌ መሰሚት ግንዛቀ ውስጥ ገብቶ በባህር ህጉ አንቀጜ 203(1) ዹተቀመጠው ዚአንድ አመት ጊዜ ዚሚያበቃው ኚዚካቲት 06 ቀን 2005 ዓ/ም ጀምሮ ሲሆን አመልካቜ ግን ይሄው ጊዜ ኹማለፉ በፊት ዚካቲት 05 ቀን 2005 ዓ/ም ክሱን ያቀሚበ በመሆኑ ክሱ በይርጋ ዚሚታገድ ሁኖ አልተገኘም፡፡ሲጠቃለልም ዚበታቜ ፍርድ ቀቶቜ ዚአመልካቜ ክስ በአንድ አመት ይርጋ ዚሚታገድ ነው በማለት ዚሰጡት ብይን ተገቢውን ዹይርጋ መቁጠሪያ ጊዜ መነሻ ያላደሚገ ኹመሆኑም በላይ ዚባህር ህግ ቁጥር 162 ድንጋጌን ይዘቱንና መንፈሱን ኚተያዘው ጉዳይ ልዩ ባህርይ ጋር ባላገናዘበ መልኩ በመሆኑ ብይኑ መሰሚታዊ ዹሆነ ዹሕግ ስህተት ያለበት ሁኖ ተገኝቷል፡፡ በዚህም መሰሚት ተኚታዩን ወስነናል፡፡

     

     ው ሳኔ

     

    1. በፌዎራሉ መጀመሪያ ደሹጃ ፍርድ ቀት በመ/ቁጥር 203024 ግንቊት 06 ቀን 2005 ዓ/ም ተሰጥቶ በፌዎራል መጀመሪያ ደሹጃ ፍርድ ቀት በመ/ቁጥር 137802 ታህሳስ 08 ቀን 2006 ዓ/ም በትእዛዝ ዹፀናው ብይን በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 348(1)መሰሚት ተሞሯል፡፡

    2.  ዚአመልካቜ ክስ በይርጋ ዚታገደ አይደለም ብለናል፡፡

    3. ዚፌዎራሉ መጀመሪያ ደሹጃ ፍርድ ቀት ክርክሩን በመ/ቁጥር 203024 ቀጥሎ በሌሎቜ ዚግራ ቀኙ ዹክርክር ነጥቊቜ ተገቢውን ዹክርክር አመራር ስርዓት ተኚትሎ ተገቢውን ዳኝነት እንዲሰጥበት ጉዳዩን በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 341(1) መሰሚት መልሰን ልኚንለታል፡፡ይፃፍ፡፡

    4.  በዚህ ቜሎት ለተደሹገው ክርክር ዚወጣውን ወጪና ኪሳራ ዚዚራሳ቞ውን ይቻሉ ብለናል፡፡

    መዝገቡ ተዘግቷልፀወደ መዝገብ ቀት ይመለስ ብለናል፡፡

     


     

    ት/ጌ


    ዚማይነበብ ዚአምስት ዳኞቜ ፊርማ አለበት፡፡

  • ዚዲፕሎማቲክ ግንኙነቶቜን ስምምነት ልምድን ለማክበር ሲባል ዹውጭ ዲፕሎማቲክ ሚሲዮኖቜና ኢትዮጲያዊያን ሠራተኞቻ቞ው ዚሚያደርጉት ዚቅጥር ግንኙነት ላይ ዚአሠሪና ሠራተኛ ሕግ ተፈፃሚ ዹማይሆን ስለመሆኑ፡-

     

    ዚተባበሩት መንግስታት አካል ዹሆነ ድርጅት ዚተባበሩት መንግስታት ጥቅምና ዹተለዹ ኹለላን በተመለኹተ በተደነገገ ሥምምነት በማንኛውም ዚመንግስት ፍ/ቀቶቜ ተኚሶ መቅሚብ ዚሌለበት ሥለመሆኑ፡-

     

    አፈፃፀም በፍርድ ቀት ዹተሰጠ ውሳኔ ትርጉም እንዲኖሚው በማድሚግ ውጀት ያለውና በተገቢው መንገድ መፈፀም ያለበት መሆኑ ዚሚታወቅ ቢሆንም ለማንኛውም ጉዳዮቜ ይሰራል ተብሎ ድምዳሜ ላይ መድሚስ ዚማይቻል ስለመሆኑ፡-

     

    አዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀፅ 3/3(ሀ) ዚተባበሩት መንግስታት ቻርተር አንቀፅ 105

    ኚተባበሩት መንግስት ጥቅምና ዹተለዹ ኹለላን በተመለኹተ ዹተደነገገው ሥምምነት አንቀፅ 2/2/ እና 3

     

    ዹፍ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ 212

    ዹሰ/መ/ቁ/ 98541

     

    ህዳር 10 ቀን 2007 ዓ.ም

     

    ዳኞቜ፡-አልማው ወሌ

     

    ዓሊ መሐመድ ሡልጣን አባተማም መስጠፋ አህመድ ተኜሊት ይመሰል

    አመልካቜ፡- አቶ አለማዹሁ ኩላና - ቀሚቡ

     

    ተጠሪ፡-ዚተባበሩት መንግስታት ዚልማት ድርጅት (UNDP) ታልፏል ፡፡

     

    መዝገቡ ተመርምሮ ተኚታዩ ፍርድ ተሰጥቷል፡፡

     

     ፍ ርድ

     

    ይህ ዹሰበር ጉዳይ ዹቀሹበው አመልካቜ በተጠሪ ላይ ዚአሠሪና ሰራተኛ ጉዳይ አዋጅ ቁጥር 377/1996 ድንጋጌዎቜን መሰሚት አድርገው ያቀሚቡት ክስ ተጠሪ በሌለበት ታይቶ በክርክሩ ኚተሚጋገጠበት ዚፍሬ ነገር ጉዳዮቜ በመነሳት ዹአሁኑ አመልካቜ ዚተለያዩ ክፍያዎቜ በተጠሪ እንዲኚፍሏ቞ው በወሚዳው ፍርድ ቀት በተወሰነው መሰሚት ዚአፈጻጞም መዝገብ ኹፍተው ክርክሩ በመታዚት ላይ እያለ ተጠሪ ዚመኚሰስ መብት ዹለውም ተብሎ ዚአፈጻጞም መዝገቡ በሁሉም ዚበታቜ ፍርድ ቀቶቜ መዘጋቱ ተገቢ መሆን ያለመሆኑን ለመመርመር ተብሎ ነው፡፡

     

    ዹአሁን አመልካቜ ተጠሪ ኹህግ ውጪ ኚስራ አሰናብቶኛል በማለት ካሳና ዚተለያዩ ክፍያዎቜ እንዲኚፍሏ቞ው ይወሰን ዘንድ በያበሎ ወሚዳ ፍርድ ቀት በአሁኑ ተጠሪ ላይ ክስ መስርተው ዹአሁኑ ተጠሪ በሌለበት ጉዳዩ እንዲታይ ተደርጎ ፍርድ ቀቱ ጉዳዩን መርምሮ ስንብቱ ሕገ ወጥ መሆኑን በመደምደም ለአመልካቜ ካሳና ዚተለያዩ ክፍያዎቜ እንዲኚፈሉ በማለት ወስኗል፡፡አመልካቜ ይህንኑ ውሳኔ ለማስፈፀም በወሚዳው ፍርድ ቀት ዚአፈጻጞም ክስ ኹፍተው ጉዳዩ መታዚት ኹጀመሹ በኋላ ዚወሚዳው ፍርድ ቀት ጉዳዩን መርምሮ ዚተባበሩት መንግስታት ኮንቬንሜንን አንቀፅ 2(3) በዋቢነት ጠቅሶ ፍርድ ቀቱ ጉዳዩን ለማዚት ስልጣን ዹለውም በማለት ዚአፈጻጞም መዝገቡን ዘግቶታል። በዚህ ትዕዛዝ አመልካቜ ቅር በመሰኘት ይግባኛ቞ውን  ለቩሹና ዞን ኹፍተኛ ፍርድ ቀት ቢያቀርቡም ተቀባይነት አላገኙም፡፡አመልካቜ ለክልሉ ሰበር ሰሚ ቜሎት አቀቱታ቞ውን አቅርበውም ቜሎቱ ጉዳዩን መርምሮ ተጠሪን ያስቀርባል ዹሚል ትዕዛዝ ሰጥቶ


    ተጠሪ ሊቀርብ ባለመቻሉ መልስ መስጠቱ ዚታለፈ ሲሆን ቜሎቱ ጉዳዩን መርምሮ ጉዳዩ ዚአሰሪና ሰራተኛ ጉዳይ ሁኖ አመልካቜ ዚሚኚራኚሩት ዚተባበሩት መንግስታት አካል ኹሆነው ድርጅት ጋር መሆኑን፣ ኚእንደዚህ አይነት ድርጅቶቜ ጋር ዹሚደሹግ ግንኙነት በአዋጅ ቁጥር 377/1996 ዹማይገዛ መሆኑ በተጠቃሹ አዋጅ አንቀጜ 3(ሀ) ስር መመልኚቱን፣ተጠሪና መሠል አካላት በሕግ ዹተለዹ ኹለላ ያላ቞ው መሆኑ በተባበሩት መንግስታት ቻርተር አንቀጜ105፣በተባበሩት መንግስታት ጥቅምና ዹተለዹ ኹለላን በተመለኹተ ለመንደንገግ በወጣው ስምምነት አንቀጜ 2(2) እና 3 ስር መደንገጉን፣ኢትዩጵያም ይህንኑ ስምምነት መፈሹሟን በዋቢነት ጠቅሶ ኚመነሻውም ተጠሪ በወሚዳው ፍርድ ቀት መኚሰሱ ተገቢነት እንደሌለው፣አመልካቜ ያላ቞ው መፍትሔም በ"United Nations Commission on International Trade Law (UNCITRAL)" ደንቊቜ  መሰሚት ኚተጠሪ ጋር ባላ቞ው ስምምነት መሰሚት በእርቅ መጚሚስ መሆኑን፣በዋናው ጉዳይ ስልጣን ዹሌለው ፍርድ ቀት ጉዳዩን አይቶ መወሰኑን ኚተጠሪ ጥቅምና ኚባለ መብቶቜ አንፃር ሲታይ ዋናውን ውሳኔ ሕጋዊ ዚማያደርገው መሆኑን ዘርዝሮ ዚበታቜ ፍርድ ቀቶቜ ጉዳዩን ዚማዚት ስልጣን ዹለንም በማለት ዚአፈጻጞም መዝገብ መዝጋታ቞ውን በመቀበል ዚአመልካቜን ዹሰበር አቀቱታ ውድቅ አድርጎታል፡፡ዚአሁኑ ዹሰበር አቀቱታ ዹቀሹበውም ይህንኑ ውሳኔ በመቃወም ለማስለወጥ ነው፡፡ዚአመልካቜ ዹሰበር አቀቱታ መሰሚታዊ ይዘትም በዋናው ጉዳይ ላይ ተጠሪ ቀርቩ ባልተኚራኚሚበት ሁኔታ በአፈጻጞም መዝገብ ዚተጠሪን ያለመኚሰስ ኹለላ በመጥቅስ ዋናውን ውሳኔ ውድቅ ማድሚግ ሥነ ሥርዓታዊና ዹሕግ ዚበላይነት እንዲሁም አመልካቜ እንደ ዜጋ ፍትህ ዚማግኘት መብት ያላ቞ው መሆኑን ያላገናዘበ ነው በማለት መኚራኚራ቞ውን ዚሚያሳይ ነው፡፡አቀቱታው ተመርምሮም በዚህ ቜሎት እንዲታይ በመደሹጉ ለተጠሪ ጥሪ ተደርጎለት ባለመቅሚቡ በጜሑፍ መልስ መስጠቱ ታልፏል፡፡

     

    ዚጉዳዩ አመጣጥ አጠር አጠር ባለመልኩ ኹላይ ዹተገለፀው ሲሆን ይህ ቜሎት ጉዳዩን ኚበታቜ ፍርድ ቀቶቜ ውሳኔ እና አግባብነት ካላ቞ው ድንጋጌዎቜ ጋር በማገናዘብ እንደሚኚተለው መርምሮታል፡፡

     

    በመሰሚቱ በአመልካቜና በተጠሪ መካኚል ዚተነሳው ግንኙነት ዚቅጥር ውልን መሰሚት  ያደሚገ ሲሆን ዋናው ክርክር በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አግባብ ታይቶ ዳኝነት ማግኘቱን ዚክርክሩ ሂደት ያሳያል፡፡ ዚተለያዩ ዓይነት በቅጥር ላይ ዚተመሰሚቱ ዚስራ ግንኙነቶቜ ዚሚኖሩ ሲሆን ግንኙነቶቹ ዚሚገዙበት ዹሕግ አግባብም ይለያያል፡፡ አዋጅ ቁጥር 377/1996 ተፈፃሚ ዚማይሆንባ቞ው ግንኙነቶቜ ያሉ ሲሆን ኹነዚህ ውስጥ ይህ አዋጅ በዚትኞቹ ላይ ተፈጻሚነት ሊኖሹው እንደሚቜል በዋነኝነት ዚሚመራው ዹአዋጁን ዚተፈጻሚነት ወሰን ዹደነገገው አንቀጜ 3 ነው፡፡ለዚህ ጉዳይ ቀጥተኛ አግባብነት ያለው ዚአንቀጹ ድንጋጌ በንዑስ ቁጥር ሶስት በፊደል "ሀ" ስር ዹተመለኹተው ሲሆን በዚህ ንዑስ ድንጋጌ ስር ዚስራ ግንኙነቱ በንዑስ አንቀጜ ሁለት ስር ዚሚወድቁ ባለመሆና቞ዉ በአዋጁ አንቀጜ 1 መሰሚት በቀጥታ ሊፈጞምባ቞ው ዚሚቜል ቢሆንም በንኡስ አንቀጜ 3 ስር በተገለጹት ሁኔታዎቜ መሰሚት ኹአዋጁ ሜፋን ውጭ ሊደሹጉ ዚሚቜሉ ዚስራ ግንኙነቶቜን ዚሚመለኚት ነው፡፡በዚሁ መሰሚት ኢትዮጰያ ውስጥ ዚሚሰሩ ዚዲፕሎማቲክ ሚሲዮኖቜ ወይም አለም አቀፍ ድርጅቶቜ ኚኢትዮጵያውያን ጋር ዚሚመሰርቱት ዚስራግንኙነት ዚሚኒስትሮቜ ምክር ቀት በሚያወጣው ደንብ መሰሚት ወይም ኢትዮጵያ በምትፈርማ቞ው አለምዓቀፍ ስምምነቶቜ መሰሚት በአዋጁ ሊሾፈኑ እንደማይቜሉ ተመልክቷል፡፡በመሆኑም በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጜ 3 ድንጋጌዎቜ ሲታዩ አዋጁ በአጠቃላይ በአሰሪና ሰራተኛ መካካል በሚቋቋም በቅጥር ላይ በተመሰሹተ ዚስራ ግንኙነት ላይ ተፈጻሚነት ዹሚኖሹው ቢሆንም በአዋጁ


    በግልጜ በተደነገጉ ሌላ ህግ በሚገዛቾው ግንኙነቶቜ ላይ ተፈጻሚነት  እንደማይኖሚው ያስገነዝባሉ፡፡ በተጚማሪም አሁንም አዋጁ ዹሚሾፍናቾው ዚስራ ግንኙነቶቜ ሊሆኑ ቢቜሉም ነገርግን ዚሚኒስትሮቜ ምክርቀት ወይም ኢትዮጵያ ዚምትፈርማ቞ው አለምአቀፍ ስምምነቶቜ በሚወስኑት መሰሚት ኹአዋጁ ሜፋን ውጭ ሊደሹጉ ዚሚቜሉ መሆኑን ተመልክቷል፡፡ኚእነዚህ ድንጋጌዎቜ ይዘትና መንፈስ ዚምንሚዳው ሕግ አውጪው ዚዲፕሎማቲክ ግንኙነቶቜን ስምምነትና ልምድን ለማክበር ሲባል ዹውጭ ዲፕሎማቲክ ሚስዮኖቹና ኢትዩጵያውን ሠራተኞቻ቞ው ዚሚያደርጉት ዚቅጥር ግኙነት ላይ ዚአሰሪና ሰራተኛ ሕግ ተፈጻሚ እንዳይሆን ያደሚገ መሆኑን ነው፡፡በመሆኑም በሕጉ በተሰጠው ስልጣን መሰሚት ዚሚኒስትሮቜ ምክር ቀት በሚያወጣው ደንብ ወይም ኢትዩጵያ ኹውጭ ድርጅቶቜ ጋር በምትፈራሚምባ቞ው አለም አቀፍ ስምምነቶቜ መሰሚት አዋጅ ቁጥር 377/1996 ተፈፃሚ እንዳይሆን ዚሚደሚግበት አግባብ መኖሩን ሕግ አውጪ በግልፅ ያስቀመጠው ጉዳይ ነው፡፡ዚአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጜ 3(3((ሀ)) መሰሚታዊ አላማ ዹውጭ አገር መንግሥታት ተወካዮቜን ሉአላዊነት እና አለምአቀፍ ስምምነቶቜን ለማክበር ተብሎ ነው ተብሎ ዚሚታሰብ ሲሆን በተጚባጭ ባለው ሁኔታ ደግሞ ዚውጪ ዲፕሎማቲክ ሚሲዮኖቜና አለም አቀፍ ድርጅቶቜ ኚኢትዩጵያ ዹውጭ ጉዳይ ሚኒስትር መስሪያ ቀት ጋር ስምምነት ተፈራርመው ይኌው ዚመንግስት አካል በእነዚህ ተቋሞቜ ተቀጥሚው ዚሚሰሩት ኢትዩጵያውንን መብትና ጥቅም ለማስኚበር ዚሚያስቜል ስርዓት ዘርግቶ በአለም አቀፍ ስምምነቶቜ በተካተተው አግባብ ዹተፈጠሹው አለመግባብት ሰላማዊ በሆነ መንገድ በማግባባትና በድርድር እንዲፈታ በማድሚግ ላይ እንደሚገኝ ዚሚታወቅ ነው፡፡

     

    ወደተያዘው ጉዳይ ስንመለስም አመልካቜ ክርክር ያቀሚቡት ግንኙነቱ በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጜ 3(3(ሀ)) መሰሚት ሊገዛ ኚማይቜል አካል ጋር ነው፡፡ተጠሪ ዚተባበሩት መንግስታት አካል ሲሆን ዚተባበሩት መንግስታት ጥቅምና ዹተለዹ  ኹለላን በተመለኹተ በተደነገገ ስምምነትም በማንኛውም መንግስት ፍርድ ቀቶቜ ተኚሶ መቅሚብ ዚሌለበት መሆኑን በተባበሩት መንግስታት ቻርተር አንቀፅ 105 እንዲሁም ኚተባበሩት መንግስታት ጥቅምና ዹተለዹ ኹለላን በተመለኹተ በተደነገገው ስምምነት አንቀጜ 2(2) እና 3 ስር በግልጜ ተመልክቷል፡፡አመልካቜ በዚህ ሚገድ ዚሚያቀርቡት ክርክር ዹሌለ ቢሆንም አሁን አጥብቀው ዚሚኚራኚሩት በዋናው ጉዳይ ውሳኔ ኹአሹፈ በውሳኔው መሰሚት ኹሚፈጾም በስተቀር ዚተጠሪ በሕግ ያለው ዹተለዹ ኹለላ እንደ አቢይ ምክንያት ተወስዶ አፈፃጾሙ ሊቆም ዚሚቜልበት አግባብ ዹለም በሚል ነው፡፡በሕግ አግባብ ዹተሰጠ ፍርድ ዋጋ እንዳይኖሚው ዹሚደሹገው ዚአፈጻጞም ትዕዛዝ ተገቢነት እንደሌለው ኹፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 378 ድንጋጌዎቜ ይዘትና መንፈስ ዹምንገነዘበው ጉዳይ ነው፡፡በሕግ አግባብ ታይቶ ዹተሰጠን ውሳኔ በሕጉ አግባብ ማስፈፀም በኢ.ፌ.ዲ.ሪፐብሊክ ሕገ መንግስት አንቀጜ 78(1) እና 79(1) እና (4) ስር ዹተሹጋገጠውንና ዹተኹበሹውን ዚነጻ ፍርድ ቀት መኖርንና ዚዳኝነት ስልጣን በአግባቡ ተግባራዊ ዚሚያደርገው እና በሕገ መንግስቱ አንቀጜ 37 ስር ዹተሹጋገጠው ዚዜጎቜ ፍትህ ዚማግኘት መብትም ውጀት ባለው መልኩ ተግባራዊ ዚሚሆንበት መንገድ መሆኑ ግልጜ ነው፡፡አፈጻጞም በፍርድ ቀት ዹተሰጠ ውሳኔ ትርጉም እንዲኖሚው ዚማድሚግ ውጀት ያለውና በተገቢው መንገድም መፈፀም ያለበት መሆኑ ዚሚታወቅ ነው፡፡ይህ ግን ለማንኛውም ጉዳዮቜ ሁሉ ይሰራል ብሎ ድምዳሜ ላይ መድሚስ ተገቢ ያልሆነ ሕጋዊ ውጀት ዚሚያስኚትል መሆኑ እሙን ነው፡፡በእርግጥ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 212 ድንጋጌ ስር በስነ ስርዓት ጉድለት አንድ ፍርድ ውድቅ ሊሆን እንደማይቜል ዹተመለኹተ ሲሆን ይህ ግን ዚሚሰራው ዚፍትሓ  ብሔር ስነ ስርዓት ሕጉ ተፈፃሚነት ወስንን መሰሚት በማድሚግ በሌላ አኳኃን እንዲፈፀም በሕግ


    ባልተደነገገበት ሁኔታ መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡በመሆኑም ኚመነሻውም ኢትዩጵያ በፈሚመቜው አለም አቀፍ ስምምነት መሰሚት በኢትዩጵያ ፍርድ ቀቶቜ ላለመዳኘት ነገር ግን ኚኢትዩጵያ ዜጎቜ ጋር ለመሰሹተው ግንኙነት በሌላ አግባብ ጉዳዩን ለመጚሚስ ዚሚያስቜል ስርዓት ያለው ወገን በዋናው ክርክር ጊዜ ቀርቩ ባለመኚራኚሩና በይግባኝ ጉዳዩን ባለማሳሚሙ ምክንያት ብቻ ስልጣን ዹሌለው ፍርድ ቀት ዹሰጠውን ውሳኔ እንዲፈጜም ዚሚገደድበት አግባብ ዚለም፡፡ስለዚህ ኹዚህ ጉዳይ ዹተለዹ ባሕርይ ስንነሳ ዹፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 212 እና 4 ድንጋጌዎቜ አንድ ላይ ተጣምሚው ሲታዩ አፈፃጾሙ ዋጋ ያለውን ፍርድ መሰሚት ያደሚገ ነው፣ጉዳዩ ኚስነ ስርዓት ጉድለት ጋር ዚተያያዘ ነው ለማለት ዚሚቻል ሁኖ አላገኘነም፡፡ተጠሪ በሕግ ዚተጠበቀለት ዹኹለላ መብትና ጥቅም እያለው ስልጣን ዹሌለው ፍርድ ቀት ዹሰጠውን ውሳኔ እንዲፈጜም ማድሚግ ሕግ አውጪው ዚዲፕሎማቲክ ግንኙነቶቜን ልምድን ለማክበር ሲባል በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጜ 3(3(ሀ)) ስር ያስቀመጠውን ድንጋጌ  ዋጋ ዚሚያሳጣው እና በዲፕሎማቲክ ግንኙነቱም አሉታዊ ውጀት ዚሚያስኚትል በመሆኑ ተመራጭ ሁኖ አላገኘነውም፡፡ሲጠቃለልም ዚጉዳዩ ልዩ ባህርይ ሲታይ ዹፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 212 ድንጋጌን ጠቅሶ አፈፃጾሙን ማስቀጠል ዚሚቻልበት አግባብ ስለሌለና አመልካቜም እንደዜጋ መንግስት በውጪ ጉዳይ ሚኒስ቎ር መስሪያ ቀት በኩል በዘሹጋው ስርዓት መሰሚት መብትና ጥቅማ቞ውን ዚሚያስኚበሩበት ሁኔታ ያለ በመሆኑ ዹሕግ ዚበላይነት አልተኚበሚም፣ ዹዜጋ ፍትህ ዚማግኘት ሕገ መንግስታዊ መብት ተጥሷል ለማለት ስላልተቻለ ዹክልሉ ፍርድ ቀቶቜ ዚሰጡት ውሳኔ መሰሚታዊ ዹሆነ ዹሕግ ስህተት ዚለበትም በማለት ተኚታዩን ወስናል፡፡

     

     ው ሣኔ

     

    1.  በኊሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ጠቅላይ ፍርድ ቀት ሰበር ሰሚ ቜሎት በመ/ቁጥር

    163639 ታህሳስ 07 ቀን 2006 ዓ/ም ዚበታቜ ፍርድ ቀቶቜን ትዕዛዝ በማፅናት ዹተሰጠው ውሳኔ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 348(1) መሰሚት ፀንቷል፡፡

    2. ዚአመልካቜ ዚአፈጻጞም ክስ መዘጋቱ ተገቢ ነው ብለናል፡፡አመልካቜ አለኝ ዚሚሉትን መብትና ጥቅም በሌላ አግባብ ኹመጠዹቅ ይህ ውሳኔ አያግዳ቞ውም ብለናል፡፡

    3. በዚህ ቜሎት ለተደሹገው ክርክር ዚወጣውን ወጪና ኪሳራ አመልካቜ ዚራሳ቞ውን ይቻሉ ብለናል፡፡

    መዝገቡ ተዘግቷልፀወደ መዝገብ ቀተ ይመለስ ብለናል፡፡

     

    ዚማይነበብ ዚአምስት ዳኞቜ ፊርማ አለበት::

     

     

     

     

    መ/ብ

  • አንድ ባለሙያ በአሠሪው ቁጥጥር ሳይሆን በራሱ ዚሙያ ኃላፊነት ዚሙያ አገልግሎት ለመስጠት ኚአንድ አሠሪ ጋር ውል ሲኖሚው ጉዳዩ ዹሚገዛው በአሠሪና ሠራተኛ ህግ ስላለመሆኑ፣

    -ኚአንድ ባለሙያ ጋር ዚሙያ ግልጋሎት ውል ያለው አሠሪ ውሉን በማናቾውም ጊዜ ማፍሚስ ሥለመቻሉ፣

    አዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጜ 3 ንዑስ አንቀስ /1//2/ ዹፍ/ህ/ቁ. 2140፣2646/1/፣ 2638/1/

     

    ዹሰ/መ/ቁ. 101396

     

    ታህሳስ 21 ቀን 2007 ዓ.ም

     

    ዳኞቜ፡- አልማው ወሌ

     

    ዓሊ መሐመድ ሱልጣን አባተማም ሙስጠፋ አህመድ ተኞሊት ይመሰል

    አመልካቜ፡- አዲስ አጠቃላይ ሆስፒታል ጠበቃ አብደላ ዓሊ ቀሚቡ ተጠሪ፡- ዶ/ር ምስራቅ ጥላሁን ጠበቃ አቶ ስመኘው አራጌ ቀሚቡ

    መዝገቡን መርምሹን ዹሚኹተለውን ፍርድ ሰጥተናል

     

     ፍ ር ድ

     

    ጉዳዩ ዹቀሹበው አመልካቜ ዚፌደራል ዚመጀመሪያ ደሹጃ ፍርድ ቀት በመዝገብ ቁጥር 42275 ሐምሌ 9 ቀን 2005 ዓ.ም ዹሰጠው ውሣኔና ዚፌደራል ኹፍተኛ ፍርድ ቀት በመዝገብ ቁጥር 135997 ግንቊት 18 ቀን 2006ዓ.ም ዹሰጠው ውሳኔ መሠሚታዊ ዹሕግ ስህተት ያለበት ስለሆነ በሰበር ታይቶ ይታሚምልኝ በማለት ያቀሚበውን ዹሰበር አቀቱታ አጣርቶ ለመወሰን ነው፡፡ ጉዳዩ ዚሥራ ውል ኹሕግ ውጭ በአሠሪው ተቋርጣል በማለት ያቀሚቡትን ጥያቄዚሚመለኚት ነው፡፡

    1. ዚክርክሩ መነሻ ተጠሪ ያቀሚበው ዚክስ ማመልኚቻ ነው፡፡ተጠሪ በአመልካቜ ድርጅት ውስጥ በወር ብር 8000,/ስምንት ሺ ብር/ እዚተኚፈለው በራዲያሎጅስት ሙያ ኚጥር 1 ቀን 2000ዓ.ም ጀምሮ ሲያገለግሉ ዚቆዩ መሆኑን ገልፀውፀአሰሪው አመልካቜ ኹሕግ አግባብ ውጭ ያቋሚጠ ስለሆነ በአዋጅ ቁጥር 377/96 ድንጋጌዎቜ መሠሚት ዚተለያዩ ክፍያዎቜ እንዲኚፍል ውሣኔ ይሰጥልኝ በማለት አመልክተዋል፡፡

    አመልካቜ ተኚሣሜ ሆኖ ቀርቩ ኚኚሳሜ/ተጠሪ/ጋር ዚሥራ ቅጥር ውል ግንኙነት ዚለንም፡፡ኚሳሜ ጋር ያለን ግንኙነት፣ኚሳሜ በትርፍ ሠዓታ቞ው ዚሙያ ግልጋሎት እዚሰጡ ክፍያ ዚሚያገኙበት ዹውል ግንኙነት ነው፡፡ተኚሳሜ ይህንን በትርፍ ሠዓት ዚሚሰጥ ዚሙያ ግልጋሎት ውል አላቋሚጠም፡፡ ኚሳሜ ዚሙያ ፈቃዳ቞ውን ኚጀና ጥበቃ ሚኒስትር ያላሳደሱ በመሆኑ ፈቃዳ቞ውን አድሰው ሲቀርቡ ሥራ ዚሚጀምሩ ፀመሆኑን ተገልፆላቾዋል ኚሳሜ በድርጅታቜን ውስጥ በቀን ሁለት ሰዓት ዚሚሠራ ሲሆን በጡሚታ ዹተገለሉ በመሆኑ ኚኚሳሜ ጋር ቋሚ ዹሆነ ዚአሠሪና ዚሠራተኛ ግንኙነት ዹላቾውም በማለት ተኚራክሚዋል፡፡

    2. ዚሥር ፍ/ቀት ግራ ቀኙ ያቀሚቡትን ክርክር ኹመሹመሹ በኃላ ዚጀና ጥበቃ ሚኒስ቎ር ዚኚሳሜን ስም በመጥቀስ ጥቅምት 5 ቀን 2002 ዓ.ም ዹፃፈው ደብዳቀና ሌሎቜ ዹፅሑፍ ሰነዶቜ በማስሚጃነት ያቀሚቡለት መሆኑን ጠቅሶ በኚሳሜ እና በተኚሳሜ መካኚል ዚአሠሪና ሰራተኛ ግንኙነት አለ ኚሳሜ ዚተኚሳሜን ዚሥራ ውል ያቋሚጠው ኹሕግ አግባብ ውጭ ነው


    በማለት ኚሳሜ ለተኚሳሜ ዚሥራ ስንብት ክፍያ ዚማስጠንቀቂያ ክፍያ ዚካሣ ክፍያና ክፍያ ለዘገዚበት ክፍያና ዹፅሁፍ ክፍያ እንዲኚፍል ውሳኔ ሰጥቶበታል፡፡ አመልካቜ በዚህ ውሳኔ ቅር በመሰኘት ይግባኝ ለፌዎራል ኹፍተኛ ፍርድ ቀት አቅርቧል፡፡ ዚፌዎራል ኹፍተኛ ፍርድ ቀት ዚግራ ቀኙን ክርክር ኹሰማ በኃላ ዚሥር ፍርድ ቀት ዹሰጠውን ውሣኔ አፅንቶታል፡፡

    3. አመልካቜ ግንቊት 28 ቀን 2005 ዓ.ም በተፃፈ ዹሰበር አቀቱታ ተጠሪ ኚጀና ጥበቃ ሚኒስ቎ር ዚሙያ ብቃት ማሚጋገጫ ተሰጥቷ቞ው ኚአመልካቜ ዘንድ በቀን ሁለት ሠዓት ብቻ ዚሚያገለግሉራዲዮሎጂስት ና቞ው፡፡ ይህ ፍሬ ጉዳይ በተጠሪ አልተካደም ይህም በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀፅ 3 ንዑስ አንቀጜ 2(1) ዹሚሾፈንና በአመልካቜ እና በተጠሪ መካኚል ዚአሠራና እና ሠራተኛ ግንኙነት ዹሌለ መሆኑን ዚሚያሳይ ሆኖ እያለ ዚበታቜ ፍርድ ቀቶቜ ዚሥራ ውል አላግባብ ተቋርጧል በማለት ዚተለያዩ ክፍያዎቜ እንድኚፍል መወሰናቾው መሠሚታዊ ዹሕግ ስህተት ያለበት ስለሆነ በሰበር ታይቶ እንዲታሚምልኝ በማለት አመልክቷል፡፡ ተጠሪ ሐምሌ 17 ቀን 2005 ዓ.ም በተፃፈ መልስ እኔ በራሎ ኃላፊነት ሳይሆን በአመልካቜ ኃላፊነትና ቁጥጥር ሥር ሆኜ ሥራ ዚምሠራ ሠራተኛ ነኝ፡፡ ሬዲዮሎጅስት አገልግሎት ዚሚሰጥበት ዚሙያ ዘርፍ ነው፡፡ አመልካቜ ኹሚገኘው ደመወዝ በዚወሩ ዚሥራ ግብር 2,433.65(ሁለት ሺ አራት መቶ ሰላሣ ሶስት ብር ኚስልሣ አምስት ሣንቲም ) እዚቀነሰ ያስቀራል እንጅ በቀን ሁለት ሰዓት መስራት ዚአመልካቜና ዚእኔን ዚስራ ውል ስምምነት  ዚሚያሳይ  እንጂ ዚአመልካቜ ሰራተኛ አለመሆኔን ዚሚያሳይ አይደለም፡፡ ስለዚህ ዚበታቜ ፍርድ ቀቶቜ ዚሰጡት ውሣኔ ይጜናልኝ በማለት ተኚራክሚዋል፡፡ አመልካቜ ሐምሌ 29 ቀን 2006 ዓ.ም ዹተፃፈ ዚመልስ መልስ አቅርበዋል፡፡

    4. ኚሥር ዚክርክሩ አመጣጥና በሰበር ዹቀሹበው ክርክር ኹላይ ዹተገለፀው ሲሆን  እኛም ዚበታቜ ፍርድ ቀቶቜ በአመልካቜና በተጠሪ መካኚል በአዋጅ ቁጥር 377/1996 ዹሚሾፈን ዚአሠሪና ሠራተኛ ግንኙነት አለ፣ አመልካቜ ኹሕግ አግባብ ውጭ ዚሥራ ውሉን አቋርጧል በማለት ዚተለያዩ ክፍያዎቜ አመልካቜ ለተጠሪ እንዲኚፍል ዹሰጠው ዹሕግ መሠሚት ያለው ነው ወይስ አይደለም ዹሚለውን ጭብጥ በመያዝ ጉዳዩን መርምሚናል፡፡

    5. ጉዳዩን እንደመሚመርነው ተጠሪ “በሬድዮሎጂ” ዹሕክምና ሙያ ዚስልጠና በቂ ዕውቀትና ክህሎት ያለውና ዚደንብ ቁጥር 76/1994 አንቀፅ 20 በሚደነግገው መሠሚት በሕግ ሥልጣን ኹተሰጠው አካል በሙያው ዹሕክምና አገልግሎት ለመስጠት ዚሚያስቜለው ዚሙያ ብቃት ማሚጋገጫ ዚምስክር ወሚቀት ዹተሰጠው ባለሙያ መሆኑ በግራ ቀኙ ክርክርና ማስሚጃ ተሚጋግጧል፡፡ ኹዚህ በተጚማሪ ተጠሪ ኚጥር 1 ቀን 2000 ዓ.ም ጀምሮ በአመልካቜ ድርጅት በቀን ለሁለት ሠዓት ያህል በመገኘት ኚአመልካቜ ጋርበፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2641 በሚደነግገው መሠሚት ዚሆስፒታል ውል ኹተዋዋሉ ዚአመልካቜ ደንበኞቜ ዚሙያ አገልግሎት ሲሰጥ ዹቆዹ መሆኑና ተጠሪ ለሚሰጠው አገልግሎት አመልካቜ በዚወሩ ብር 8000 /ስምንት ሺ ብር/ክፍያ ሲኚፍለው  ዹኖሹ መሆኑ በግራ ቀኙ ክርክርና ማስሚጃ ተሚጋግጧል፡፡

    6. አመልካቜ እና ተጠሪ ኹላይ ዹተገለፀው አይነት ዹውል ግንኙነት ዚነበራ቞ው መሆኑ አያኚራክርም፡፡ አኚራካሪው ጉዳይ ይኜ በአመልካቜና በተጠሪ መካኚል ፀንቶ ዹኖሹው ግንኙነት ዚአሠሪና ሠራተኛ ግንኙነት ነው ወይስ ዚዕውቀትና ዚሙያ ሥራ ለማኚራዚት ዹተደሹገ ዹውል ግንኙነት ነው? ዹሚለው ነጥብ ነው፡፡ ይህንን ጭብጥ ለመወሰን በአመልካቜ ተጠሪና ዹሕክምና አገልግሎት በሚሰጣ቞ው ህሙማን /ዚአመልካቜ ደንበኞቜ


    መካኚል ዹሚኖሹውን ግንኙነት መመልኚት ያስፈልጋል፡፡ ኹላይ እንደተገለፀው አመልካቜ በደንብ ቁጥር 76/94 አንቀጜ 20 እና ተኚታይ ድንጋጌዎቜ መሠሚት በሙያው ዹሕክምና ግልጋሎት ለመስጠት ዚሙያ ብቃት ማሚጋገጫ ሰርተፊኬት ያለው ባለሙያ ነው፡፡ኚዚህ በተጚማሪ አመልካቜ ዚፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2140 በሕክምና ባለሙያዎቜ ላይ ዚሚጥለው ግዎታና በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2646(1) መሠሚት ለሚሰጠው አገልግሎት ዚአመልካቜ ደንበኛ ኹሚኹፍለው ክፍያ ተጠሪ ምን ያህል ገንዘብ በወር ሊኹፈለው እንደሚቜል በውል በመስማማት፣ሙሉ በሙሉ በአመልካቜ ተቆጣጣሪነትና አሠሪነት እዚተመደበ ሳይሆን ፣በቀን ለሁለት ሠዓቶቜ ሙያዊ አገልግሎትዚሚሰጥ ባለሙያ መሆኑን ዚግራ ቀኙ ክርክርና በበታቜ ፍርድ ቀቶቜ ዚተሚጋገጡት ፍሬ ጉዳዮቜ ያሳያሉ፡፡

    7. ዚአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ ዚተፈፃሚነት ወሰን በዝርዝር ዹሚደነግገው በአዋጅ ቁጥር 397/96 አንቀፅ 3 ፣ንዑስ አንቀፅ (1) አዋጅ በአሠሪና ሠራተኛ መካኚል በሚደሹግ በቅጥር ላይ ዹተመሠሹተ ዚሥራ ግንኙነት ላይ ተፈፃሚ እንደሚሆን በመርህ ደሹጃ ደንግጓል፡፡ አዋጅ በዚህ ጠቅላላ መርህ ዚማይካተቱና ዚቅጥር ላይ ዚተመሰሚቱ ዚሥራ ግንኘነቶቜ በአዋጅ ቁጥር 377 አንቀጜ 3 ንዑስ አንቀጜ 2 በልዩ ሁኔታና በዝርዝር ደንግጓል፡፡ ዹአዋጅ አንቀፅ 3 ንዑስ አንቀፅ 2 ድንጋጌ ቃል በቃል ሲነበብ ‹‹ይህ አዋጅ ኹዚህ በታቜ በተዘሚዘሩት በቅጥር ላይ በተመሠሚቱ ዚሥራ ግንኙነቶቜ ላይ ተፈፃሚ አይሆንም ›› ዹሚል ይዘት ያለው ሲሆን በአዋጅ አንቀጜ 3 ንዑስ አንቀጜ 2 በዝርዝር ኹተደነገጉ አዋጅ ተፈፃሚነት ኚማይሆንባ቞ው ግንኙነቶቜ ውስጥፀአንድ ተዋዋይ ወገን ዋጋ እዚተኚፈለው በራሱ ዚንግድ ሥራ ወይም በራሱ ዚሙያ ኃላፊነት ዚሚሠራ ስራ ዚሚያኚናውን ሲሆን፣አዋጅ ቁጥር 377/96 ድንጋጌዎቜ ተፈፃሚነት ዹሌላቾው መሆኑ በአዋጅ አንቀጜ 3 ንዑስ አንቀጜ 2(1) ተደንግጓል፡፡

    8. ኹላይ እንደተገለፀው ተጠሪ ሙሉ በሙሉ በአመልካቜ መሪነትና ቁጥጥር ሣይሆን በአመልካቜ ድርጅት ውስጥ በቀን ለሁለት ሠዓት ያክል ኚአመልካቜ ጋር ዚሆስፒታል ውል ለተዋዋሉ ዚአመልካቜ ደንበኞቜ ዚራድዮሎጅ ዚሙያ ግልጋሎት በራሱ ዚሙያ ኃላፊነት ዚሚሰጥ ነው፡፡ አመልካቜ ተጠሪ ይህንን ዚሙያ ግልጋሎቱን ሌላ ቊታ ዹሚገኝ ዹህክምና ተቋም ወይም ኚአመልካቜ ጋር ምንም አይነት ዚሆስፒታል ውል ግንኙነት ለሌላቾውና ዚአመልካቜ ዹህክምና ካርድ ላልያዙ ሰዎቜ እንዲሰጥናዚሥራ ስምሪት መስጠትና አመልካቜን ተቆጣጥሮ ማሠራት አይቜልም፡፡ ኹዚህ  በተጚማሪ ተጠሪ ዹአዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀፅ 61 እና ተኚታታይ ድንጋጌዎቜ መሠሚት በቀን ሥምንት ሠዓት በሣምንት አርባ ሥምንት ሠዓት ኚሥራ ቊታ እንዲገኝ ለማስገደድና ተቆጣጥሮ ማሰራት እንደማይቜል ዚግራ ቀኙ ክርክርና ኚበታቜ ፍርድ ቀቶቜ ውሣኔ ተሚድተናል፡፡

    9. ዚሥር ፍ/ቀት ተጠሪ በቀን ለሁለት ሠዓት ብቻ አገልግሎት መስጠቱፀ ኚአመልካቜ ጋርበአዋጅ ቁጥር 377/96 ዹሚሾፈን ዚአሠሪና ሠራተኛ ግንኙነት ኚመመስሚት አይገድበውም በማለት ውሣኔ ሰጥቷል፡፡ ሆኖም ይህ ዚስር ፍርድ ቀት ዹሰጠው ዹሕግ ትርጉምና ውሳኔ ዹአዋጅ ቁጥር 377/1996 ኹአንቀፅ 61 እስኚ አንቀፅ  64 ዚተደነገጉትን ድንጋጌዎቜ ይዘትና ውጀት ያገናዘበ ካለመሆኑም በላይ ፣በአዋጅ አንቀጜ 65 ልዩ ድንጋጌ ያገናዘበ ሆኖ አላገኘነውም፡፡ በአዋጅ አንቀጜ 65 መሠሚት በሥራ ውሉ  ወይም በህብሚት ስምምነት በሌላ አኳኃን ካልተወሰነ በስተቀር ፣ዚአዋጁ ዚስራ ሰዓት ዚሚመለኚቱት ኚአንቀጜ 61 እስኚ አንቀጜ 64 ዚተደነገጉት ድንጋጌዎቜ ተፈፃሚነት ዚማይኖራ቞ው በንግድ መልዕክተኞቜ በንግድ ወኪሎቜ ላይ እንደሆነ በግልፅ ተደንግጎአል፡፡ ኹዚህ አንፃር


    ዚሥር ፍርድ ቀት ዹአዋጅ ዚሥራ ሠዓት ድንጋጌዎቜ ተጠሪ ዚአመልካቜ ቅጥር ሰራተኛ ነው ብሎ ለመወሰን ተፈፃሚነት እንደሌላ቞ው በመግለፅ ዹሰጠው ትርጓሜ ዹአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀፅ 65 ልዩ ድንጋጌ ያላገናዘበና መሠሚታዊ ዹሕግ ስህተት ያለበት ሆኖ አግኝተነዋል፡፡

    10. ኹላይ በዝርዝር ዚተገለፁት ምክንያቶቜ ተጠሪ በአዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጜ 3 ንዑስ አንቀፅ 2/1) መሠሚት ኚአመልካቜ ቁጥጥርና ዚሥራ አለመሚዳት ሣይገደብ በራሱ ዚሙያ ኃላፊነት በቀን ለሁለት ሠዓት ዚራዲዮሎጅ ዚሙያ አገልግሎት ዚሚሰጥ ባለሙያ እንጅ ዚአመልካቜ ሠራተኛ አይደለም፡፡ ተጠሪ ለአመልካቜ ዹሚሰጠው ዚእውቀት  ግልጋሎት እና ሥራ ውል በመሆኑ አመልካቜ በማናቾውም ጊዜ ውሉን ለማፍሚስ ዚሚቜል መሆኑን በፍትሐብሔር ህግ ቁጥር 2638 ንዑስ አንቀጜ 1 ተደንግጓል፡፡ ይህም በመሆኑ አመልካቜ አግባብነት ያለውንና ተፈፃነሚነት ያለውን ዹህግ ድንጋጌ መሠሚት በማድሚግ አለኝ ዹሚለውን መብትና ጥቅም ኹሚጠይቅ በስተቀር ተጠሪ ዹአዋጅ ቁጥር 377/1996 ድንጋጌዎቜ መሠሚት ዚተለያዩ ክፍያዎቜ እንዲኚፍለው ዹመጠዹቅ መብት ዹለውም ። በመሆኑም ዚበታቜ ፍ/ቀቶቜ ዚሰጡት ውሳኔ ኹላይ በዝርዝር ዚጠቀስና቞ውን ዹሕግ ድንጋጌዎቜ ዚሚጥስና መሠሚታዊ ዹሕግ ስህተት ያለበት ነው በማለት ወስነናል፡፡

     ው ሣ ኔ

     

    1. ዚፌዎራል ዚመጀመሪያ ደሹጃ ፍርድ ቀትና ዚፌዎራል ኹፍተኛ ፍርድ ቀት ዚሰጡት ውሳኔ ተሞሯል ፡፡

    2. ተጠሪ በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጜ 3 ንዑስ 2(1) መሠሚት በራሱ ዚሙያ ኃላፊነት በቀን ለሁለት ሠዓት ዚሙያ አገልግሎት ዚሚሠጥ በመሆኑ ዚአመልካቜ ቅጥር ሠራተኛ ሣይሆን ዚዕውቀት ሥራና ግልጋሎት ለመሰጠት ዹተዋዋለ ባለሙያ ነው በማለት ወስነናል፡፡

    3. አመልካቜ ኚተጠሪ ጋር ዹነበሹውን ዚሙያ (ዕውቀት)ሥራ ግልጋሎት ውል ያቋሚጠው በፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 2637 ንዑስ አንቀፅ 1 መሠሚት ነው በማለት ወስነናል፡፡

    4. ይኜ ውሣኔ ተጠሪ ዚሙያ ግልጋሎት ውሉ በመቋሚጡ ምክንያት አለኝ ዹሚለውን ዚመብት ጥያቄ ኚማቅሚብ ዚሚገድበው አይደለም ብለናል፡፡

    5.  በዚህ ፍርድ ቀት ዚወጣውን ወጭና ኪሣራ ግራ ቀኙ ለዚራሳ቞ው ይቻሉ፡፡

     

     

     

    ዚማይነበብ ዚአምስት ዳኞቜ ፊርማ አለበት ፡፡

  • አንድ አሠሪ ለሙኚራ ዹቀጠሹውን ሠራተኛ በቀጠሹው በ46ኛው ቀን ለስራው ብቁ አይደለም ብሎ ዚስንብት ደብዳቀ ቢጜፍለት ድርጊቱ ህገ ወጥ ነው ሊባል ዚማይቜል ስለመሆኑ፣

     

    አዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጜ 11(2)፣(3)

    ዹሰ/መ/ቁ. 101890

    ጥቅምት 24 ቀን 2007 ዓ.ም.


     

    አመልካቜ፡- ዚኢትዮጵያ አዹር መንገድ- ጠበቃ አውላቾው  ደሣለኝ ቀሚቡ፡፡ ተጠሪ፡- ወ/ት ፍጹም ኃይሉ - ዹቀሹበ ዚለም፡፡

    መዝገቡ ተመርምሮ ዹሚኹተለው ፍርድ ተሰጥተናል፡፡

     ፍ ር ድ

     

    በዚህ ጉዳይ ዹቀሹበው ክርክር ዚሥራ ውሉ ማቋሚጡን ዚሚመለኚት ነው፡፡ ለዚህ ሰበር አቀቱታ መነሻ ዹሆነው ተጠሪ ያቀሚቡት ክስ ነው፡፡ ዚተጠሪ ዚዳኝነት ጥያቄ አመልካቜ ኚግንቊት 3ዐ ቀን 2005 ዓ.ም ጀምሮ በዕቃ ግምጃ ቀት ተቆጣጣሪነት በቋሚ ደመወዝ ብር 2,639 ዚቀጠራ቞ው መሆኑና ያለማስጠንቀቂያ በ12/11/2005 ዹተፃፈ ዚቅጥር ውል ማቋሚጫ ደብዳቀ በ15/11/2005 እንዲሰጣ቞ው በሕገወጥ መንገድ ኚሥራ ሰለአሰናበታ቞ው ዚተለያዩ ክፍያዎቜ ተኹፍሏቾው ወደ ሥራ እንዲመለሱ እንዲወሰን ዹሚል ነበር፡፡ ዹአሁኗ ተጠሪ ኚኢትዮጵያ አዹር መንገድ በትብብር በሚሰራ ድርጅት ተቀጥሚው ሲሰሩ ስለነበር ዚተቀጠሩት በቋሚነት ነው በማለት ያቀሚቡት ክርክር ኹቀሹበው ማስሚጃ አንፃር ተገቢነት ዹለውም በማለት ዚታለፈ ሲሆን በግራ ቀኙ ዹነበሹው ዚሥራ ውል ግንኙነት በ29/09/2005 ዓ.ም በተፃፈው ደብዳቀ ኚግንቊት 7 ቀን 2005 ዓ.ም ጀምሮ ለ45 ቀናት ዚሙኚራ ቅጥር ተቀጥሚው ሲሰሩ እንደነበር መሠሚት በማድሚግ ታልፏል፡፡

    አመልካቜ በሥር ፍርድ ቀት በተደሹገው ክርክር ተጠሪ ሊመደቡበት ላቀደው ዹዕቃ ግምጃ ቀት ዚስራ መደብ ተስማሚ መሆናቾውን ለመመዘን ለ45 ቀናት ዚሙኚራ ግዜ ተቀጥሚው ለታቀደው ሥራ ተስማሚ ያለመሆና቞ውን በማሚጋገጥ ሕጉ በሚፈቅደው አግባብ ዚሥራ ውል ማቋሚጡን ገልጿል፡፡ ዚፌዎራል መጀመሪያ ደሹጃ ፍ/ቀት ዚግራ ቀኙ ክርክር እና ማስሚጃ በማገናዘብ በሰጠው ውሣኔ ተጠሪ በሰጡት ዚምስክርነት ቃል ዚሥራ ውል ማቋሚጫ ደብዳቀ ዚተሰጣ቞ው እ.ኀ.አ ጁላይ 22/2013 ወይም ወደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር ሲመለስ ሐምሌ 15/11/2005 መሆኑን ፀ ዚአመልካቜ ምስክርም ደብዳቀው ዚተሰጣ቞ው ጁላይ 19 ቀን 2013 ወይም ሐምሌ 15 ቀን 2005 ዓ.ም ነው በማለታ቞ው ዚተጠሪ ዚሥራ ውል ማቋሚጫ ደብዳቀ ዚተሰጣ቞ው በ46ኛው ቀን ሐምሌ 15/11/2005 ዓ.ም በመሆኑ ስንብቱ ዹሕግ መሠሚት ዚለውም፡፡ አመልካቜ ለተጠሪ ያልኚፈላ቞ው ዹ22 ቀናት ቀሪ ደመወዝ እንዲሁም ዚካሣ ክፍያ እንዲኚፍላ቞ው ዚሥራ ልምድ ማስሚጃም እንዲሰጣ቞ውበማለት ወስኗል፡፡ በይግባኝ ሥልጣኑዚተመለኚተው ኹፍተኛ ፍ/ቀትም ዚአመልካቜን ይግባኝ ሰርዞታል፡፡

    አመልካቜም በሥር ፍ/ቀቶቜ ፍርድ ላይ ቅር በመሰኘት ዹሰበር አቀቱታ ያቀሚቡ ሲሆን ዚቅሬታ ነጥቡም ሲጠቃለል፡- በአመልካቜ እና ተጠሪ ዹነበሹው ዚሥራ ግንኙነት ሕጉ በሚፈቅደው አግባብ ጁላይ 19 ቀን 2013 እ.ኀ.አ በተፃፈ ደብዳቀ መቋሚጡፀ ይህ ደግሞ ወደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር ሲመለስ ሐምሌ 12 ቀን 2ዐዐ5 ዓ.ም መሆኑን እዚታወቀ ዹውል መቋሚጫ ደብዳቀ በ43ኛው  ቀን


    ተድፎ ሳለ ስንብቱ በ46ኛው ቀን ዹተደሹገ በመሆኑ ሕገ ወጥ ነው ተብሎ በሥር ፍርድ ቀት መወሰኑ ያላግባብ ነው ዹሚል ነው፡፡ ተጠሪ በበኩላ቞ው በሰጡት መልስ ኹአሁን በፊት ለ5ወር ኹ6 ቀን በማ቎ሪያል ኢንቚንተሪ ኮንትሮል ሥራ በአመልካቜ መስሪያ ቀት መሥራታ቞ው እዚታወቀ ድጋሚ በዚያው ሥራ በሙኚራ ዚቅጥር ውል መሥራታ቞ው ሕጋዊ አለመሆኑን

    ፀዚሥር ፍ/ቀት ማስሚጃዎቜ በመመዘን ውሣኔ መስጠቱ ፀዚተጠሪ ምስክሮቜ ዚሥራ ውል ማቋሚጫ ደብዳቀ እ.ኀ.አ ጁላይ 22 ቀን 2013 እንደተሰጣ቞ው ማስሚዳታ቞ውአመልካቜ በሕግ ዹተቀመጠውን 45 ቀን አሳንሶ በ43ኛው ቀን ዚስንብት ደብዳቀ መስጠት እንደማይቜልፀ ደብዳቀውም ኚሥራ ሰዓት ውጭ ዚተሰጣ቞ው መሆኑንበመግለጜ ዚሥር ፍ/ቀት እንዲፀና አመልክቷል፡፡ አመልካቜም ተጠሪ ላቀሚቡት መልስ ዚመልስ መልስ በማቅሚብ አቀቱታውን በማጠናኹር ተኚራክሯል፡፡

    ዚጉዳዩ አመጣጥ አጠር አጠር ባለ መልኩ ኹላይ ዹተገለፀው ሲሆን ይህ ቜሎትም ዚግራ ቀኙክርክር ለሰበር አቀቱታ መነሻ ኹሆነው ውሳኔ እና አግባብነት ካላ቞ው ድንጋጌዎቜ ጋር በማዛመድ ጉዳዩ ለሰበር ቜሎት ሲቀርብ ኚተያዘው ጭብጥ አንፃር በሚኹተለው መልኩ መርምሮታል፡፡

    ኚሥር ፍርድ ቀት መዝገብ መሚዳት እንደተቻለው በአመልካቜ እና ተጠሪ በሙኚራ ጊዜ ላይ ዚተመሰሚቱ ዚሥራ ቅጥር ውል መፈፀሙን ነው፡፡ ተጠሪ ኚድርጅቱ ጋር ግንኙነት ባለው ሌላድርጅት በዚህ ዚሥራ መደብ ላይ ሲሰሩ እንደነበር በድጋሚ በተመሳሳይ ዚሥራ መደብ ለሙኚራ መቀጠራ቞ው ሕጋዊ አለመሆኑን በመጥቀስ ቢኚራኚሩም ዚሥር ፍርድ ቀት  ለሙኚራ ዚተቀጠሩበት ደብዳቀ በማስሚጃነት በመውሰድ ክርክራ቞ው አግባብነት ዹሌለው መሆኑን በውሣኔው አስፍሯል፡፡ ተጠሪ ይህንን ውሣኔ በመቃወም ያቀሚቡት ይግባኝ ይሁን መስቀለኛ አቀቱታ ዚለም፡፡ በዚህ ሚገድ በሰበር አቀቱታ቞ው በሥር መጀመሪያ ደሹጃ ፍ/ቀት ውድቅ ዹተደሹገው ክርክር በሰበር ደሹጃ ማቅሚባ቞ው ሥነ-ስርዓታዊ አካሄድ ዹተኹተለ አይደለም፡፡

    አንድ ሠራተኛ ሊመደብበት ለታቀደው ቊታ ተስማሚ መሆኑና አለመሆኑን ለመመዘን ለሙኚራ ጊዜ ሊቀጠር እንደሚቜልፀ ይህ ዚግራ ቀኙ ስምምነትም በጜሑፍ መደሹግ እንዳለበትፀ ዚሙኚራ ጊዜውም ኹ45 ተኚታታይ ቀናት መብለጥ እንደሌለበት ኚአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ ቁጥር 377/96 አንቀጜ 11(1) ፣(2) እና (3) አጠቃላይ ይዘትና መንፈስ ዹምንገነዘበው ነው፡፡ አመልካቜ ተጠሪን ለሙኚራ ጊዜ መቅጠሩ በሥር ፍ/ቀት ዚታመነበት ጉዳይ ነው፡፡ አመልካቜ ተጠሪን በግዜ ገደቡ ውስጥ ማሰናበቱን ሲኚራኚር ተጠሪ ደግሞ በ46ኛው ቀን ዚተሰናበቱ መሆናቾው በመግለፅ ስንብቱ ህገ ወጥ እንዲባልላ቞ው አመልክተዋል፡፡ በስር ፍ/ቀት ዚአመልካቜ ምስክሮቜ ስንብቱ እ.ኀ.አ. ጁላይ 19 ቀን 2013 መሆኑን ይህ ደግሞ ወደ ኢትዮጵያ ዹጊዜ አቆጣጠር ሲመለስ ሐምሌ 15 ቀን 2005 ዓ.ም መሆኑን በሥር ፍርድ ቀት መዝገብ ሰፍሯል፡፡ ተጠሪ በሰጡት ዚምስክርነት ቃል ዚስንብት ደብዳቀው እ.ኀ.አ. ጁላይ 22 ቀን 2013 መሆኑፀዚጊዜ ስሌቱ ሲሰራ ኚተቀጠሩበት ጊዜ ጀምሮ በ46ኛው ቀን መሆኑን ገልጿል፡፡ ዚሥር ፍርድ ቀቱ ዚአመልካቜ ድርጊት ሕገወጥ ነው ለማለት እንደመነሻ ዹወሰደው ተጠሪን በ46ኛው ቀን ኚሥራ አሰናብቷል በሚል ነው፡፡ አመልካቜ ተጠሪን ያሰናበታ቞ው በ43ኛ ቀን ነው?ወይስ በ46ኛው ቀን?በ46ኛው ቀን ሲሰናበቱ ሕጋዊ ውጀቱስ ዹተለዹ ሊሆን ይቜላል? ዹሚለው መመልኚቱ ተገቢ ነው፡፡ ዚሥር ፍ/ቀት በአመልካቜ ተሰጠ ዚተባለው ደብዳቀ እ.ኀ.አ አቆጣጠር ጁላይ 19 ቀን 2013 ዓ.ም ዚተጻፈ መሆኑ ወደ ኢትዮጵያ ዹጊዜ አቆጣጠር ሲመለስ                         ደግሞ ሐምሌ 15 ቀን 2ዐዐ5 ዓ.ም  መሆኑን በውሣኔው አስፍሯል፡፡ ዚሥር ፍርድ ቀት እ.ኀ.አ. ጁላይ 19 ቀን 2013 ወደ ኢትዮጵያ ዹጊዜ አቆጣጠር ሲመለስ  ሐምሌ  15  ቀን 2ዐዐ5  ዓ.ም  በማለት በውሣኔ  ዹተጠቀሰው  ተቀባይነት

    /conventional/ ካልሆነው ዹጊዜ አቆጣጠር ቀመር አኳያ ሲታይ አግባብነት ያለው አይደለም፡፡ ኹላይ ዹተገለፀው ጁላይ 19 ቀን 2ዐ13 ወደ ኢትዮጵያ ዹጊዜ አቆጣጠር ሲመለስ ሐምሌ 12  ቀን


    2ዐዐ5 ዓ.ም መሆኑን ተቀባይነት ካለው ዹጊዜ አቆጣጠር /ካላንደር/ አንፃር በማዛመድ በቀላሉ ግንዛቀ ዚሚወሰድበት ነው፡፡ በመሆኑም ዚሥር ፍርድ ቀት ጁላይ 19 ቀን 2ዐ13 እ.ኀ.አ ወደ ኢትዮጵያ ዹጊዜ አቆጣጠር ሲመለስ ሐምሌ 15 ቀን 2ዐዐ5 ዓ.ም ነው፡፡ በማለት ማስፈሩ አግባብነት ያለው ሆኖ አልተገኘም፡፡ አመልካቜ ተጠሪን ሐምሌ 12 ቀን 2ዐዐ5 ዓ.ም በፃፈው ደብዳቀ ዚሙኚራ ግዜ ቅጥር ውል እንዲቋሚጥ ዹተደሹገ ኹሆነ በ45 ቀን ጊዜ ገደብ ውስጥ ዹተፃፈ ደብዳቀ መሆኑ መሚዳት ይቻላል ፡፡ አመልካቜ ተጠሪ ሊመደቡበት ለታቀደው ቊታ ተስማሚ መሆኑን አለመሆናቾው በ45 ቀን ውስጥ ውሣኔ ማስተላለፍ ለዚህ ጉዳይ አግባብነት ካለው ሕግ ጋር ዹሚቃሹን ውሣኔ አይደለም፡፡

    ዚሥር ፍርድ ቀት ዚአመልካቜ ድርጊት ሕገወጥ ነው በማለት ለመወሰን እንደ መነሻ ዹወሰደው ስንብቱ በ46ኛው ቀን ተኹናውኗል በሚል ነው፡፡አንድ አሠሪ ዚሙኚራ ጊዜ ውል ያለአግባብ በማሳጠር ይሁን ኚሚገባው በላይ ጊዜው በማራዘም ዚሠራተኛው ዹተሹጋጋ ዚሥራ ዋስትና እንዳይኖር ማድሚግ እንደሌለበት ኹአጠቃላይ ዚአሠሪና ሠራተኛ አዋጅቁ. 377/96 ድንጋጌዎቜ ዹምንገነዘበው ጉዳይ ነው፡፡ ይሁንና አሠሪው በ45ኛው ቀን መጚሚሻ ይሁን በ46ኛው ቀን መጀመሪያ ሠራተኛው ለተመደበበት ዚሥራ ቊታ ተስማሚ አይደለም በማለት ኹወሰነ ዹፈጠነ ወይም በጣም ዹዘገዹ ውሣኔ ነው ለማለት አይቻልም፡፡ ዚሙኚራ ግዜው በ45ኛው ቀን መጚሚሻ ዹሚጠናቀቅ ኹሆነ በ46ኛው ዚመጀመሪያ ቀን ዚስንበት ደብዳቀ መፃፉ ዚሠራተኛው ዚሥራ ዋስትና አደጋ ውስጥ አስገብቷል ለማለት ዚሚያስቜል አሳማኝ ምክንያት ዚለውም፡፡ በሥር ፍ/ቀት ተሹጋግጧል ዚተባለው ፍሬ ነገር ተወስዶ ደብዳቀው በ46ኛው ቀን ነው ዹተፃፈው ቢባል እንኳ ዚአሠሪው ዚማሰናበት መብትና ሥልጣን ዘግይቶ ተግባራዊ ዹተደሹገ ነው ሊባል አይቜልም፡፡ ዚሙኚራ ጊዜ ውል ለ 45 ተኚታታይ ቀናት ዚሚቀጥል ኹሆነ ግለሰቡ በመጚሚሻው ቀን በመገምገም ለታቀደው ቊታ ተስማሚ ነው ወይስ አይደለም ዹሚለውን ውሣኔ ለማስተላለፍ ዚመጚሚሻ ቀን ዚሥራ አፈፃፀም ውጀት ጭምር ታሳቢ መደሹግ ያለበት በመሆኑ በ46ኛው ቀን ዚስንብት ደብዳቀ መፃፉ ዹሕጉን ይዘትና መንፈስ ዹሚቃሹን አይደለም፡፡ ስለሆነም ዚሥር ፍ/ቀቶቜ ግራ ቀኙ እያኚራኚሚ ያለውን ጉዳይ በአግባቡ ሳያገናዝቡ ዚሙኚራ ጊዜ ኹ45 ቀናት መብለጥ ዚለበትም ዹሚለውን ዹሕጉ ይዘት ኹአጠቃላይ ዹሕጉ ዓላማና ግብ ሳያገናዝቡ መወሰናቾው በአግባቡ አይደለም ብለናል፡፡ በዚህ ሁሉ ምክንያት ዚሥር ፍ/ቀቶቜ ዚአመልካቜ ድርጊት ሕገወጥ ነው በማለት መወሰናቾው መሠሚታዊ ዹሕግ አተሹጓጐም ስህተት ፈጜመዋል፡፡ በመሆኑም ተኚታዩን ወስነናል፡፡

     ት ዕ ዛ ዝ

    1. ዚፌዎራል ዹመ/ደ/ፍ/ቀት በኮ.መ.ቁ.85529 በ18/07/2006 ዓ.ም እንዲሁም ዹፌ/ኹ/ፍ/ቀት በኮ.መ.ቁ. 139947 በ19/07/2006 ዚሰጡት ፍርድ እና ትዕዛዝ ተሜሯል፡፡

    2.  አመልካቜ ተጠሪ ያለማስጠንቀቂያ ማሰናበቱ በአግባቡ ነው ብለናል፡፡

    3. ለዚህ ወጪና ኪሳራ ግራ ቀኙ ዚዚራሳ቞ው ይቻሉ፡፡ መዝገቡ ተዘግቷል፡፡ ወደ መዝገብ ቀት ይመለስ፡፡

     

    ብ/ግ                                     ዚማይነበብ   ዚአምስት ዳኞቜ ፊርማ አለበት፡፡

  • በገጠር መሬት ላይ ዹሚኖሹው መብት ዹመጠቀም መብት ሲሆን ይህንን መብት ለ3ኛ ወገን /ለሌላ/ ሰው ለሹጅም ጊዜ ሰጥቶ ተጠቃሚነቱ ዚተቋሚጠበት ባለመብት መልሶ መጠዹቅ ዚማይቜል ስለመሆኑ፣ ዚኊሮሚያ ክልለ ዹገጠር መሬት አጠቃቀም አዋጅ ቁጥር 130/1997 አንቀፅ 9(5)

     

    ዹሰ/መ/ቁ. 113973

    ቀን 21/04/2008 ዓ/ም

    ዳኞቜ፡- ተሻገር ገ/ስላሎ

     

    ሙስጠፋ አህመድ ተፈሪ ገብሩ

    ሞምሱ ሲርጋጋ ፈይሳ ወርቁ

    አመልካቜ፡- ወ/ሮ ጠጅቱ ኡርጋ - ቀሚቡ ተጠሪ፡- አቶ ገመዳ ሬባ - አልቀሚቡም

    መዝገቡን መርምሹን ተኚታዩን ፍርድ ሰጥተናል፡፡

     

     ፍ ር ድ

     

    ጉዳዩ ዚባልና ሚስት ንብሚት ክርክርን ዚሚመለኚት ሲሆን ክርክሩ ዹጀመሹው በኊሮሚያ ክልል ምዕራብ ሾዋ ዞን ሜታ ሮቢ ወ/ፍ/ቀት ነው፡፡ አመልካቜ በዚህ ወሚዳ ፍ/ቀት ባለቀታ቞ው በነበሩት አቶ አሰፋ ገመዳ ላይ ክስ ዚመሰሚቱት ኀዎ ኚተባለ አኚባቢ ዹሚገኝ ሁለት ዚበሬ መዋያ  መሬት እና ሰምንተኛ ተብሎ ኚሚጠራው አካባቢ ግማሾ ዚበሬ መዋያ ይዞታ መሬታቜንን እኩል እንደንካፈል ይወሰንልኝ ዹሚል ሲሆን ተኚሳሜ በበኩላ቞ው ዹተጠቀሰው ይዞታ መሬት ዚጋራ ይዞታቜን አይደለም ሊካፈል አይገባም ብለዋል፡፡ ዹአሁኑ ተጠሪ ወደ ክርክሩ ጣልቃ ገብተው ግራ ቀኙ ዚሚኚሚኚሩበት መሬት ዹግል ይዞታዬ ነው በስሜ ተለኚቶ ዹሚገኝ እና በስሜ ዚምግብርበት ነው ኚሳሜና ተኚሳሜ በዚህ መሬት ላይ አንዳቜም መብት ዹላቾውም ብለው ተኚራካሚዋል፡፡

     

    ኚሳሜ (ዹአሁኑ አመልካቜ) በበኩላ቞ው ለክርክር ምክንያት ዹሆነውን መሬት በ1994 ዓ/ም ኚተኚሳሜ ጋር ስንጋባ ዚተኚሳሜ አባት ዚሆኑት ጣልቃ ገብ ሰጥተውን በጋብቻ ውላቜን ላይም ተጠቅሶ ኹ1994 ዓ/ም ጀምሮ በይዞታቜን ስር ሆኖ ስንጠቀምበት ቆይተናል፡፡ ሰሞንኛ ተብሎ ኚሚታወቀው አካባቢ ባለን ይዞታ ላይ ቀት ያለን ሲሆን በመ/ቁ. 15710 እና 14792 በሆኑ መዝገቊቜ በዚህ ቀት ውስጥ ሆኜ ልጆቜን እንደሳደግ ፍ/ቀት አዞልኛል ዚጣልቃ ገብ አቀቱታ ውድቅ ይደሹግልኝ ብለው ተኚራኚሚዋል፡፡


    ፍ/ቀቱ ዚግራ ቀኙ ምስክሮቜን ሰምቶ ክርክራ቞ው ኹቀሹበው ማስሚጃ ጋር በማገናዘብ መርምሮ ለክርክር ምክንያት ዹሆነው መሬት በጋብቻ ውሉ ላይ ዹተመዘገበ እና ኚሳሜና ተኚሳሜ ይዘውት ሲጠቀሙበት ዚቆዩ በመሆኑ ጣልቃ ገብ ዚመሬቱ ይዞታ በስማ቞ው ዹሚገኝና ግብር በስማ቞ው ዚሚገብርብት ቢሆንም ኚሳሜና ተኚሳሜ ይዘው ዚሚጠቀሙበትን መሬት ጣልቃ ገብ መጠዹቅ አይቜሉም ለክርክር ምክንያት ዹሆነውን መሬት ኚሳሜና ተኚሳሜ እኩል ይካፈሉ በማለት ወስኗል፡፡

     

    ጣልቃ ገብ (ዹአሁኑ ተጠሪ) በዚህ ውሳኔ ላይ ቅሬታ቞ውን ለምዕራብ ሾዋ ዞን ኹፍ/ፍ/ቀት አቅርበዋል፡፡ ፍ/ቀቱ ግራ ቀኙን አኚራክሮ ለክርክር ምክንያት ዹሆነውን መሬት ዚስር ኚሳሜና ተኚሳሜ ሲጋቡ ይ/ባይ (ዚስር ጣልቃ ገብ) ዹሰጠው መሆኑን ዚስር ኚሳሜ ምስክሮቜ ያስሚዳ ቢሆንም መሬት ዹሚሰጠው በቃል ሳይሆን በጜሁፍ ማስሚጃ ሆኖ ስልጣን ባለው አካል መመዝገብ እንዳለበት ኹገጠር መሬት አዋጅና ኹፍ/ብ/ህ/ቁ. 1723 መሚዳት ይቻላል፡፡ መሬቱ ዚጣልቃ ገብ መሆኑ ተሚጋግጧል፡፡ ለይግባኝ መልስ ሰጭ ኚባለቀታ቞ው ጋር በህጋዊ  መንገድ ዹተሰጠ ስለመሆኑ ሳይሚጋገጥ ዚጋብቻ ውሉም ለወደፊቱ ኚአባታቜን ላይ ዹምናገኛው መሬት ዹሚል በመሆኑ እና ኚዚያ ወዲህም ዹተደሹገ ስጊታ ዹሌለ በመሆኑ ክርክር ያስነሳው መሬት ዚይግባኝ ባይ (ዚስር ጣልቃ ገብ) ይዞታ ነው በማለት ዚስር ፍ/ቀትን ውሳኔ በመሻር ወስኗል፡፡

     

    ዹአሁኑ አመልካቜ በዚህ ውሳኔ ላይ ቅሬታ቞ውን ለኊሮሚያ ክልል ጠ/ፍ/ቀት በይግባኝ አቅርበው ፍ/ቀቱ ግራ ቀኙን አኚራክሮ በሰጠው ውሳኔ ክርክር ያስነሳውን መሬት ይ/ባይ ኚስር ተኚሳሜ ጋር በሚጋቡበት ጊዜ በጋብቻ ውላቾው ላይ ዹተገለጾ እና ኚዚያ ወዲህ ይ/ባይ ኚባለቀታ቞ው ጋር እዚተጠቀሙበት ዚቆዩ መሆኑ ተመስኚሯል ዹቀበሌው አስተዳደር ለወሚዳ ፍ/ቀት በጻፈው ሪፖርት ላይም መሬቱን ተጋቢዎቹ በጋራ ሲጠቀሙበት ዚቆዩ መሆኑን ገልጿል፡፡ ዚመሬት እና አካባቢ ጥበቃ ጜ/ቀት ለወ/ፍ/ቀት በጻፈው ደብዳቀ መሬቱ በመልስ ሰጭ (በስር ጣልቃ ገብ) ስም ዚተለካ መሆኑን ነገር ግን እዚተጠቀሙበት ያሉት ተጋቢዎቹ መሆናቾውን ገልጿል፡፡ መሬቱ በጋብቻ ውል ላይ ዹተጠቀሰ መሆኑን ግራ ቀኙ አልተካካዱም ኚዚያ ወዲህም ተጋቢዎቹ ሲጠቀሙበት ዚቆዩ መሆኑ በማስሚጃ ተሚጋግጧል፡፡ መ/ሰጭ በስሙ በመመዝገቡ ብቻ እስካሁን ያልተጠቀሙበትን መሬት በስሜ ተለክቷል በማለት ያቀሚቡት መኚራኚሪያ ተቀባይነት ዚለውም፡፡ ቀት ዚሰሩበትን መሬት ይ/ባይ ቀደም ሲል እንደኖርበት በፍ/ቀት ተውስኖልኛል ብለው ያቀሚቡትን መኚራካሪያ መ/ሰጭ አላስተባበሉም ክርክር ያስናሳውን መሬት ይ/ባይ ኚባለቀታ቞ው ጋር ሊካፈሉ ይገባል በማለት ዹኹፍ/ፍ/ቀቱን ውሳኔ በመሻር ወስኗል፡፡ ዹአሁኑ ተጠሪ በዚህ ውሳኔ ላይ ያላ቞ውን ቅሬታ ለማስሚም ለኊሮሚያ ክልል ጠ/ፍ/ቀት ሰበር ቜሎት አቀቱታ አቅርበዋል፡፡ ሰበር ቜሎቱም ዚግራ ቀኙን ክርክር እና ዚስር ፍ/ቀቶቜን ውሳኔ በማገናዘብ መርምሮ ለክርክሩ ምክንያት ዹሆነውን መሬት ተጠሪዋ ኚባለቀቷ አባት (ኚአመልካቜ) ያገኙትና ለ9 ዓመት ሲጠቀሙበት ዚቆዩ መሆኑ  በምስክሮቜ  ተሚጋግጧል፡፡  ይሁን  እንጂ  ዹገጠር  መሬት  አጠቃቀም  ደንብ    እና


    ፍ/ብ/ህ/ቁ.1723 መሰሚት ዹገጠር መሬት ስጊታ በጜሁፍ መሆንና መመዝገበ አለበት ተጠሪ መሬቱን በጋብቻ ወቅት በስጊታ ያገኙ ስለመሆኑ አግባብነት ያለው ማስሚጃ አቅርበው ያላሚጋገጡ በመሆኑ ክርክር ያስነሳው መሬት ዚአመልካቜ (ዚስር ጣ/ገብ) ይዞታ ነው በማለት ወሚዳ እና ዹጠቅላይ ፍ/ቀት ይ/ሰሚ ቜሎት ውሳኔን በመሻር ወስኗል፡፡

     

    አመልካቜ በዚህ ውሳኔ ላይ ያላ቞ውን ቅሬታ በመዘርዘር እንዲታሚምላ቞ውን አቀቱታ አቅርበዋል፡፡ አቀቱታው ተመርምሮ አመልካቜ አኚራካሪውን 2 ጥማድ እርሻ መሬት ኹ1994 ዓ/ም ጀምሮ ኚስር ተኚሳሜ ጋር እስኚተፋቱበት ጊዜ 2003 ዓ/ም ድሚስ በጋራ ሲጠቀሙ መቆዚታ቞ው ተሹጋግጩ እያለ መሬቱን ልትካፈል አይገባም ተብሎ ጥያቄዋ በክልሉ ሰበር ቜሎት  ተቀባይነት ዚማጣቱን አግባብነት ለመመርመር ተጠሪ መልስ እንዲሰጡበት ተደርጓል፡፡ ግራ ቀኙ በጜሁፍ ክርክራ቞ውን አቅርበዋል፡፡

     

    ዚግራ ቀኙን ክርክር ለሰበር አቀቱታ መነሻ ኹሆነው ዚስር ፍ/ቀት ውሳኔ ጋር በማገናዘብ አቀቱታው እንዲመሚመር ኚተያዝው ጭብጥ አንጻር ዚስር ፍ/ቀት ውሳኔ ላይ መሰሚታዊ ዹሆነ ዹህግ ስህተት ዹተፈጾመ መሆን አለመሆኑን መርምሚናል፡፡

     

    እንደመሚመርነውም ክርክር ያስነሳውን መሬት አመልካቜ ዚስር ተኚሳሜ ኚነበሩበት  ባለቀታ቞ው ጋር በ1994 ዓ/ም ሲጋቡ ዚባለቀታ቞ው አባት ዚሆኑት ተጠሪ ሰጥተዋ቞ው በጋብቻ ውላቾው ላይም ተጠቅሶ ጋብቻ ኚመሰሚቱበት ኹ1994 ዓ/ም ጀምሮ ጋብቻው በፍቺ እስኚፈሚሰበት 2003 ዓ/ም ድሚስ ተጋቢዎቹ በጋራ ሲጠቀሙበት ዹነበሹ መሆኑ ፍሬ ነገርን ለማጣራት እና ማስሚጃ ለመመዘን በህግ ስልጣን በተሰጣ቞ው ዚስር ፍ/ቀቶቜ ውሳኔ ላይ ተሚጋግጧል፡፡ ክርክር ያስነሳው መሬት ተመዝግቩ ዹሚገኘው እና ግብር ዚሚኚፈልበት በተጠሪው ስም ቢሆንም ይህን መሬት ለአመልካቹ እና ለባለቀታ቞ው ሰጡ ኚተባለበት ኹ1994 ዓ/ም ጀምሮ እስኚ 2003 ዓ/ም ድሚስ ተጠሪ ተጠቅመውበት ዚማያውቁ መሆኑና ሲጠቀሙበት ዚቆዩት አመልካቜ ኚባለቀታ቞ው (ዚስር ተኚሳሜ) ጋር መሆኑ በስር ፍ/ቀቶቜ ተሚጋግጧል፡፡ ማንኛውም አርሶአደር በመሬት ይዞታው ዹመጠቀም መብቱን በዚያ መሬት ገቢ ለሚተዳደሩ ወይም ሌላ ገቢ ለሌላቾው ዚቀተሰብ አባላት ወይም መሬት ለሌላቾው ልጆቹ በስጊታ ማስተላለፍ እንደሚቜል በኊሮሚያ ዹገጠር መሬት አስተዳደርና አጠቃቀም አዋጅ ቁጥር 130/1997 አንቀጜ 9(5) ላይ ተመልክቷል፡፡

     

    በተያዘው ጉዳይ በጜሁፍ ዹተደሹጉ ዚስጊታ ውል ባይኖርም ለክርክር ምክንያት ዹሆነውን መሬት በተጠሪ ስም ተመዝግቩ ያለ መሆኑን ነገር ግን እዚተጠቀሙበት ያሉት አመልካቜ  እና ባለቀታ቞ው መሆኑን ገልጻ ለሜታ ሮቢ ወ/ፍ/ቀት መልስ ዹሰጠ ሲሆን ዹቀበሌው አስተዳደርም ለስር ፍ/ቀት በጻፈው ደብዳቀ ለክርክር ምክንያት በሆነው መሬት አመልካቜ ኚባለቀታ቞ው ጋር ሲጠቀሙበት ዚቆዩ መሆኑን ገልጿል፡፡ ስር ፍ/ቀት ቀርበው ዹተሰሙ ዚአመልካቜ ምስክሮቜም


    መሬቱን ተጠሪ ሰጥተዋ቞ው አመልካቜና ባለቀታ቞ው ሲጠቀሙበት ዚቆዩ መሆኑን አስሚድተዋል፡፡ ተጠሪ ለኹርክር ምክንያት በሆነው መሬት ላይ ዚነበራ቞ውን ዹመጠቀም መብት ልጃቾው ዹሆነው ዚአመልካቜ ባለቀት ኚአመልካቜ ጋር ጋብቻ ሲፈጜሙ በዚህ መሬት እንዲተዳደሩ በአባትነታ቞ው አስልፈው ሰጥተው ኹ1994 ዓ/ም ጀምሮ አመልካቜ ኚባለቀታ቞ው ጋር በፍቺ ውሳኔ እስኚተለያዩበት 2003 ዓ/ም ድሚስ ሲጠቀሙበት ዚቆዩ በመሆኑ በመሬቱ ዚነበራ቞ውን ዚተጠቃሚነት መብት ካስተላለፉ በኋላ መሬቱ ተመዝግቩ ዹሚገኘው እና ግብርም ዹሚኹፈለው በተጠሪው ስም ብቻ በመሆኑ መሬቱ ለተጠሪ ሊመለስላ቞ው ይገባል ማለት ዚሚቻል አይደለም፡፡ ለክርክር ምክንያት ዹሆነውን መሬት እንደቀተሰብ በእኔ ስር ሆነው አመልካቜ ባለቀቷ ተጠቀሙ እንጂ በግላቾው ስር ሆኖ አንድም ቀን አልተጠቀሙበትም በማለት ተጠሪ ለዚህ ቜሎት ባቀሚቡት መልስ ዚተጠቀሱ ቢሆንም ይህን ስር ፍ/ቀት በነበሹው ክርኚራ቞ው አላስሚዳም፡፡ በስር ፍ/ቀቶቜ ውሳኔ ላይ ዹተሹጋገጠው መሬቱን ተጠሪ ለአመልካቜ ኚሰጡ በኃላ ሲጠቀሙበት ዚቆዩት አመልካቜ እና ባለቀታ቞ው መሆናቾውን ነው፡፡ በገጠር መሬት ላይ ዹሚኖሹው መብት ዹመጠቀም መብት ሲሆን ተጠሪ ይህን መብታ቞ውን ለአመልካቜና ባለቀታ቞ው አሳልፈው ሰጥተው ለሹጀም ጊዜ በዚህ መሬት ላይ ተጠቃሚነታ቞ው በተቋሚጠበት ሁኔታ ዚምዕራብ ሾዋ ዞን ኹፍ/ፍ/ቀት እና ዚኊሮሚያ ክልል ጠ/ፍ/ቀት ሰበር ቜሎት በጜሁፍ ዹተደሹገ ስጊታ ውል አለመኖሩን ብቻ መሰሚት በማድሚግ በክርክሩ ኹተሹጋገጠው ፍሬ ነገር ውጪ ዚሰጡት ውሳኔ መሰሚታዊ ዹህግ ስህተት ዚተፈጞመበት ሆነ በመገኘቱ ዹሚኹተለው ውሳኔ ተሰጥቷል፡፡

     

     ው ሳ ኔ

     

    1. ዚኊሮሚያ ክልል ምዕራብ ሾዋ ዞን ኹፍ/ፍ/ቀት በመ/ቁ. 55478 በቀን 3/03/2006 ዓ/ም በዋለ ቜሎት ዹሰጠው ውሳኔ እና ዚኊሮሚያ ጠ/ፍ/ቀት ሰበር ቜሎት በመ/ቁ.186326 በቀን 26/08/2007 ዓ/ም በዋለ ቜሎት ዹሰጠው ውሳኔ በፍ/ብ/ስ/ስ/ህ/ቁ. 348(1) መሰሚት ተሜሯል፡፡

    2. በኊሮሚያ  ክልል   ምዕራብ   ሾዋ  ዞን  ሜታ   ሮቀ   ወ/ፍ/ቀት በመ/ቁ.15357   በቀን

    10/01/2006 ዓ/ም በዋለ ቜሎት ዹሰጠው ውሳኔ እና ዚኊሮሚያ ክልል ጠ/ፍ/ቀት ይግባኝ ሰሚ ቜሎት በመ/ቁ. 170790 በቀን 8/11/2006 ዓ/ም በዋለ ቜሎት ዹሰጠው ውሳኔ በፍ/ብ/ስ/ስ/ቁ.348(1) መሰሚት ጞንቷል፡፡

    3. ለክርክሩ ምክንያት ዹሆነው መሬት ዚአመልካቜ እና ባለቀታ቞ው ዚነበሩተ ዚስር ተኚሳሜ ዚጋራ ይዘት ነው ብለናል፡፡

     

    4. ግራ ቀኙ በዚህ ቜሎት ላደሚጉት ክርክር ያወጡትን ወጪ ዚዚራሳ቞ውን ይቻሉ ብለናል፡፡ መዝገቡ ዕልባት ያገኘ በመሆኑ ወደ መ/ቀት ይመለሰ፡፡ዚማይነበብ ዚአምስት ዳኞቜ ፊርማ አለበት

  • በስራ ክርክር ዚተኚራካሪ ወገኖቜ ማንነት ዚፍርድ ቀቶቜን ስልጣን (ዹክልል ወይም ዚፌዎራል)ብሎ ለመወሰን እንደወሳኝ  መለኪያ ሊወሰድ ዚማይገባ ስለመሆኑፀ

     

    ዚአሰሪው እርምጃ ህገ ወጥነት ዹተሹጋገጠ እንደሆነ  ዚክፍያ መጠኑ ሊሰላ ዚሚገባው አዋጁ ባስቀመጠው ስሌትና በማስሚጃ በተሹጋገጠ ዹደመወዝ መጠን መሆን ያለበት ስለመሆኑ፣

     

    አዋጅቁጥር377/1996አንቀፅ 35(1(ለ))፣39(1(ለ))፣40(1)(2)፣43(4(ሀ)፣68፣71

    ዹሰ/መ/ቁጥር 95638

     

    መስኚሚም 29 ቀን 2007 ዓ/ም

     

    ዳኞቜ፡-አልማው ወሌ ሡልጣን አባተማም መኮንን ገ/ሕይወት ሙስጠፋ አህመድ ተፈሪ ገብሩ

    አመልካቜ፡-ኢስት ሲሜንት አክሲዩን ማህበር - ጠበቃ ዓለሙ ደነቀው - ቀሚቡ ተጠሪ፡-አቶ ዘላለም ታደሰ  - ጠበቃ ገናናው ተሟመ ቀሚቡ

    መዝገቡ ተመርምሮ ተኚታዩ ፍርድ ተሰጥቷል፡፡

     

     ፍ  ር ድ

     

    ጉዳዩ በአዋጅ ቁጥር 377/1996 መሰሚት ዹቀሹበውን ዹግል ዚስራ ክርክርን ዚሚመለኚት ሲሆን ክርክሩ ዚተጀመሚበት ፍርድ ቀት ዚሂደቡ አቩቮ ወሚዳ ፍርድ ቀት ነው፡፡በዚህ ፍርድ ቀት ኚሳሜ ዹአሁኑ ተጠሪ ሁኖ ዚክሱ ይዘትም፡-በተጠሪ ድርጅት በአስተዳደር ኃላፊነት እና ጉዳይ አስፈፃሚነት አምስት አመት ኹዘጠኝ ወር ብር 6,410.90 በወር እዚተኚፈላ቞ው ማገልገላቾውንና ዚስራ ውሉ ኹሕግ ውጪ መቋሚጡን ገልጾው ልዩ ልዩ ክፍያዎቜ እንዲኚፈላ቞ው ይወሰን ዘንድ ዳኝነት መጠዹቃቾውን ዚሚያሳይ ነው፡፡ዚአሁኑ አመልካቜ ተኚሳሜ ዹነበሹ ቢሆንም መጥሪያ ደርሶታል፣ግን አልቀሹበም ተብሎ በሌለበት ጉዳዩእንዲታይ ተደርጓል፡፡ዚሥር ፍርድ ቀትም ጉዳዩን መርምሮ ዹአሁኑ አመልካቜ ለክሱ ኃላፊ ነው ተብሎ ለኚሳሜ ብር 277,294.00 ( ሁለት መቶ ሰባ ሰባት ሺህ ሁለት መቶ ዘጠና አራት) ብር እንዲኚፈል ወሰኗል፡፡

     

    ዹአሁኑ አመልካቜ በሌለሁበት ታይቶ ዹተወሰነው ውሳኔ ተነስቶ ባለሁበት ይታይልኝ በማለት ጥያቄ ያቀሚበ ሲሆን ኹዚሁ ጋር በተጚማሪ ኚሳሹ ዚአሰሪ ወገን ስለሆነ በአሰሪና ሰራተኛ ጉዳይ አዋጅ ሊዳኙ አይገባም፣በአዋጁ መሰሚት ሊዳኝ ይገባል ኚተባለም ዚስራ ውሉ ዹተቋሹጠው በሕጋዊ መንገድ ስለሆነ ሊፈጾም ዚሚገባ ክፍያ ዚለም፣ክፍያ ሊፈፀም ይገባል ኚተባለም ኚሳሜ ደሞዜ ነው ብሎ ያቀሚበው መጠን ትክክል አይደለም፣በትክክል ደመወዙ ላይ ተመስርቶ ሊኹፈል ዚሚገባውም ዹደመወዙን

         ኛውን ያህል ብቻ ነው ብሎ ተኚራክሯል፡፡ዚስር ፍርድ ቀት በአመልካቜ በሌለሁበት ታይቶ

     

    ዹተወሰነው ውሳኔ ይነሳልኝ ጥያቄ ላይ ዹአሁኑ ተጠሪ (ዚስር ኚሳሜ) አስተያዚት እንዲሰጡበት  ያደሚገ

    ሲሆን ተጠሪው በሰጡት አስተያዚትም ለአመልካቜ መጥሪያውን ባቀሚቡት ዹቃለ መሓላ አቀቱታ ዚተዘሚዘሩ ምስክሮቜ ዚሚያሚጋገጡ መሆኑን እና ዚተለያዩ ክፍያዎቜ እንዲኚፈሏ቞ው ዹተወሰነውም በአግባቡ ነው በማለት ተኚራክሚዋል፡፡ዚወሚዳው ፍርድ ቀት ጉዳዩን መርምሮ አመልካቜ ጉዳዩ ባለሁበት ይታይልኝ በማለት ያቀሚበው ጥያቄ ተቀባይነት ዚለውም፣በቃለ መሐላ ተሹጋግጧል በማለት ውሳኔ ሰጠ ፡፡ በዚህ ውሳኔ ዹአሁኑ አመልካቜ ቅር በመሰኘት ይግባኙን ለሰሜን ሾዋ ዞን ኹፍተኛ


    ፍርድ ቀት አቅርቩ ተቀባይነት አላገኘም፡፡ኚዚህም በኋላ አመልካቜ ዹሰበር አቀቱታውን ለክልሉ ሰበር ሰሚ ቜሎት አቅርቩ ቜሎቱ ግራ ቀኙን ኚአኚራኚሚ በኋላ ጉዳዩን መርምሮ መጥሪያው በሕጉ መሰሚት ለአሁኑ አመልካቜ ዹደሹሰው መሆንያለመሆኑን ዚግራ ቀኙን ምስክሮቜእንዲሰሙና ተገቢው እንዲወሰን በማለት ጉዳዩን ለወሚዳው ፍርድ ቀት መልሶታል፡፡ በዚህ አግባብ ጉዳዩ ዚተመለሰለት ዚወሚዳው ፍርድ ቀትም በ18/03/2004 ዓ/ም ዹአሁኑ ተጠሪ ለወሚዳው ፍርድ ቀት ባቀሚቡት ቃለ መሃላ ላይ ያሉትን ምስክሮቜን ኹሰማ በኋላ ዹአሁኑ አመልካቜ ደግሞ ዚቀሚቡት ምስክሮቜ ይበቁናል ስላለ ፍርድ ቀቱ ጉዳዩን መርምሮ መጥሪያው ለአመልካቜ መድሚሱ ተሹጋግጧል በማለት በጉዳዩ ላይ ዹሰጠውን ውሳኔ አይነሳም ሲል በ24/05/2005 ዓ/ም በዋለው ቜሎት ወሰኗል፡፡በዚህ ውሳኔ ላይ ለሰሜን ሾዋ ዞን ኹፍተኛ ፍርድ ቀት ዹአሁኑ አመልካቜ ይግባኙን አቅርቩ ፍርድ ቀቱም ግራ ቀኙን ኚአኚራኚሚ በኋላ ጉዳዩን መርምሮ መሰማት ዚሚገባ቞ው ምስክሮቜ በ18/03/2004 ዓ/ም በተጻፈ ዚተጠሪ ቃለ መሃላ ላይ ያሉት ምስክሮቜ ሳይሆኑ በ26/03/2004 ዓ/ም በተጻፈ ቃለ መሃላ ላይ ያሉት ምስክሮቜ ናቾው በማለት በክልሉ ሰበር ሰሚ ቜሎት መመሪያ መሰሚት ዚወሚዳው ፍርድ ቀት አልፈጾመም ሲል በዚህ ሚገድ ዹተሰጠውን ውሳኔ በ28/06/2005 ዓ/ም በዋለው ቜሎት ሜሮ በ26/03/2004 ዓ/ም በተጻፈ ቃለ መሃላ ላይ ያሉት ምስክሮቜ እንዲሰሙ ሲል ጉዳዩን ለወሚዳው ፍርድ ቀት መልሶ ልኮለታል፡፡.ዹአሁኑ ተጠሪ በዚህ ዹዞኑ ኹፍተኛ ፍርድ ቀት ውሳኔ ቅር በመሰኘት ዹሰበር አቀቱታውን ለክልሉ ሰበር ሰሚ ቜሎት አቅርበው ቜሎቱም ዚግራ ቀኙን ክርክር ኹሰማ በኋላ ቜሎቱ መሰማት ዚሚገባ቞ው በ18/03/2004 ዓ/ም በተፃፈ ቃለ መሃላ ላይ ዚተዘሚዘሩት ምስክሮቜ ናቾው? ወይስ በ26/03/2004 ዓ/ም በተጻፈ ቃለ መሃላ ላይ ዚተገለፁት ምስክሮቜ ናቾው? ዹሚለውን ጭብጥ ይዞ ጉዳዩን በመመርመር ዚወሚዳው ፍርድ ቀት በ12/03/2004 ዓ/ም ዹሰጠው ትዕዛዝ ዚተኚሳሜን መልስ ለመቀበል ብሎ ለ18/03/2004 ዓ/ም መቅጠሩን፣በዚህ ቀን ኚሳሜ ለተኚሳሜ መጥሪያ ማድሚሱን በመግለፅ በቃለ መሃላ ዚተኚሳሜ መልስ ዚመስጠት መብት መታለፉን፣በ26/03/2004 ዓ/ም ደግሞ ኚሳሜ ደመወዝ ሲበላበት ዹነበሹ ፔሮል ለተኚሳሜ ድርጅት እንዲያቀርብ ዚታዘዘ መሆኑን ኚመዝገቡ መሚዳቱን ጠቅሶ መሰማት ያለባ቞ው ምስክሮቜ በ18/03/2004 ዓ/ም በተፃፈው ቃለ መሃላ ያሉት ምስክሮቜ እንጂ በ26/04/2004 ዓ/ም በተጻፈ ቃለ መሃላ ዹተገለፁ ምስክሮቜ አይደሉም በማለት ዹዞኑ ኹፍተኛ ፍርድ ቀት በዚህ ሚገድ በ20/01/2006 ዓ/ም በዋለው ቜሎት ዹተሠጠውን ውሳኔ ሜሮ ዚወሚዳ ፍ/ቀት ውሳኔን አጜንቷል፡፡

     

    ዹአሁኑ ዹሰበር አቀቱታ ዹቀሹበውም በዚሁ ዹክልሉ ሰበር ሰሚ ቜሎት ሲሆን ዚአመልካቜ ዹሠበር አቀቱታ ቅሬታ መሰሚታዊ ነጥቊቜም፡-ዹክልሉ ሰበር ሰሚ ቜሎት ጉዳዩን ለወሚዳው ፍርድ ቀት ዹመለሰው በ26/03/2004 ዓ/ም በተፃፈ ቃለ መሃላ ዚተገለፁትን ምስክሮቜ እንዲሰሙ ሁኖ እያለ መልሶ መሰማት ያለባ቞ው በ18/03/2004 ዓ/ም በተጻፈ ቃለ መሃላ ዚተገለፁትን ምስክሮቜ ናቾው ማለቱ ተገቢነት ዚለውም፣ዚተጠሪው ደመወዝ ተጠሪው እንደገለፀው ብር 6,410.00 ሳይሆን ብር 3,230.70 ብቻ መሆኑ ኹተሹጋገጠ በኋላ ዚስራ ስንብት ክፍያ ብር 47,383.60 እንዲሆን መወሰኑ ያላግባብ ሲሆን ዚስራ ስንብት ክፍያው ብር 8,348.00 ብቻ ነው፣ዚካሳ ክፍያ ብር 19,384.00 መሆን ሲገባው ብር 25,849.60 መሆኑ ያላግባብ ነው፣ዚሳምንት ዚእሚፍት ክፍያ ሊተመን በማይቜል ስሌት ብር 188,784.57 ሁኗል፣ዚአምስት አመት በዓል በማለት ብር 16,357.00 እንዲኚፍል መወሰኑ ያላግባብ ነው፣ዚአመልካቜ እርምጃ ሕገ ወጥ ነው ዚሚባል ኹሆነም ሊኹፈሉ ዚሚገባ቞ው ክፍያዎቜፀ- ዚአገልግሎት ክፍያ ብር 8,384.30፣ዚሁለት ወር ማስጠንቀቂያ ብር 6,461.40፣ዚካሳ ክፍያ ብር 19,384.20 በድምሩ ብር 34,229.90 እንጂ ብር 277,294.00 እንዲኚፈል መወሰኑ ያለአግባብ ነው በማለት በዚህ ቜሎት እንዲወሰን ዹጠዹቀው ዳኝነትም ዚአመልካቜ ዚመኚራኚር መብቱ እንዲጠበቅለት፣ይህ  ዚሚታለፍ  ኹሆነ  በአዋጁ  መሰሚት  ክፍያዎቹ  መወሰን  አለባ቞ው  ዹሚል


    ነው፡፡ዚሠበር አቀቱታው ተመርምሮም በዚህ ቜሎት ጉዳዩ እንዲታይ ዹተደሹገው ኚአመልካቜ ማንነት አንፃር ይህንኑ ጉዳይ ዹክልሉ ሰበር ሰሚ ቜሎት ተቀብሎ ማዚቱ ተገቢ መሆን ያለመሆኑን ለመመርመር ተብሎ ሲሆን ተጠሪ ቀርበው በሰጡት መልስም ጉዳዩ ዚአሰሪና ሰራተኛ ስለሆነ አዋጁ ኚወጣበት ጊዜ አንጻር በክልሉ ሰበር ሰሚ ቜሎት ዚማይታይበት ምክንያት ዚለም፣ጉዳዩ ዚማስሚጃ ምዘና ጉዳይ ስለሆነ በዚህ ቜሎት ዚሚታይ አይደለም፣በሌለበት በታዚ ጉዳይ በስንብቱ እና በደመወዝ መጠኑ ሊኚራኚርአይቜልም፣ተጠሪ ዚአሰሪ ዚአስተዳደር አካል ያለመሆና቞ው በማስሚጃ ተሚጋግጧል፣በቃለ መሃላ ጉዳይ ላይ ማስተባበያ ማስሚጃ አላቀሚበም፣ዚተጠሪ ምስክሮቜ ዚእኔም ምስክሮቜ ናቾው በማለት መግለፁን ዚስር ፍርድ ቀት መዝገብ ያሳያል፣ዚክልሉ ሰበር ሰሚ ቜሎት ራሱ ዹሰጠውን ውሳኔ አልሻሚም፣በ26/03/04 በተጻፈ ቃለ መሃላ ዚተገለጹት ምስክሮቜ ዚሚሰሙበት ምክንያት ዚለም፣በዚህ ቀን ዹቀሹበው ቃለ መሃላ ዚስር ተኚሳሜ ኚሳሜ ዹሚበላውን ደመወዝ መዝገቡን እንዲያቀርብ በ22/03/2004 ዓ/ም በዋለው ቜሎት ፍርድ ቀቱ አዞት ስለነበር ተኚሳሹ ዚፍርድ ቀቱን ትዕዛዝ አልፈፀመም፣ዚፍርድ ቀቱን መጥሪያአልወስድም ማለቱን ለማሚጋጋጥ ነው፣ በማለት ዘርዝሮ ዹክልሉ ሰበር ሰሚ ቜሎት በመ/ቁጥር 163369 በ20/01/2006 ዓ/ም ዹሰጠው ውሳኔ እንዲፀናላ቞ው ዳኝነት መጠዹቃቾውን ዚሚያሳይ ነው፡፡ዚአሁኑ አመልካቜም ያስቀርባል ዚተባለበትን ነጥብ በመደገፍና በሰበር አቀቱታው ላይ ዚተዘሚዘሩትን ነጥቊቜን በማጠናኹር ዚመልስ መልሱን ሰጥቷል፡፡

     

    ኹዚህም በኋላ ይህ ቜሎት ጉዳዩን መርምሮ አመልካቜ መጀመሪያ በሌለበት ታይቶ ዹተሰጠው ውሳኔ እንዲነሳለት ለወሚዳው ፍርድ ቀት አመልክቶ ተቀባይነት ካጣ በኋላ ለዞኑ ኹፍተኛ ፍርድ ቀት ይግባኙን ሲያቀርብ በፍሬ ጉዳዩ ላይ ስርዓቱን ጠብቆ እስኚ ክልሉ ሰበር ሰሚ ቜሎት መኚራኚሩን ለማወቅ ይሚዳ ዘንድ ዚወሚዳው ፍርድ ቀት መጀመሪያ በፍሬ ጉዳዩ ላይ ዹሰጠው ውሳኔ ግልባጭ፣አመልካቜ ለዞኑ ኹፍተኛ ፍርድ ቀት እና ለክልሉ ሰበር ሰሚ ቜሎት ያቀሚበው ዚይግባኝ እና ዹሰበር አቀቱታ ግልባጮቜን እንዲያያይዝ ትዕዛዝ ሰጥቶ አመልካቜአሉኝ ያላ቞ውን ውሳኔዎቜን አያይዟል፡፡

     

    ዚጉዳዩ አመጣጥ አጠር አጠር ባለመልኩ ኹላይ ዹተገለጾው ሲሆን ይህ ቜሎትም ዚግራ ቀኙን ክርክርና ለሰበር አቀቱታው መነሻ ዹሆነውን ውሳኔ አግባብነት ካላ቞ው ድንጋጌዎቜ ጋር በማገናዘብ ጉዳዩን በሚኹተለው መልኩመርምሮታል፡፡እንደመሚመሚውም ዹዚህን ቜሎት ምላሜ ዚሚያስፈልጋ቞ው አበይት ነጥቊቜ፡-

     

    1.  ዹክልሉ ሰበር ሰሚ ቜሎት ጉዳዩን ለማዚት ስልጣን አለው ወይስ ዹለም?

    2.  ዚአመልካቜ ዚመኚራኚር መብት ዚታለፈው በሕጉ አግባብ ነው ወይስ አይደለም?

    3. ዚአመልካቜ እርምጃ ሕገ ወጥ ነው ተብሎ ዚተለያዩ ክፍያዎቜን ለተጠሪ እንዲኚፍል በተሰጠው ውሳኔ መሰሚታዊ ዹሆነ ዹሕግ ስህተት አለ ለማለት ይቻላል ወይስ አይቻልም?

     ዹ መጀ መሪያ ውን ጭ ብጥበተመለኚተ፡-በመሰሚቱ ዚኢትዮጵያ ፌዎራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ በፌዎራል መንግስትና በክልሎቜ መዋቀሩን መሰሚት በማድሚግ ዚዳኝነቱም ሥልጣን በፌዎራል መንግስቱ እና በክልል መንግስታት መካኚል እንደተኚፋፈለ በህገ መንግስቱ አንቀጜ 5ዐ እና 51 ሥር ተመለክቷል፡፡በኢ.ፌ.ዲ.ሪሕገ መንግስት በአንቀጜ 8ዐ “ዹፍ/ቀቶቜ ጣምራነትና ሥልጣን” በሚል ርዕስ በፌዎራል ጉዳዩቜ ላይ ዹበላይና ዚመጚሚሻዚዳኝነት ሥልጣኑ በፌዎራል ጠቅላይ ፍ/ቀትፀበክልል ጉዳዮቜ ላይ በክልሉ መንግስት ጠቅላይ ፍ/ቀት ሥልጣኑ ዹተደነገገ ሲሆን ዹክልል ፍ/ቀቶቜ በህገ- መንግስቱ በተሰጣ቞ው ዹውክልና ሥልጣን መሠሚት ካልሆነ በቀር ዚፌዎራልን ጉዳይ ለማዚትፀእንዲሁም ዚፌዎራል ፍ/ቀቶቜ ዹክልልን ጉዳይ ለማስተናገድ ዚሚያስቜል  ሥልጣን ዹሌላቾው  መሆኑን  በዚሁ  ድንጋጌ  ስር  ዚተቀመጡት  ንዑስ  ድንጋጌዎቜ  ይዘትና    መንፈስ


    ያሳያል፡፡አንድ ጉዳይ ዚፌዎራል ነው? ወይስ ዹክልል? ዹሚለውን ለመለዚትም መሰሚቱ ዹአዋጅ ቁጥር 25/88 ሲሆንፀበዚሁ ህግ አንቀጜ 5 ሥር በተመለኚቱት ጉዳዮቜ ላይ ብ቞ኛ ሥልጣን ያላ቞ው ዚፌዎራል ፍ/ቀቶቜ ና቞ው፡፡ በእነዚህ ጉዳዮቜ ላይ ዹክልል ፍ/ቀቶቜስልጣን ዚሚኖራ቞ው በህገመንግስቱ በተሰጣ቞ው ዹውክልና ሥልጣን አግባብ ብቻ ነው፡፡ይህ በግልፅ ዚሚያሳዚው በአዋጅ ቁጥር 25/1988 አንቀጜ 5 መሰሚት ዚፍርድ ቀቶቜ ስልጣን በጉዳዩ ባለቀትነት (Subject matter) ዚሥልጣን ክፍፍል እንደተጠበቀ ሆኖ ክሱም መቅሚብ ያለበት ጉዳዩን አይቶ ለመወሰን ዚሥሚ-ነገር ሥልጣን ላለው ፍ/ቀት ስለመሆኑ ነው፡፡ዚፌደራል ፍ/ቀቶቜን ለማቋቋም በወጣው አዋጅ ቁጥር 25/88 አንቀጜ 8፣11፣14 እና 15 ድንጋጌዎቜ ይዘትና መንፈስ ደግሞ አንዳንድ ጉዳዮቜ ሊያስነሱ በሚቜሉት ዹክርክር ባህርይ ምክንያት ለተወሰኑ ፍ/ቀቶቜ እንዲቀርቡ በህግ ተለይተው ኚተመለኚቱት በቀር ዚሥሚ-ነገር ሥልጣን ዹተደለደለው በክሱ በተመለኹተው ዚገንዘብ ወይም ዚንብሚት ግምት መነሻ እንደሆነ ኹፍ/ብ/ሥ/ሥ/ህ/ቁ 14 እና 15 ስር ኚተመለኚቱት ድንጋጌቜ ጣምራ ንባብ እና ዹክልል መንግስታት ፍርድ ቀቶቜ ማቋቋሚያ ሕጎቜ ያስሚዳሉ፡፡ይህ በእንዲህ እንዳለ ግን አዋጅ ቁጥር 25/1988"ን" ያወጣው ዚፌዎራል መንግስት ዚሕዝብ ተወካዮቜ ምክር ቀት ዚስራ ክርክሮቜ ዚሚመሩበትን ስርኣት ዹዘሹጋውን አዋጅ ቁጥር 377/1996 ኚዚካቲት 18 ቀን 1996 ዓ/ም ስራ ላይ ያዋለ ሲሆን በዚህ አዋጅ ዚስራ ክርክር ስልጣን ድልድል ዹተደሹገው ዹግል ዚስራ ክርክርና ዹወል ዚስራ ክርክር ዚሚሉትን ጉዳዮቜን መሰሚት በማድሚግ ሲሆን ዚተኚራካሪ ወገንን ማንነትን ግንዛቀ ውስጥ ባስገባ መልኩ አይደለም፡፡በመሆኑም ክርክሮቹ ክልል ዚተነሱ ቢሆንም ጉዳዩን ዹክልል ዚመጀመሪያ ደሹጃ ፍርድ ቀት ወይም አግባብነት ያላ቞ው ዹቋሚ ወይም ጊዜአዊ ቊርዶቜ ሊመለኚቱ እንደሚቜሉ አድርጎ ሕጉን ሕግ አውጪው አውጥቷል፡፡ይህ አዋጅ ኹአዋጅ ቁጥር 25/1988 በኋላ ኚመውጣቱም በላይ ለስራ ክርክሮቜ ልዩ ሕግ ነው፡፡እንዲህ ኹሆነ አዋጅ ቁጥር 377/1996 ለስራ ክርክሮቜ ኹሕገ መንግስቱ በመለስ ባሉት ማናቾውም ሕጎቜ ዹበላይ ተፈፃሚነት ያለው ስለመሆኑ ተቀባይነት ያላ቞ው ዹሕግ አተሹጓጎም ደንቊቜ ዚሚያስሚዱን ጉዳይ ነው፡፡በመሆኑም በስራ ክርክር ተኚራካሪ ወገኖቜ ማንነት ዚፍርድ ቀቶቜን ስልጣን (ዹክልል ወይም ዚፌዎራል) ብሎ ለመወሰን እንደወሳኝ መለኪያ ሊወሰድ ዚሚገባው አይደለም፡፡ኚዚህ አንጻር ሲታይ ደግሞ ዚኊሮሚያ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቀት ሰበር ሰሚ ቜሎት ጉዳዩን ተቀብሎ ማዚቱ ኹላይ ዹተመለኹተውን ዹህጉን ማዕቀፍ እና በዚህ ሚገድ ይህ ቜሎት በመ/ቁጥር 95298 እና በሌሎቜ በርካታ መዛግብት በአዋጅ ቁጥር 454/1997 አንቀጜ 2(1) መሰሚት በአኚራካሪው ዹህግ ነጥብ ላይ ኹሰጠው አስገዳጅ ዹሕግ ትርጉም ጋር ዚተጣጣመ ነው ኚሚባል በስተቀር ዚሚነቀፍበትን አግባብ አላገኘንም፡፡

     

     ሁ ለተ ኛ ውን ጭብጥ በተ መለ ኚተ፡- በመሰሚቱ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር94 ስር እንደተመለኚተው መጥሪያ በቅድሚያ መድሚስ ያለበት ለተኹሰሰው ሰው ሲሆን ዹተኹሰሰው ሰው ዚንግድ ድርጅት ኹሆነ ደግሞ ኚድርጅቱ ጾሃፊ ወይም ለድርጅቱ ኃላፊ መሰጠት ያለበት መሆኑ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 97(1) ስር ተመልክቷል፡፡ሕጉ መጥሪያ አሰጣጥ ዘዮና ቅደም ተኹተሉ እንዲሁም መጥሪያው ለማን እንደሚሰጥ ዹሚመለኹተው ዚፍትሐ ብሔር ሥነ ሥርዓት ሕግ ክፍል ዓይነተኛ ዓላማ ኚሆኑት መካኚል አንዱ ተካራካሪ ወገኖቜን እኩል ዚመኚራኚር መብት እንዲኖራ቞ው በማድሚግ ጉዳዩን ፍትሐዊ በሆነ አኳኋን ለመወሰንማስቻል መሆኑን ይታወቃል፡፡በመሆኑም ፍርድ ቀቱ መጥሪያ ዚሚደርስበትን ተገቢ መንገድና ለማን መድሚስ እንዳለበት ማሚጋገጥ ይገባዋል፡፡

     

    መጥሪያ በተገቢው መንገድ ደርሶት ተኚራካሪ ወገን ካልቀሚበ ወይም መጥሪያን አልቀበልም ካለ ፍርድ ቀቱ ሊኹተለው ዚሚገባው ስርዓትም በሕጉ በግልጜ ተመልክቷል፡፡ ኚእነዚህም ድንጋጌዎቜ መካኚል በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 70(ሀ)፣103፣104፣105፣ 106 እና 107 ስር ዹተመለኹተው ሊጠቀሱ


    ዚሚቜሉ ሲሆን በእነዚህ ድንጋጌዎቜ መሰሚት ተኚሳሜ በሌለበት ክርክሩ ታይቶ ውሳኔ ሊሰጥ ዚሚቜለው መጥሪያው በአግባቡ ዹደሹሰው መሆኑ ሲሚጋገጥ ወይም መጥሪያውን ለመቀበል ፈቃደኛ አለመሆኑ ወይም ሊገኝ ያልቻለ መሆኑ ሲሚጋገጥ ስለመሆኑ ተመልክቷል፡፡ ድንጋጌዎቹ መጥሪያው በትክክል ያልደሚሰው መሆኑ ኹተሹጋገጠ ጉዳዩ ተኚሳሜ በሌለበት እንዲታይ ዚማይታዘዝ ስለመሆኑ ያስገነዝባሉ፡፡በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 70(ሀ) ድንጋጌ ስር ላይ "መጥሪያው በትክክል  መድሚሱ"ዹሚለው ሐሹግ መኖሩም ዚሚያሳዚው ስለመጥሪያ አሰጣጥና አደራሚስ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 94 እስኚ 110 ድሚስ ዚተመለኚቱት ሁኔታዎቜ በአግባቡ መሟላታ቞ውን ዚሚያስገነዝብ ነው፡፡አንድ ተኚሳሜ በሌለበት ጉዳዩ ታይቶ ውሳኔ ኹተሰጠውም በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 78 መሰሚት መፍትሔ መጠዹቅ ዚሚቜል ስለመሆኑ ተመልክቷል፡፡በዚህ ድንጋጌ መሰሚት መፍትሔ ሊጠዹቅ ዚሚቜለው አቀቱታ አቅራቢው በሚያቀርበው አቀቱታ ላይ ዚጥሪው ትዕዛዝ "በሚገባ ያልደሚሰው" መሆኑን በመጥቀስ ይህንኑ ማሚጋገጥ ሲቜል ነው፡፡ኚእነዚህ ሁሉ ድንጋጌዎቜ መገንዘብ ዚሚቻለው አንድ ሰው ዚመኚራኚር መብቱን እንደተወው ዹሚቆጠሹው መጥሪያው በሕጉ በተዘሹጋው ሥርዓትና ቅደም ተኹተል መሰሚት ደርሶት ክርክር ያለው መሆኑን እያወቀሳይቀርብ ሲቀር ብቻ መሆኑን ነው፡፡ፍርድ ቀቱ በሕጉ ዹተዘሹጋውን ስርዓት ተኚትሎ አማራጭ ዚመጥሪያ አደራሚስ ሥርዓት  ኹፈጾመ መጥሪያው ለተኚሳሹ እንደደሚሰ እንደሚቆጠርና በቂና ሕጋዊ ምንክያት ካለው ብቻወደ ክርክሩ እንዲገባ ዚሚፈቀድ መሆኑን ኹላይ ዚተጠቀሱት ድንጋጌዎቜ ይዘትና መንፈስ ያስገነዝባል፡፡ስለሆነም ማንኛውም ውሳኔ መሰጠት ያለበትም በሕጉ በተዘሹጋው ሥርዓት መሰሚት መጥሪያው መድሚሱ በሚገባ ዹተሹጋገጠና ዚተኚሳሜ ዚመኚራኚር መብት ዹተጠበቀ መሆኑ ሲታወቅ ሊሆን ይገባል፡፡

     

    ወደ ተያዘው ጉዳይ ስንመለስም በወሚዳው ፍርድ ቀት በነበሹው ክስ ተጠሪ ለአመልካቜ ድርጅት መጥሪያውን እንዲያደርሱ ዹተደሹገ ሲሆን ተጠሪ መጥሪያውን ይዘው "ለድርጅቱ ኃላፊ ልሰጥ ስል ኃላፊው አልቀበልም ብለውኛል" በማለት በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 103 መሰሚት በቃለ መሃላ አሹጋግጠው መጥሪያውን ዚመለሱ ሲሆን ለዚህም ምስክሮቜ ያላ቞ው መሆኑን ጭምር ዘርዝሹው አቅርበዋል፡፡ተጠሪ ለስር ፍርድ ቀት በ18/03/2004 ዓ/ም እና በ26/03/2004 ዓ/ም ዚተጻፉ  ሁለት ቃላ መሃላዎቜን ያቀሚቡ ሲሆን አሁን በዚህ ሚገድ ግራ ቀኙን እያኚራኚሚ ያለው በዚትኛው ቀን ዚተዘሚዘሩት ምስክሮቜ ናቾው ስለመጥሪያው አደራሚስ ሊመሰክሩ ዚሚገባ቞ው? ዹሚል ነጥብ ነው፡፡ኚላይ እንደተገለጞው ዚተጠሪ ዚመጥሪያ አደራሚስ በቃለ መሃላ ተደግፎ ዹቀሹበ ቢሆንም መጥሪያውን ለአመልካቜ ድርጅት ያደሚሱ መሆን ያለመሆኑን በተመለኹተ ምስክሮቜ እንዲሰሙ በማለት በክልሉ ሰበር ሰሚ ቜሎት በመ/ቁጥር 148159 ጥቅምት 26 ቀን 2005 ዓ/ም ተወስኖ ጉዳዩ ዚተመለሰለት ዚወሚዳው ፍርድ ቀትም በ18/03/2006 ዓ/ም በተፃፈው ቃለ መሃላ ዚተጠቀሱትን ምስክሮቜ ዹሠማና ምስክሮቹ መጥሪያውን ተጠሪ ለአመልካቜ ድርጅት ማድሚሳ቞ውንና ዚአመልካቜ ድርጅት ኃላፊ አልቀበልም ማለታ቞ውን ማሚጋገጣ቞ውን ምክንያት አድርጎ ዚአመልካቜን በሌለሁበት ታይቶ ዹተወሰነ ውሳኔ ይነሳልኝ ጥያቄን ሳይቀበለው ዹቀሹ ሲሆን ይኌው ዚወሚዳው ፍርድ ቀት ውሳኔ በክልሉ ዹሰበር ሰሚ ቜሎትም ተቀባይነት አግኝቷል። እንግዲህ በክልሉ ሰበር ሰሚ ቜሎት በመ/ቁጥር 148159 በ26/02/2005 ዓ/ም በተሰጠው ውሳኔ ስለመጥሪያው አደራሚስ ዚግራ ቀኙምስክሮቜ እንዲሰሙ ተብሎ ለወሚዳው ፍርድ ቀት ኚመመለሱ ውጪ በ26/03/2004 ዓ/ም በተጠሪ ለወሚዳው ፍርድ ቀት በቀሹበው ቃለ መሃላ ዚተጠቀሱት ምስክሮቜ እንዲሰሙ በግልጜ ዹተሰጠ ውሳኔ ዚለም፡፡በ26/03/2004 ዓ/ም ቀሹበ በተባለው ቃለ መሃላ ያሉት ምስክሮቜም አመልካቜ ዚተጠሪን ደመወዝ መጠን ለማወቅ ይቻል ዘንድ መዝገቡን እንዲያቀርብ ዚወሚዳው ፍርድ ቀት በ22/03/2004 ዓ/ም በዋለው ቜሎት ትዕዛዝ ሰጥቶ ስለነበር አመልካቜ ዚፍርድ ቀቱን ትዕዛዝ አልፈፀምም፣ዚፍርድ ቀቱን መጥሪያአልወሰድም ማለቱን ለማሚጋጋጥ ዚቀሚቡ ስለመሆኑ ዚክርክሩ ሂደት ዚሚያሳይ   ሁኖ


    አግኝተናል፡፡እንዲህ ኹሆነ በ26/03/2004 ዓ/ም በቀሹበው ቃለ መሃላ ዚተጠቀሱት ዚተጠሪ ምስክሮቜ ስለመጥሪያ አደራሚስ ዚሚሰሙበት ዹሕግ አግባብ ዚለም፡፡አንድ ማስሚጃ መሰማት ዚሚገባው ለጉዳዩ አግባብነት ሲኖሚው ስለመሆኑ ተቀባይነት ያላ቞ው ዚማስሚጃ ሕግ ደንቊቜ ዚሚሳዩት ጉዳይ ነው፡፡ ስለሆነምአመልካቜ በዚህ ሚገድ ዚሚያቀርበው ክርክር ተቀባይነት ዹሚሰጠው ሁኖ አልተገኘም፡፡በ18/03/2004 ዓ/ም በተጻፈ ዚተጠሪ ቃለ መሃላ ዚተጠቀሱት ምስክሮቜ መሰማታ቞ው ተገቢ ነው ኚተባለ እነዚህ ምስክሮቜ አመልካቜ መጥሪያ ደርሶት አልቀበልምበማለት ተጠሪን ዚመለሳ቞ው መሆኑን ያሚጋገጡት ዚፍሬ ነገር ጉዳይ በመሆኑ ዚተጠሪ ዚመኚራኚር መብቱ መታለፉ ኹፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 97(1)፣103፣70(ሀ) እና 78 ድንጋጌዎቜ ይዘትና መንፈስ ተገቢ እንጂ ዚሚነቀፍበት አግባብ ዚለም፡፡

     

     ሊ ስተ ኛውን ጭብጥ በተመ ለኚተ፡ -አመልካቜ ተጠሪን ያሰናበተበትን ሕጋዊ ምክንያት በዋናው ክርክር ያለበቂ ምክንያት ባለመቅሚቡ አላስሚዳም፡፡ይልቁንም ተጠሪ አመልካቜ ኹህግ ውጪ ያሰናበታ቞ው መሆኑን በወሚዳው ፍርድ ቀት ባቀሚቡት ማስሚጃ ያሚጋገጡት ጉዳይ መሆኑን ዚክርክሩ ሂደት ያሳያል፡፡በመሆኑም ዚአመልካቜ እርምጃ ሕገ ወጥ ነው ተብሎ ዹተሰጠው ውሳኔ በዚህ ቜሎት ዚሚለወጥበት አግባብ ዚለም፡፡በመሰሚቱ አንድ ተኚሳሜ በሌለበት ታይቶ በተሰጠው በዋናው ጉዳይ ላይ ለበላይ ፍ/ቀት ይግባኝ ሲያቀርብ ዚይግባኝ አቀራሚብ አድማሱ በተወሰኑት ነጥቊቜ ላይ ብቻ መሆን እንዳለበት ዚይግባኝ አቀራሚብን በተመለኹተ ዚተደነገጉት ድንጋጌዎቜ መንፈስ እንደሚያስሚዳና ጉዳዩ በሌለበት ታይቶ ዚተወሰነበት ተኚሣሜ ለበላይ ፍ/ቀት ይግባኝ ሲያቀርብ በስር ፍ/ቀት በተኚራካሪነት ቀርቩ ያላነሣውን ነጥብ ማንሳት እንደማይቜል፣እንደዚህ ዓይነት ተኚራካሪ በፍ/ቀቱ ዚውሣኔ አሰጣጥ ሂደት ውስጥ ክሱን፣ዚማስሚጃዎቜን አግባብነት ተቀባይነት እና ጥንካሬ ባግባቡ ያላገናዘበ ሁኔታ አለ ዹሚል ኹሆነ ይግባኝ ሊያቀርብ እንደሚቜል ይህ ሰበር ሰሚ ቜሎት በመ/ቁጥር 36412  በአዋጅ ቁጥር 454/1997 አንቀጜ 2(1) በዚትኛውም እርኚን ዹሚገኝ ፍርድ ቀትን ዚሚያስገድድ ዹሕግ ትርጉም ዚሰጠበት ጉዳይ ነው፡፡ስለሆነም ፍ/ቀት ኚሣሹ ያቀሚበው ክስ አባሪ ሆነው ኚቀሚቡት ማስሚጃዎቜ አግባብነት፣ተቀባይነትና ጥንካሬ አኳያ በመመርመር ተገቢውን ዳኝነት አልሰጠም በሚል ይግባኝ ዚማቅሚብና ወደ ቀጣዩ ዹሰበር ደሹጃም ቅሬታውን ማድሚስ ጉዳዩ በሌለበት ታይቶ ውሳኔ ለተሰጠበት ወገን በሕግ ዚተጠበቀለት መብት መሆኑ አስገዳጅ ዹሕግ ትርጉም ዚተሰጠበት ጉዳይ ነው፡፡

     

    ወደ ተያዘው ጉዳይ ስንመለስም ዚወሚዳው ፍርድ ቀት በ29/03/2004 ዓ/ም በዋለው ቜሎት ስንብቱ ህገ ወጥ ነው ብሎ ሲወሰን በዚህ ውሳኔ ተጠሪ ዹሚኹፈለኝ ገንዘብ በግልጜ አልተቀመጠልኝም በማለት ለዞኑ ኹፍተኛ ፍርድ ቀት ይግባኝ አቅርበው ዹዞኑ ኹፍተኛ ፍርድ ቀትም ጉዳዩን አይቶ ለስር ዚተጠሪ ደመወዝ ተጣርቶ ሊታወቅ ይገባል፣ኚዚህ በኋላ ዚማስጠንቀቂያ፣ዚስራ ስንብት ክፍያ እና ካሳ፣ዚሳምንት፣ዚአመት እና ዹበዓል ቀናት ክፍያዎቜ እንዲሁም ያልተኚፈለው ደመወዝ ታስቊ በግልጜ መቀመጥ አለበት በማለት በመ/ቁጥር 33824 በ17/05/2004 ዓ/ም በዋለው ቜሎት ለወሚዳው ፍርድ ቀት መልሶለት ዚወሚዳው ፍርድ ቀትም ተኚሳሜ ግብር ሲኚፍልበት ዚቆዚበት ቊታ በደገም ወሚዳ ገቢዎቜ ጜ/ቀት እና በተኚሳሜ ድርጅት እንዲቀርብ አዝዞ ደመወዝንና ዚትርፍ ሰዓት ክፍያ በጠቅላላው ብር 6410.92 መሆኑ በድጋሚ እንደቀሚበለት ጠቅሶ እንዲሁም ኹደገም ወሚዳ ገቢዎቜ ጜ/ቀት ኚሳሜ ደመወዝ ሲበላበት ዹነበሹው እና ወሩ ያልታወቀ ፔሮል ቀርቩ በሁለቱም ወገኖቜ ስምምነት መደሚሱን ገልፆ ውሳኔውን ወደ ገንዘብ ለውጩ ማስቀመጥ ዹአፈፀጾም ክስ ቡድን እንጂ ዚፍርድ ቀት ተግባር አይደለም፣ግን ዚይግባኝ ሰሚውን ፍርድ ቀት ትዕዛዝ መኹተል ተገቢ ነው ብሎ ተጠሪ በሰዓት ዚሚያገኘው ደመወዝ ብር 13.46.00፣በቀን ደግሞ 107.69 መሆኑን ማሚጋገጡን ጠቅሶ ዹወር


    ደመወዙን ብር 3230.70 ይዞ ክፍያዎቜን አስልቶ በጠቅላላው ብር 277,294.04 እንዲኚፈለው ሲል በመ/ቁጥር 03756 ዚካቲት 12 ቀን 2004 ዓ/ም በዋለው ቜሎት ወስኗል፡፡አመልካቜ በሌለበት ጉዳዩ በመታዚቱ ላይ ዚይግባኝ ቅሬታና ዹሰበር አቀቱታ ለክልል ፍርድ ቀቶቜ ሲያቀርብ ለተጠሪ እንዲኚፈሉ በተወሰኑ ክፍያዎቜ መጠን ላይም በሕግ አግባብ ያልተሰሉ መሆኑን ጭምር በመጥቀስ ቅሬታ ሲያቀርብ ዹነበሹ መሆኑን ዹክርክር ሂደት ዚሚያሳይ ሲሆን ተጠሪ በዚህ ሚገድ ዚሚያቀርቡት ክርክር አመልካቜ በሌለበት በታዚው ውሳኔ ላይ ይግባኝና ዹሰበር ክርክር ማቅሚብ አይቜልም ዹሚል መሆኑን ተሚድተናል፡፡ይሁን እንጂ ኹላይ እንደተገለጞው አመልካቜ በሌለበት ጉዳዩ ቢታይም ተጠሪ ያቀሚቡት ክስ አባሪ ሆነው ኚቀሚቡት ማስሚጃዎቜ አግባብነት፣ተቀባይነትና ጥንካሬ ያለመመርመሩንና እንዲሁም አዋጅ ቁጥር 377/1996 ኚአስቀመጠው ዚክፍያ ስሌት ውጪ መሆኑን በሚያሳዩት ነጥቊቜ ላይ በዚህ ቜሎት ክርክር ኚማቅሚብ ዚሚያግደው ዚሥነ ስርዓት ህግ ዹሌለ በመሆኑ በዚህ ሚገድ ተጠሪ ያቀሚቡትን ክርክር ዹምንቀበለው ሁኖ አልተገኘም፡፡

     

    አመልካቜ ኚተጠሪ ጋር ያለውን ዚሥራ ውል በአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ ቁጥር 377/1996 አግባብ ያለማስጠንቀቂያ ኚሥራ ለማሰናበት ዚሚያስቜል ሁኔታ ሣያጋጥመው ካቋሚጠ በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀፅ 39(1/ለ) መሠሚት በአንቀፅ 40 ንዑስ አንቀፅ 2፣ በአንቀፅ 44 እና በአንቀፅ 43 ንዑስ አንቀፅ 4(ለ) ዚተደነገጉትን ክፍያዎቜ ለተጠሪ ዹመክፈል ኃላፊነት አለበት፡፡ኚዚህ አንጻር ዚስር ፍርድ ቀት አመልካቜ ለተጠሪ እንዲኚፍል በማለት ዚዘሚዘራ቞ው ዚክፍያ አይነቶቜ  ዚማስጠንቀቂያ ጊዜ ክፍያ፣ካሳ፣ዚስራ ስንብት ክፍያ፣ዚሳምንት እሚፍት ክፍያ፣ዚአምስት አመት በዓላት ክፍያ ና቞ው፡፡ዚማስጠንቀቂያ ጊዜ ክፍያ፣ዚስራ ስንብት ክፍያና ዚካሳ ክፍያዎቜ ዚሚሰሉበት አግባብ በሕጉ ተለይቶ ዹተቀመጠ ሲሆን ይህንኑ በሕጉ ዹተቀመጠውን ስሌት ተግባራዊ ለማድሚግ ሰራተኛው በወር ሲኚፈለው ዹነበሹው ደመወዝ በሕጋዊ ማስሚጃ መሚጋግጥ ዚግድ ይላል፡፡ኚዚህ አንፃር ጉዳዩን ስንመለኚተው ዚወሚዳው ፍርድ ቀት ዚተጠሪ ዹወር ደመወዝ ብር 3230.70(ሶስት ሺህ ሁለት መቶ ሰላሳ ብር ኚሰባ ሳንቲም) መሆኑን በመ/ቁጥር 03756 ዚካቲት 12 ቀን 2004 ዓ/ም በዋለው ቜሎት በሰጠው ውሳኔ አሚጋግጧል፡፡በመሆኑም ዚተጠሪ ዚማስጠንቀቂያ ጊዜ ክፍያ፣ዚስራ ስንብትና ዚካሳ ክፍያዎቜ መሰላት ያለባ቞ው በዚሁ ዚተጠሪ ወርሃዊ ደመወዝ ዚተባለው መጠን መሰሚት ተደርጎ በሕጉ ዹተቀመጠው ስሌት ባገናዘበ መልኩ ሊሆን ይገባል፡፡

     

    ይህንኑ መሰሚት አድርገን እያንዳንዱን ዚክፍያ መጠን ስንመለኚትም ተጠሪ በአመልካቜ ድርጅት ያላ቞ው ዚአገልግሎት ዘመን አምስት አመት ኹዘጠኝ ወርበመሆኑ በአዋጅ ቁጥር 377/1996 አንቀጜ 35(1)(ለ)) መሰሚት ሊኹፈላቾው ዚሚገባው ዚማስጠንቀቂያ ጊዜ ክፍያ ዚሁለት ወር ደመወዝ ብር

    6,461.40 (ስድስት ሺህ አራት መቶ ስልሳ አንድ ብር ኚአርባ ሳንቲም) ሁኖ አግኝተናል፡፡ዚስራ ስንብት ክፍያን በተመለኹተም በአዋጁ አንቀጜ 39(1(ለ)) እና 40(1)(2) ድንጋጌዎቜ መሰሚት ዚሚመጣው ውጀት ብር 8,384.30 (ስምንት ሺህ ሶስት መቶ ሰማንያ አራት ኚሰላሳ ሳንቲም) እንጂ ብር 47,383.60 ያለመሆኑን ተሚድተናል፡፡እንዲሁም ዚካሳ መጠኑ በአዋጁ አንቀጜ 43(4(ሀ)) መሰሚት ሲሰላ ዚወሚዳ ፍርድ ቀት ዚተጠሪን አማካይ ዹቀን ደመወዝ ብር 107.69 ያደሚገው በመሆኑ ይኌው ዹቀን አማካይ ደመወዝ በመቶ ሰማንያ ሲባዛ ዚሚመጣው ውጀት ብር 19,384.20(አስራ ዘጠኝ ሺህ ሶስትመቶ ሰማንያ አራት ብር ኚሃያ ሳንቲም) እንጂ ብር  25,849.60 ያለመሆኑን ተገንዝበናል፡፡ሌላው ዚስር ፍርድ ቀት በአዋጁ አንቀጜ 71 እና 68 መሰሚት ዚሳምንት እሚፍት ክፍያ በማለት ያስቀመጠው ብር 188,784.57(አንድ መቶ ሰማንያ ስምንት ሺህ ሰባት መቶ ሰማንያ አራት ብር ኚሃምሳ ሳንቲም) ዚስሌቱ መነሻ እና ዚመብቱ አድማስ ለጉዳዩ አግባብነትና ጥንካሬ ያላ቞ውን ማስሚጃዎቜን መሰሚት ያደሚገ ስለመሆኑ ዚክርክሩ ሂደት አያሳይም፡፡በመሆኑም በዚህ ሚገድ ዹተሰጠው


    ዚውሳኔ ክፍል ሕግና ማስሚጃን መሰሚት ያደሚገ ሁኖ አላገኘነውም፡፡ዚአምስት አመት በዓል ክፍያን በተመለኹተ ግን አመልካቜ በስር ፍርድ ቀት በሌለበት ዚታዚ በመሆኑና ዹይርጋ ክርክር ተነስቷል ለማለት ስለማይቻል እንዲሁም ፍርድ ቀቱ ደግሞ ይርጋውን በራሱ ሊያነሳ ዚሚቜልበት አግባብ ዹሌለ በመሆኑ ዚገንዘቡ መጠን ብር 16,357.00(አስራ ስድስት ሾህ ሶስት መቶ ሃምሳ ሰባት ብር) ተብሎ በስር ፍርድ ቀት መቀመጡን ዚማንቀበልበትን አግባብ አላገኘንም፡፡ በአጠቃላይ በጉዳዩ ላይ ዹተሰጠው ውሳኔ በኹፊል መሰሚታዊ ዹሆነ ዹሕግ ስህተት ያለበት ነው በማለት ተኚታዩን ወስነናል፡፡

     

     ው ሳ ኔ

     

    1.  በኊሮሚያ ብሔራዊ  ክልላዊ  መንግስት ጠቅላይ  ፍርድ  ቀት  ሰበር  ሰሚ  ቜሎት በመ/ቁጥር

    163369 በ20/01/2006 ዓ/ም ዹተሰጠው ውሳኔ ተሻሜሏል፡፡

    2. በሂደቡ አቩቮ ወሚዳ በመ/ቁጥር 03756 ዚካቲት 12 ቀን 2004 ዓ/ም በዋለው ቜሎት ዚአመልካቜ ዚስንብት እርምጃ ሕገ ወጥ ነው ተብሎ ዹተሰጠው ዚውሳኔ ክፍል ዹፀና ሲሆን ውጀቱን በተመለኹተ ዹሰጠው ዚውሳኔ ክፍል ግን በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 348(1) መሰሚት ተሻሜሏል፡፡

    3. ዹክልሉ ሰበር ሰሚ ቜሎት ጉዳዩን ዚማዚት ስልጣን አለው፣ዚአመልካቜ ዚመኚራኚር መብት ዚታለፈው ባግባቡ ነው፣ዚአመልካቜ እርምጃ ህገ ወጥ ነው በማለት መወሰኑም ተገቢ ነው በማለት ውጀቱን ግን አመልካቜ ለተጠሪ ሊኹፍል ዚሚገባው በአዋጅ ቁጥር 377/1996 በተቀመጠው ስሌትና በማስሚጃ በተሹጋገጠው ዹደመወዝ መጠን በመሆኑ፡-

    3.1  ዚስራ ስንብት ክፍያ ብር 8,384.30፣

    3.2  ዚሁለት ወር ማስጠንቀቂያ ጊዜ ክፍያ ብር 6,461.40፣

    3.3  ዚካሳ ክፍያ ብር 19,384.20 እና

    3.4 ዚአምስት አመት   ዹበዓል   ቀናት   ክፍያ  ብር   16,357.00  ሁኖ በድምሩ   ብር

    50,586.90(ሃምሳ ሺህ አምስት መቶ ሰማንያ ስድስት ብር ኹዘጠና ሳንቲም) ነው በማለት ወስነናል፡፡

    4. ዚሳምንት ዕሚፍት ቀናት ክፍያ ብር 188,784.57 በተመለኹተ ግን በሕግ እና በማስሚጃ ያልተደገፈ በመሆኑ  አመልካቜ ለተጠሪ ሊኹፍል አይገባም በማለት ወስነናል፡፡

    5. በዚህ ቜሎት ለተደሹገው ክርክር ዚወጣውን ወጪና ኪሳራ ዚዚራሳ቞ውን ይቻሉ ብለናል፡፡ መዝገቡ ተዘግቷልፀወደ መዝገብ ቀት ይመለስ ብለናል፡፡

    ዚማይነበብ ዚአምስት ዳኞቜ ፊርማ አለበት፡፡

     

     

    ት/ጌ

     

  • ጋብቻ በሁኔታ ፈርሷል ሊባልባ቞ው ስለሚቜሉባ቞ው ሁኔታዎቜ ጋብቻ በሁኔታ ፈርሷል ተብሎ ኚሚታሰብበት ጊዜ አንስቶ በአስር ዓመት ጊዜ ውስጥ ዚንብሚት ክፍፍል ጥያቄ ካልቀሚበ በይርጋ ዚሚታገድ ስለመሆኑ

     

    ዹሰ/መ/ቁ.102662

    ዚካቲት 15 ቀን 2008 ዓ/ም

    ዳኞቜ፡-አልማው ወሌ ዓሊ መሐመድ ተኜሊት ይመሰል እንዳሻው አዳነ ቀነዓ ቂጣታ

    አመልካቜ፡- ወ/ሮ አልማዝ ለሌ- ጠበቃ ኀርሚያስ ደስታ ቀሚቡ፡፡ ተጠሪ፡- አቶ በቀለ በላቾው- ወኪል  ትርፍነሜ በቀለ ቀሚቡ

    መዝገቡ ተመርምሮ ተኚታዩ ፍርድ ተሰጥቷል፡፡

     ፍ ር ድ

     

    ጉዳዩ ጋብቻ ፈርሷል ሊባል ዚሚቜልበትን አግባብ ዚሚመለኚት ነው፡፡ጉዳዩ ዹተጀመሹው በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ዚደብሚብርሃን ወሚዳ ፍርድ ቀት ሲሆን ክሱን ያቀሚቡት ዹአሁኑ አመልካቜ ና቞ው፡፡ ዚክሱ ይዘትም፡- ኹአሁኑ ተጠሪ ጋር በአገር ባህል ዚጋብቻ አፈጻጞም ስርዓት ጋብቻ ፈጜመው ለአርባ አመታት ያህል አብሚው መኖራ቞ውን፣ ይሁን እንጂ ኚመስኚሚም 2006 ዓ/ም ጀምሮ ሊስማሙ ባለመቻላ቞ው በመካኚላ቞ው ሰላም እንደሌለ ገልፅው ጋብቻው ፈርሶ ዚጋራ ንብሚት እንዲካፈሉ ይወሰን ዘንድ ዳኝነት መጠዹቃቾውን ዚሚያሳይ ነው፡፡ ዹአሁኑ ተጠሪ ለክሱ በሰጡት መልስም ኚአመልካቜ ጋር ባልና ሚስት ዚነበሩ መሆኑን ሳይክዱ አመልካቜ ኚአስራ ዘጠኝ አመታት በፊት ቀቱን ጥለው መሄዳ቞ውንና ተለያይተው ዚሚኖሩ መሆኑን ጠቅሰው ክሱ በይርጋ ሊታገድ ይገባል  በማለት ዚመጀመሪያ ደሹጃ መቃወሚያ ያስቀደሙ ሲሆን በፍሬ ነገር ሚገድ ደግሞ ኚአመልካቜ ጋር ያፈሩት ዚጋራ ንብሚት ዹሌለ መሆኑን ዘርዝሹው ክሱ ውድቅ ሊሆን ይገባል ሲሉ ተኚራክሚዋል፡፡

     

    ዚግራ ቀኙ ክርክር በዚህ መልኩ ዚቀሚበለት ዚሥር ፍ/ቀትም ጉዳዩን መርምሮ በአመልካቜ እና በተጠሪ መካኚል ዹነበሹው ጋብቻ ኚአስር አመታት በፊት ፈርሷል ዹሚል ድምዳሜ ደርሶ ዚአመልካቜ ክሱ በይርጋ ዚታገደ ነው በማለት ውድቅ አድርጎታል፡፡ በዚህ ብይን ዹአሁኗ አመልካቜ ቅር በመሰኘት ይግባኛ቞ውን ለሰሜን ሾዋ አስተዳደር ዞን ኹፍተኛ ፍርድ ቀት ቢያቀርቡም ተቀባይነት አላገኙም፡፡


    ኹዚህም በኋላ አመልካቜ ዹሰበር አቀቱታ቞ውን ለክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቀት ሰበር ሰሚ ቜሎት አቅርበውም በጉዳዩ ላይ በተሠጠው ብይን መሰሚታዊ ዹሆነ ዹሕግ ስህተት ዹለም ተብሎ መዝገቡ ተዘግቶባ቞ዋል፡፡ ዹአሁኑ ዹሰበር አቀቱታው ዹቀሹበው ይህንኑ ውሳኔ በመቃወም ሲሆን ይህ ቜሎት ዹቀሹበውን አቀቱታ መርምሮ ተጠሪን በመጥራት ግራ ቀኙን በጜሑፍ አኚራክሯል፡፡እንዲሁም ዚወሚዳው ፍርድ ቀት ዋና መዝገብ እንዲመጣ አድርጓል፡፡

     

    በአጠቃላይ ዚክርክሩ ይዘት ኹላይ ዹተመለኹተው ሲሆን ምላሜ ማግኘት ዚሚገባው ዚጉዳዩ ጭብጥ በተጠሪና በአመልካቜ መካኚል ጋብቻ በሁኔታ ፈርሷል ተብሎ በበታቜ ፍርድ ቀቶቜ መወሰኑ ተገቢነት አለውን? ዚሚለውነው፡፡

    ኚክርክሩ ሂደት መገንዘብ ዚተቻለው ዚወሚዳው ፍርድ ቀት ዚግራ ቀኙን ምስክሮቜ ሰምቶ በአመልካቜናበተጠሪ መካኚልዚነበሚውጋብቻ በሁኔታ ፈርሷል በማለት በአመልካቜ በኩል ዹቀሹበውን ክርክር አልተቀበለውም፡፡ ፍርድ ቀቱ ወደዚህ ድምዳሜ ዹደሹሰው በአመልካቜና በተጠሪ መካኚል ዹነበሹው ዚጋብቻ ግንኙነታ቞ው ኹ1987 ዓ/ም ጀምሮ ተቋርጩ ግራ ቀኙ ለዚብቻ መኖር መጀመራ቞ው ተሹጋግጧል በሚል አቢይ ምክንያት ነው፡፡ ይህ ዚወሚዳው ፍርድ ቀት ዚፍሬ ነገር ማጣራትና ዚማስሚጃ ምዘና ድምዳሜ በዚህ ሚገድ ተመሳሳይ ዹሆነ ስልጣን ባለው ዹዞኑ ኹፍተኛ ፍርድ ቀት ሙሉ በሙሉ ተቀባይነት አግኝቷል፡፡ አመልካቜ በዚህ ቜሎት አጥብቀው ዚሚኚራኚሩት ግራ ቀኙ ሌላ ትዳር መስርተው ዚራሳ቞ውን ሕይወት ዚማይኖሩ መሆኑን፣ አልፎ አልፎ በጀና ምክንያት አመልካቜ ለፀበል ወደ ሌላ ቊታ ኚመሄዳ቞ው ውጪ አመልካቜና ተጠሪ ያልተለያዩና እስኚ መስኚሚም 2006 ዓ/ም ድሚስ አንድ ላይ ዚሚኖሩ መሆኑን ዘርዝሹው ለጉዳዩ አግባብነት ዹሌለው አስገዳጅ ውሳኔ ተጠቅሶ መወሰኑ ያላግባብ ነው በሚል ነው፡፡ እኛም ጉዳዩን ይህ ሰበር ቜሎት በመ/ቁ. 14290፣ 20983፣ 31891፣ 67924 እና በሌሎቜ በርካታ መዛግብት ኚሰጣ቞ው አስገዳጅ ውሳኔዎቜ ጋር አገናዝበን ተመልክተናል፡፡

    በመሰሚቱ ዚወሚዳው ፍርድ ቀት ለውሳኔው መሰሚት ያደሚገውና ይህ ሰበር ሰሚ ቜሎት በሰ/መ/ቁጥር 31891 ሌሎቜ ኹላይ በተጠቀሱት መዛግብት በሰጣ቞ው አስገዳጅ ውሳኔዎቜ በባልና ሚስት መካኚል ያለ ጋብቻ በፍ/ቀት በተሰጠ ዚፍቺ ውሳኔ ፈርሷል ባይባልም ዚተጋቢዎቜ ተለያይቶ ለሹጅም ጊዜ መኖር፣ በዚህም ጊዜ ሌላ ትዳር መሥርቶ መገኘት ዚቀድሞው ጋብቻ በሕጋዊ መንገድ ተቋርጧል ሊያስብል ይቜላል በማለት በአዋጅ ቁጥር 454/97 አንቀጜ 2(1) መሰሚት በዚትኛውም እርኚን ዹሚገኝ ፍርድ ቀትን ዚሚያስገድድ ዹሕግ ትርጉም ዚሰጠበት ጉዳይ ነው፡፡ ኹዚህም ውሳኔ ይዘትና መንፈስ መሚዳት ዚሚቻለው ዚጋብቻ መፍሚስ በተጋቢዎቜ ዚሚዥም ጊዜ መለያዚት ሊኹናወን ዚሚቜል መሆኑና ፍርድ ቀቱም በዚህ አግባብ ዹፈሹሰውን ጋብቻ እንደገና እንዲፈርስ ውሳኔ ዚሚሰጥበት አግባብ ዹሌለ መሆኑን ነው፡፡ በሰ/መ/ቁጥር 67924 ዹተሰጠው አስገዳጅ ዹሕግ ትርጉም ደግሞ በቀተሰብ ሕጉ አግባብ ዹመተጋገዝና ዚመተባበር ግዎታ቞ውን


    ሲወጡና ዚነበሩና ያልተለያዩ መሆኑ ኹተሹጋገጠ ጋብቻ በሁኔታ ፈርሷል ለማለት ዚማይቻል መሆኑን በመዝገቡ ኚተሚጋገጡ ፍሬ ነገሮቜ በመነሳት ዹተወሰነ ነው፡፡

    ወደ ተያዘው ጉዳይ ስንመለስም አመልካቜና ተጠሪ በሕጉ አግባብ ጋብቻ መሰርተው ልጆቜን ኚወለዱ በኋላ በ1987 ዓ/ም ጀምሮ በአካል ተለያይተው ለአስራ ዘጠኝ አመታት ያህል ሳይገናኙ ዚኖሩ መሆኑን ኚግራ ቀኙ ምስክሮቜ ቃል ዹተሹጋገጠ መሆኑን ዚበታቜ ፍርድ ቀቶቜ ደምድመዋል፡፡ ይህ ሰበር ሰሚ ቜሎት ያስቀሚበው ዚወሚዳው ፍርድ ቀት ዋና መዝገብም  ዚግራ ቀኙ ምስክሮቜ ዚመሰኚሩት ዚፍሬ ነገር ነጥብ በይዘቱ ዚበታቜ ፍርድ ቀቶቜ ኚደመደሙት ጋር ተመሳሳይነት ያለው መሆኑን ተገንዝቊአል፡፡ በመሆኑም አመልካቜ ኚተጠሪ ጋር እስኚ መስኚሚም 2006 ዓ/ም ድሚስ አልተለያዚንም በማለት ዚሚያቀርቡት ቅሬታ በስር ፍርደ ቀት ዋና መዝገብ ውስጥ በምስክሮቜ ኹተነገሹው ዚምስክርነት ቃል ይዘትና ፍሬ ነገሩን ዚማጣራትና ማስሚጃን ዹመመዘን ስልጣን ያላ቞ው ፍርድ ቀቶቜ ኚደሚሱበት ድምዳሜ ውጪ በመሆኑ ተቀባይነት ዹሚሰጠው ሁኖ አልተገኘም፡፡ በዚህ ሚገድ አመልካቜ ያቀሚቡት ቅሬታ ለዚህ ቜሎት በኢ.ፌ.ዲ.ሪፐብሊክ ሕገ መንግስት አንቀጜ 80(3(ሀ)) እና አዋጅ ቁጥር 25/1988 አንቀጜ 10 ድንጋጌዎቜ አግባብ ዹተሰጠውን ስልጣንም ያላገናዘበ ሁኖ አግኝተናል፡፡

    በመሰሚቱ ጋብቻ በተጋቢዎቜ መካኚል ዚመተጋገዝ፣ ዚመኚባበርና መደጋገፍ እንዲሁም አብሮ ዹመኖር ግዎታን ዚሚጥል መሆኑን ኹክልሉ ዚቀተሰብ ሕግ አዋጅ ቁጥር 213/1992 አንቀጜ 60 እና 61 ድንጋጌዎቜ ይዘትና መንፈስ ዹምንገነዘበው ጉዳይ ነው፡፡ ኹዚሁ  አኳያ በተጠሪና በአመልካቜ መካኚል ዹነበሹው ጋብቻ ይህ ሰበር ቜሎት አስቀድሞ በተመሳሳይ ጉዳይ ኹሰጠው ውሳኔ አንጻር ተቋርጧል? ወይንስ አልተቋሹጠም? ዹሚለውን ለመወሰን ኹፍ ብሎ በአመልካቜና በተጠሪ መካኚል በጋብቻ ውስጥ በግራ ቀኙ ዹሚጠበቁ ግዎታዎቜ ባግባቡ ሲተገበሩ ያልነበሩና እነዚህን ግዎታዎቜን ለመወጣት ደግሞ በአመልካቜ በኩል ያጋጠመው ሁኔታ በሕጉ ዚተጣሉባ቞ውን ግዎታ቞ውን ለመወጣት ዚማያስቜል ዹነበሹ መሆኑ ባልተሚጋገጠበት ሁኔታ አመልካቜ ኚተጠሪ ጋር አልተለያዚንም፣ በጀና ቜግር ምክንያት አልፎ አልፎ ለፀበል ሌላ ቊታ እሄድ ነበር በማለት ዚሚያቀርቡት ክርክር በክርክሩ ሂደት በማስሚጃ ዚተሚጋገጡትን ፍሬ ነገሮቜን መሰሚት አድርጎ ያልቀሚበ ሁኖ አግንተነዋል፡፡ ኹዚህም በተጚማሪ በተያዘው መዝገብና ይህ ሰበር ቜሎት አስገዳጅ ዹሕግ ትርጉም ዚሰጠባ቞ው መዛግብት ዚያዟ቞ው መሰሚታዊ ፍሬ ነገሮቜ ኹዚህ መዝገብ ኚተሚጋገጡት እውነታዎቜ ሙሉ በሙሉ ዚተመሳሳይነት ያላ቞ው ሁኖ እያለ አመልካቜም ሆነ ተጠሪ ሌላ ትዳር መስርተው ሕይወታ቞ውን በመምራት ላይ አይገኙም በማለት በሰ/መ/ቁጥር 31891 ዹተሰጠውን አስገዳጅ ዹሕግ ትርጉም በመተውና ግንኙነቱ ያልተቋሚጠ  ተጋቢዎቜን መሰሚት ተደርጎ በመ/ቁጥር 67924 ዹተሰጠውን ውሳኔ መሰሚት በማድሚግ አመልካቜ መኚራኚራ቞ው ኹአዋጅ ቁጥር 454/1997 አንቀጜ 2 (1) አተገባበር ጋር ዹሚጋጭ ሁኖ አግኝተናል፡፡ ስለሆነም ዚአመልካቜና ዚተጠሪ ግንኙነት ኹ1987 ዓ/ም ጀምሮ በሁኔታ ዹፈሹሰ


    በመሆኑ እና ለጉዳዩ አግባብነት በላቾው ኹላይ በተጠቀሱት መዛግብት በተሰጠው ትርጉም መሰሚት ዚጋራ ንብሚት ጥያቄም በአስር አመት ያልቀሚበ በመሆኑ ዚተጠሪ ክስ በይርጋ ዚታገደ ነው ተብሎ ብይን መሰጠቱ ዚሚነቀፍበትን ዹሕግ ምክንያት አላገኘንም፡፡ ሲጠቃለልም በጉዳዪ ላይ ዹተሰጠው ውሳኔ መሰሚታዊ ዹሆነ ዹሕግ ስሕተት ዚተፈጞመበት ሁኖ ስላላገኘነው ተኚታዩን ወስነናል፡፡

     ው ሳ ኔ

    1. ዚደብሚብርሃን ኹተማ ወሚዳ ፍርድ ቀት በመ/ቁጥር  0108191/06  በ22/08/2006 ተሠጥቶ በሰሜን ሾዋ መስተዳደር ዞን ኹፍተኛ ፍርድ ቀት በመ/ቁጥር 0114418 በ30/08/2006 ዓ/ም፣ በክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቀት ሰበር ሰሚ ቜሎት በመ/ቁጥር 030- 5041 ግንቊት 19 ቀን 2006 ዓ/ም ዹተሰጠው ውሳኔ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁጥር 348(1) መሰሚት ጞንቷል፡፡

    2. በአመልካቜና በተጠሪ መካኚል በአገር ባህል ዚጋብቻ አፈፃጾም ስርዓት ተመስርቶ ዹነበሹው ጋብቻ ለሚዥም ጊዜ ተለያይቶ በመኖር ምክንያት ፈርሷል በማለት ወስነናል፡፡

    3.  በዚህ ቜሎት ለተደሹገው ክርክር ዚወጣውን ወጪና ኪሳራ ዚዚራሳ቞ውን ይቻሉ ብለናል፡፡

     ት ዕ ዛ ዝ

    ኚደብሚብርሃን ኹተማ ወሚዳ ፍርደ ቀት ዚመጣ መዝገብ ቁጥር 0108191/06 በመጣበት አኳሀን ይመለስ ብለናል፡፡

    መዝገቡ ተዘግቷልፀወደ መዝገብ ቀት ይመለስ፡፡

    ዚማይነበብ ዚአምስት ዳኞቜ ፊርማ አለበት፡፡

     

    ወ/ኹ

  • ሞግዚት ዚማይንቀሳቀስ ንብሚት ሜያጭ ፈጜሞ ሲገኝ ሊወሰዱ ስለሚገቡ ዝርዝር ሁኔታዎቜ ዹሕግ ድንጋጌዎቜን በመተላለፍ ሞግዚቱ ለሚፈጜማ቞ው ድርጊቶቜፀ ወኪል ዹሆነ ሰው ኹተሰጠው ሥልጣን በላይ በሚሠራበት ጊዜ አግባብነት ያላ቞ው ዹውክልና ሕግ ድንጋጌዎቜ ተፈጻሚ ዹሚሆኑ ስለመሆኑ ዚተሻሻለው ዚቀተሰብ ሕግ አዋጅ ቁ.213/1992 አንቀጜ 306፣277 ዹፍ/ብ/ሕ/ቁ.2207/1

    ዹሰ/መቁ.103151

    መስኚሚም 24 ቀን 2008 ዓ.ም

    ዳኞቜ፡-አልማው ወሌ

     

    ሚታ ቶሎሳ ሙስጠፋ አህመድ ቀነዓ ቂጣታ

    ሌሊሮ ደሳለኝ

     

    አመልካቜ፡-አቶ ግርማ ብሩ አዹለ - ቀሚቡ

     

    ተጠሪ፡-አቶ መርዕድ ብስራት - ጠበቃ አበበ ማስሚሻ ጋር ቀሚቡ መዝገቡን መርምሹን ዹሚኹተለውን ፍርድ ሰጥተናል፡፡

     ፍ ር ድ

     

    ይህ ጉዳይ ዚቀት ሜያጭ ውል እንዲፈርስ ዹቀሹበ ክስን መነሻ ያደሚገ ክርክር ነው፡፡ ዚጉዳዩ አመጣጥ ሲታይ፡- ዚሥር ኚሳሜ /ዹአሁን ተጠሪ/ በፌዎራል ዚመጀመሪያ ደሹጃ ፍ/ቀት ባቀሚበው ክስ ዹወላጅ አባ቎ እና ዹ2ኛ ተኚሳሜ ዚጋራ ንብሚት ዹሆነውን በጉለሌ ክፍለ ኹተማ ቀበሌ 03 ዚቀት ቁጥር አዲስ ካሚታ ቁ.3329 ዹሆነውን ቀት 2ኛ ተኚሳሜ ኚሞግዚትነት ስልጣን ተቃራኒ ሚያዝያ 23 ቀን 2000 ዓ.ም በተደሹገ ሜያጭ ውል ለ1ኛ ተኚሳሜ በብር 350,000 ዚሞጠቜ ስለሆነ 1ኛ ተኚሳሜም /ዹአሁኑ አመልካቜ/ ዚኚሳሜና ዚሌሎቜ ሰዎቜ ዚጋራ ንብሚት መሆኑን እያወቀ ለቅን ልቡና ተቃራኒ በሆነ መንገድ ስለገዛ ዚሜያጭ ውሉ እንዲፈርስልኝ፣ 1ኛ ተኚሳሜ ቀቱን እንዲያስሚክበኝ በማለት አመልክቷል፡፡

     

    ይህን ክስ በተመለኹተ ተኚሳሟቜ መልስ እንዲሰጡበት ዚታዘዘ ሲሆን ዚሥር 1ኛ ተኚሳሜ /ዹአሁን አመልካቜ/መጥሪያ ደርሶት ዚጜሑፍ መልስ ስላልሰጠ ታልፏል፡፡ ዚሥር 2ኛ ተኚሳሜ በሰጠቜው መልስ ባለቀ቎ ኹሞተ በኋላ ልጆቜ ለማሳደግ ዚተ቞ገርኩ በመሆኑ ዚቀት ሜያጭ ውል ፈጜሜአለሁ፡፡ 1ኛ ተኚሳሜም ዚቀቱን ሞያጭ ገንዘብ እንደውሉ አልኚፈለኝምፀ እኔ ቀቱን ዚሞጥኩኝ ለኚሳሜና ለሁለት ወንድሞቹ ጥቅም እንጂ ለግሌ ጥቅም አይደለምፀ ፍ/ቀቱ ዹመሰለውን ውሳኔ ቢሰጥ አልቃወምም በማለት ተኚራክራለቜ፡፡ 1ኛ ተኚሳሜ ክርክር በሚሰማበት ቀን ቀርቩ  ሲኚራኚር


    ሞግዚት ዚማይንቀሳቀስ ንብሚት መሞጥ ትቜላለቜ፣ እኔ በቀቱ ላይ ሰፊ ለውጥ ያደሚኩ ስለሆነ ውሉ ሊፈርስ አይገባም በማለት ተኚራክሯል፡፡

     

    ኹዚህ በኋላ ፍ/ቀት ግራ ቀኙን በማኚራኚር፣ ዚኚሳሜን ዹሰው ምስክር በመስማት በሰጠው ውሳኔ በተኚሳሟቜ መካኚል ሚያዝያ 23 ቀን 2000 ዓ.ም ዹተደሹገው ዚቀት ሜያጭ ውል ዚልጆቜን ጥቅም በሚጎዳ መልኩ ስለተፈጞመ ፈርሶ ተዋዋይ ወገኖቜ ወደ ነበሩበት ይመለሱ፣ 2ኛ ተኚሳሜ ብር 60,000 ለ1ኛ ተኚሳሜ ትመልስ፣ 1ኛ ተኚሳሜ በገዙት ይዞታ ሲገለገሉበት በነበሹው ቀት ላይ ያወጡት ወጪ ካለ ክስ አቅርቩ መጠዹቅ ይቜላል በማለት ወስኗል፡፡ ዚሥር 1ኛ ተኚሳሜ ይህን ውሳኔ በመቃወም ይግባኝ ማመልኚቻውን ለፌደራል ኹፍተኛ ፍ/ቀት ያቀሚበ ሲሆን ፍ/ቀቱ ግራ ቀኙን በማኚራኚር በሰጠው ውሳኔ፣ ዚቀቱ ሜያጭ ዋጋ በአብዛኛው ስላልተኚፈለ 2ኛ ተኚሳሜ ለግል ጥቅም አውላለቜ፣ ዚልጆቜ ቅጥም ላይ ጉዳት ድርሷል ዚሚያስብል ስላልሆነ፣ዚሜያጭ ውሉን ለማፍሚስ በቂና አሳማኝ ምክንያት ስለሌለ ሊፈርስ አይገባም በማለት ዚሥር ውሳኔ በመሻር ወስኗል፡፡ ዚሥር ኚሳሜ ይህን ውሳኔ በመቃወም ይግባኝ ማመልኚቻውን ለፌዎራል ጠቅላይ ፍ/ቀት ያቀሚበ ሲሆን ፍ/ቀቱ ግራ ቀኙን በማኚራኚር በሰጠው ውሳኔ፣ ዚቀት ሜያጭ ውሉ ዚኚሳሜን ጥቅም ዚሚጎዳ ስለሆነ ውሉ ሊፈርስ ይገባል በማለት ዚፌዎራል ኹፍተኛ ፍ/ቀት  ውሳኔ በመሻር ዚፌዎራል ዚመጀመያ ደሹጃ ፍ/ቀት ውሳኔን በማጜናት ወስኗል፡፡ ዹአሁን ዹሰበር አቀቱታም ይህን ውሳኔ በመቃወም ለማስለወጥ ዹቀሹበ ነው፡፡

     

    ዹአሁን አመልካቜ ሐምሌ 10 ቀን 2006 ዓ.ም በተጻፈ አቀቱታ ዚተጠሪ ሞግዚትና አስተዳዳሪ ዚነበሩት ወ/ሮ ክብካብ አስፋው ዚቀት ሜያጭ ውሉን ያደሚጉት ለተጠሪ እና ለሌሎቜ ሁለት ወንድሞቻ቞ው መልካም አስተዳደር ስለሆነ ውሉን ዹተደሹገው ለልጆቹ ቅጥም መዋሉ በተጠሪም ሞግዚት በጜሑፍ እና በምስክሮቜ በስር ፍ/ቀት ዹተሹጋገጠ ሆኖ ሳለ ውሉ ሊፈሚስ  ይገባል በማለት ዹተሰጠ ውሳኔ መሰሚታዊ ዹሕግ ስህተት ያለበት ነው፡፡ ዚተጠሪ ሞግዚት ኚተቀበለቜው ዚቀት ሜያጭ ውሉ ገንዘብ ዚተጠሪ ድርሻ ብር 10,000 ብቻ ስለሆነ ውሉ ዚሚፈርስበት ምክንያት ዚለም፡፡ አመልካቜ ቀቱን ኹገዛሁ በኋላ ሌላ አዲስ ሰርቪስ ቀት ክፍሎቜ ብር 450,000 በላይ ወጪ በማድሚግ በቀቱ ላይ ኹፍተኛ ዹሆነ ዚይዘት ለውጥ አድሚጎበታል፡፡ ስለዚህ ዚፌዎራል ዚመጀመሪያ ደሹጃ ፍ/ቀት እና ዚፌዎራል ጠቅላይ ፍ/ቀት ውሉ ፈርሶ ወደ ነበራቜሁበት ተመለሱ በማለት ዚወሰኑት ውሳኔ መሰሚታዊ ዹሕግ ስህተት ያለው ስለሆነ እንዲሻርልኝ፣ ዚፌዎራል ኹፍተኛ ፍ/ቀት ውሳኔ እንዲፀናልኝ በማለት አመልክቷል፡፡

     

    ዹሰበር አጣሪ ቜሎትም መዝገቡን በመመርመር "በአመልካቜ እና በተጠሪ ሞግዚት መካኚል ዹተደሹገው ዚቀት ሞያጭ ውል ይፍሚስ ተብሎ በሥር ፍ/ቀቶቜ ዹመወሰኑን አግባብነት ኚመዝገብ ቁ.46490 አንጻር ለመርመር ሲባል አቀቱታው ለሰበር ያስቀርባል በማለት ተጠሪ መልስ እንዲሰጥ


    በታዘዘው መሰሚት መስኚሚም 7 ቀን 2007 ዓ.ም ዚተጻፈ መልስ አቅርቧል፡፡ ዚመልሱ ይዘትም፡- ዚተጠሪ ሞግዚት ዚማይንቀሳቀስ ንብሚት መሞጥ አትቜልም፡፡ እኔ ኚቀቱ ድርሻ እያለኝ ያለ እኔ ፈቃድ ሞጣለቜ፡፡ ዚተጠሪ መብት መጣስ እና መጎዳት ዹሚጀምሹው ኹዚህ መሰሚታዊ ኹሆነው ዚባለቀትነት መብቶቜ አኳያ ስንነሳ ነው፡፡ እኔ በቀቱ ሜያጭ ኹፍተኛ ጉዳት እንደደሚሰብኝ አስሚድቌአለሁ፣ አመልካቜ ግን ኚሜያጩ ጥቅም ያገኘሁት መሆኑን አላስሚዳም፡፡ አመልካቜ ኚቀቱ ሜያጭ ገንዘብ ዹኹፈለው ብር 60,000 ብቻ ሲሆን ቀቱን ተሹክቩ እያኖሚበት ነው፣ ኚጉዳት በቀር ጥቅም ሊኖር አይቜልም፡፡ ተጠሪው በሜያጩ ጉዳት እንጂ ያገኘሁት ጥቅም ስለሌለ ለሰበር መዝገብ ቁ.46490 ኹሰጠው ውሳኔ ጋር ዹማይቃሹን ስለሆነ ውሳኔው እንዲፀናልኝ፣ ዹቀሹበው አቀቱታ ውድቅ እንዲደሚግልኝ፡፡ አመልካቜ ኚቀቱ ድርሻ ዚተጠሪ ድርሻ 10,000 ብር ብቻ ስለሆነ ሊፈርስ አይገባም በማለት ያቀሚበው ክርክር ዚባለቀትነት መብትን ዚጣሰ እና ሕጉ ተቃራኒ ስለሆነ ተቀባይነት ዚለውም፡፡ አመልካቹ በቀቱ ላይ ግንባታ ስለመካሄዱ ያቀሚበው ማስሚጃም ዚለም፣ በቀቱም ላይ ዚይዘትም ሆነ ዚቅርጜ ለውጥ አላደሚገም፣ ዚተጠሪ ሞግዚት ዚቀት ሜያጩን ገንዘብ ማባኚና቞ውን እንጂ ለልጆቜ ጥቅም ያወሉት መሆኑን ያሚጋገጠ ማስሚጃ  ዚለም፡፡ ስለዚህ አመልካቜ ያቀሚበው አቀቱታ ውድቅ ሆኖ ዚፌዎራል መጀመሪያ ደሹጃ ፍ/ቀት እና ዚፌዎራል ጠቅላይ ፍ/ቀት ውሳኔ መሠሚታዊ ዹሕግ ስህተት ዚለበትም ተብሎ እንዲፀናልኝ፣ ወጪና ኪሳራ እንዲወሰንልኝ በማለት ተኚራክሯል፡፡ አመልካቜ ጥቅምት 04 ቀን 2007 ዓ.ም በተጻፈ ዚመልስ መልስ አቀቱታውን በማጠናኹር ተኚራክሯል፡፡

     

    ዚጉዳዩ አመጣጥ ኹላይ እንደተመለኚተ ሲሆንፀ ይህ ሰበር ሰሚ ቜሎትም ዚግራ ቀኙ  ክርክር ለሰበር አቀቱታው መነሻ ኹሆነው ውሳኔ እና አግባብነት ካላ቞ው  ዹሕግ  ድንጋጌዎቜ ጋር በማገናዘብ አቀቱታው ያስቀርባል ሲባል ኚተያዘው ጭብጥ አንጻር እንደሚኚተለው መርምሮታል፡፡ መዝገቡን እንደመሚመርነው ተጠሪ ባቀሚበው ክስ ዚሜያጭ ውል ዚተፈጞመበት ቀት ላይ ድሚሻ እያለኝ ዚእኔን ጥቅም በሚጎዳ መልክ ሞግዚት ዚሆነቜው ወ/ሮ ክብካብ ሣህሉ ወልደማርያም በሜጚጭ ውል ለአመልካቜ ዚሞጠቜ ስለሆነ ውሉ እንዲፈርስልኝ በማለት አልክቷል፡፡ ዚተጠሪ ሞግዚት /ዚሥር 2ኛ ተኚሳሜ/ በጜሑፍ ባቀሚበቜው መልስ ቀቱን ዚሞጥኩት ለተጠሪ እና ለሌሎቜ ወንድሞቹ ቅጥም ነው በማለት ዚተኚራኚሚቜ ቢሆንም እንደምስክር ሆነ በሰጠቜው ቃል ደግሞ ኚቀቱ ሜያጭ ገንዘብ ውስጥ ብር 60,000 ብቻ ዚተቀበለቜ እንደሆነና ለራሷ ትምህርት ክፍያ እንደኚፈለቜና ቀሪውን ለወንድሟ እንዳበደሚቜ ገልጻለቜ፡፡ አመልካቜ በበኩሉ መጥሪያ ደርሶት ዹፍሑፍ መልስ ባለመስጠቱ ዚታለፈ ስለሆነ ዚጜሑፍ መልስ እና ማስሚጃ በማቅሚብ በማስሚዳት መኚራኚር ዚነበሚበትን ክርክር በተመለኹተ መብት አጥቷል፡፡ ስለዚህ አልካቜ በጜሑፍ መኚራኚር ዚነበሚበትና ማስሚጃ በማቅሚብ ማስሚዳት ዚነበሚበትን ፍሬ ነገር በተመለኹተ አሁን ለማንሳት ዚሚቜልበት ዹሕግ መሰሚት ዚለውም፡፡ ተጠሪ ባቀሚበው ክርክር አመልካቜ ኚተጠሪ ሞግዚት  ጋር


    ዚቀት ሜያጭ ውሉን ሲፈጜም በቀቱ ላይ ልጆቜ ድርሻ ያላ቞ው መሆኑን ውሉ እያመለኚተ ነው ቀቱን ዹገዛው ዚሚለውን፣ አመልካቜ ይህን ፍሬ ነገር ክዶ እዚተኚራኚሚ አይደለም፡፡ አመልካቜ አጥብቆ ዚሚኚራኚሚው በሞግዚቱ በኩል ዹተደሹገው ዚቀቱ ሜያጭ ለልጆቜ ጥቅም ነው እንጂ ጥቅማ቞ውን ዚሚጎዳ አይደለም ዹሚል ነው፡፡ ዚተጠሪ እናት ዚሆነቜው ዚሥር 2ኛ ተኚሳሜ ዚተሻሻለው ዚቀተሰብበ ሕግ አዋጅ ቁ.213/1992 አንቀጜ 220/1/ መሰሚት ሕጋዊ ዚሞግዚትነት ስልጣን እንደተሰጣ቞ው ኚመዝገቡ መሚዳት ይቻላል፡፡ ይህ ማለት ዚሥር 2ኛ ተኚሳሜ ተጠሪን በመወኹል ሕጋዊ ተግባሮቜን ለተጠሪ ጥቅም ለመፈጾም ስልጣን ዚተሰጣ቞ው መሆኑን ያመለክታል፡፡ በዚሁ ዚተሻሻለው ዚቀተሰብ ሕግ አንቀጜ 277 ዚሞግዚት ስልጣን በተመለኹተ ዚማይንቀሳቀስ ንብሚት ኚመሞጥ ጋር ተያይዞ ዹሚለው ነገር ዚለውም፡፡ ነገር ግን ሕጉ ሞግዚት መሞጥ ዚሚቜላ቞ውን ዚንብሚት ዓይነቶቜ በመዘርዘር በማስቀመጡ፣ ኹዚህ ዝርዝር ወጭ ያሉትን ንብርቶቜ በተመለኹተ ሞግዚት መሞጥ አይቜልም ቢባል እንኳን ሞግዚት ዚማይንቀሳቀስ ንብሚት ሜያጭ ፈጜሞ ኹተገኘ ግን ምላሾ ለማግኘት ሌላ ሕግ መፈተሜ አስፈላጊ ሆኖ ይታያል፡፡ ኹዚህ አንጻር ዚተሻሻለው ዚቀተሰብ ሕግ አዋጅ ቁ.213/1992 አንቀጜ 306 እንደሚደነግገው "ዹሕግ ድንጋጌዎቜን በመተላለፍ ሞግዚቱ ለሚፈጜማ቞ው ድርጊቶቜፀ ወኪል ዹሆነ ሰው ኹተሰጠው ሥልጣን በላይ በሚሠራበት ጊዜ አግባብነት ያላ቞ው ዹውክልና ሕግ ድንጋጌዎቜ ተፈጻሚ ይሆናሉ" ዹሚል ነው ፡፡ በዚህ መሰሚት ተወካዩ ኹተሰጠው ስልጣን ውጭ በመውጣት ዚሰራውን ስራ በተመለኹተ ዹፍ/ብ/ሕ/ቁ.2207/1/ እንደሚያመለክተው "ተወካዩ ኚስልጣኑ ውጭ ዚሠራው ስራ በቅን ልቡና ሆኖ ሲገኝ ሥራውን ወካዩ እንዲያጞድቅለት ይገደዳል" ዹሚል ነው፡፡ በዚህ አግባብ ዚሞግዚቱ "ቅን ልቡና" መታዚት ያለበት ዚተሰራ ስራ ዹልጁን ጥቅም ዚሚጎዳ ነው ወይስ አይደለም? ኹሚል አንጻር መሆን እንዳለበት ነው፡፡

     

    ዚፌዎራል ጠቅላይ ፍ/ቀት ሰበር ሰሚ ቜሎት በሰበር መዝገብ ቁ.46490 መጋቢት 21 ቀን 2002 ዓ.ም በሰጠው አስገዳጅ ዹሕግ ትርጉም ሞግዚት ዚማይንቀሳቀስ ንብሚት ለልጆቜ መልካም አስተዳደግና ጥቅም ዹሾጠ መሆኑ ኹተሹጋገጠ ዚሜያጭ ውል ለማፍሚስ ዚሚያስቜል በቂ ምክንያት አይደለም በማለት ወስኗል፡፡ ይህ ማለት ዚማይንቀሳቀስ ንብሚት ሜያጭን በተመለኹተ ዚሜያጭ ውሉ ሊፈርስ ይገባል ወይስ አይገባም ዹሚል ጭብጥ መታዚት ያለበት ለልጆቜ ቅጥም መሆን አለመሆኑን በማጣራት ነው፡፡ ኹዚህ አንጻር በተጠሪ ሞግዚት እና በአልመካቜ መካኚል ዹተደሹገውን ዚቀት ሜያጭ ውል ለተጠሪ እና ለሌሎቜ ወንድሞቹ ጥቅም ዹዋለ ነው ወይስ አይደለም? ዹሚለው ጭብጥ ሲታይ ለተጠሪ ጥቅም መዋሉን ዚሚያመለክት ምንም ነገር ዚለም፡፡ ዚተጠሪ ሞግዚት ኚቀቱ ሜያጭ አመልካቜ ዚኚፈላት ገንዘብ ብር 60,000 እንደሆነ ኹዚህ ውስጥ ብር 10,000 ለትምህርት እንደኚፈለቜ፣ ቀሪውን ለወንድሟ እንዳበደሚቜ አሚጋግጣለቜ፡፡  ይህ ማለት ኚቀት ሜያጭ ዹተገኘው ገንዘብ ለተጠሪም ሆነ ለሌሎቜ ልጆቜ አለመዋሉን   ያመለክታል፡፡


    እንዲሁም ኚቀቱ ሜያጭ ዹተገኘ ገንዘብ ለልጆቹ ጥቅም መዋሉን ዚሚያመለክት ማስሚጃ መቅሚቡን ዚሥር ፍ/ቀቶቜ ያሚጋገጡት ነገር ዚለም፡፡ አመልካቜ ራሱ ኚቀቱ ሜያጭ ብር 350,000 ውስጥ እስካሁን ዹኹፈለው ብር 60,000 ብቻ ሲሆን ቀሪውን ገንዘብ ያለመክፈሉ ግራ ቀኙ ዚሚካኚዱት ጉዳይ ስላልሆነ፣ ዚቀቱ ሜያጭ ውል ለተጠሪ እና ለሌሎቜ ልጆቜ ጥቅም ዹዋለ ነው ለማለት ዚሚያቜል አንድም ነገር ዚለም፡፡ አመልካቜ ቀቱ ዚተሞጠበትን ገንዘብ አብዛኛውን ሳይኚፍል እንዲያውም አነስተኛ ገንዘብ ብቻ ኹፍሎ በዚህ ሜያጭ ዚልጆቹ ጥቅም ተጠብቆላ቞ዋል፣ ዚሜያጭ ውሉም ለልጆቜ ጥቅም ዹተደሹገ ነውፀ ለተጠሪና ለሌሎቜ ወንድሞቹ መልካም  አስተዳደግ ውሏል በማለት ዚሚያቀርበው ክርክር ሚዛን ዹሚደፋ ሆኖ አይታይም፡፡ ስለዚህ ዚሚያዝያ 23 ቀን 2000 ዓ.ም በተጠሪ ሞግዚትና በመአልካቜ መካኚል ዹተደሹገው ዚቀት ሜያጭ ውል ለተጠሪና ለሌሎቜ ወንድሞቹ ማለትም ለልጆቜ ጥቅም እና መልካም አስተዳደግ ያልዋለ መሆኑ ስለተሚጋገጠ፣ ዚሞያጭ ውሉ ሌፈርስ አይገባም በማለት አመልካቜ ያቀሚበው ክርክር በዚትኛውም ዹሕግ መመዘኛ ተቀባይነት ያለው ሆኖ አልተገኘም፡፡

     

    ሌላው አመልካቜ ባቀሚበው ክርክር ተጠሪ ኚቀቱ ያለው ድርሻ አነስተኛ መሆኑን በመግለጜ ለውሉ መፍሚስ መክንያት ሊሆን አይቜልም ዹሚለው ሲታይ ተጠሪ ኚቀቱ ድርሻ እስካለው ድሚስ ዚጋራ ንብሚቱ ኚሱ ፈቃድ ውጭ መሞጥ ዚሌለበት መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ ኚልጆቜ መብት አንጻር ዚአመልካቜ ክርክር ተቀባይነት ዚለውም፡፡ በሌላ በኩል አመልካቜ ቀቱን ኹገዘሁ በኋላ በቀቱ ላይ ግንባታ አካሄጃለሁ ያለውን በተመለኹተ ተጠሪ ምንም ዓይነት ግንባታ አልተደሹገም በማለት ክዶ ዚተኚራኚሚ ሲሆን፣ አመልካቜ ደግሞ ዚጜሑፍ ክርክር በማቅሚብ በማስሚጃ ስላላስሚዳ፣ በሥር ፍ/ቀት በማስሚጃ ያላስሚዳውን ክርክር ለዚህ ሰበር ሰሚ ቜሎት እንደቅሬታ ነጥብ ማቅሚቡ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ.329/1/ መሰሚት ተቀባይነት ዚለውም፡፡ በአጠቃላይ ዚሥር ፍ/ቀቶቜ ዚሜያጭ ውሉ ዚልጆቜን ጥቅም ዚሚጎዳ ስለሆነ ውሉ ፈርሶ ግራ ቀኙ ወደ ነበሩበት ሊመለሱ ይገባል፣ አመልካቜ በቀቱ ላይ ያወጣ ወጪ ካለ ኚሶ መጠዹቅ ይቜላል በማለት ዚሰጡት ውሳኔ መሰሚታዊ ዹሕግ ስህተተ ዹሌለው በመሆኑ ዹሚኹተለው ውሳኔ ተሰጥቷል፡፡

     

     ው ሳ ኔ

     

    1. ዚፌዎራል መጀመሪያ ደሹጃ ፍ/ቀት በመዝገብ ቁ.201566 በ07/08/2005 ዓ.ም ዹሰጠው ውሳኔ፣ እንዲሁም ዚፌዎራል ኹፍተኛ ፍ/ቀት በመዝገብ ቁ.137501 ታህሳስ 22 ቀን2006 ዓ.ም ዹሰጠውን ውሳኔ መሰሚታዊ ዹሕግ ስህተት ያለው  በመሆኑ በመሻር ዚፌዎራል ጠቅላይ ፍ/ቀት በመዝገብ ቁ.98101 በ22/09/2006 ዓ.ም ዹሰጠው ውሳኔ መሰሚታዊ ዹሕግ ስህተት ዹሌለው በመሆኑ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ.348/1/ መሰሚት ጞንቷል፡፡


     

    2.  ዹዚህ ውሳኔ ግልባጭ ለስር ፍ/ቀቶቜ ይድሚስ ብለናል፡፡

    3. ግራ ቀኙ በዚህ ቜሎት ዚደሚሰባ቞ውን ወጪና ኪሳራ ዚዚራሳ቞ውን ይቻሉ ብለናል፡፡ መዝገቡ በውሳኔ ስለተዘጋ ወደ መዝገብ ቀት ይመለስ ብለናል፡፡

    ዚማይነበብ ዚአምስት ዳኞቜ ፊርማ አለበት፡፡

     

    ማ/አ

  • በተሻሻለው ዚኢ.ፌ.ዲ.ሪ ዚቀተሰብ ህግ መሰሚት ባልና ሚስት ዚጋራ ንብሚታ቞ውን እኩል ዚማስተዳደር መብት ያላ቞ውና ዚጋራ ስምምነት ሳይኖር ንብሚትን ለሌላ 3ኛ ወገን በአንደኛው ተጋቢ ፍቃድ ብቻ ዹተላለፈ ኹሆነና ይህንን ስምምነቱን ያልሰጠው ተጋቢ በህጉ በተፈቀደለት ጊዜ ገደብ ውስጥ ዚይፍሚስልኝ ጥያቄውን ካላቀሚበ ዹተፈፀመው ተግባር እንደፀና ዹሚቆይ ስለመሆኑ አዋጅ ቁ.213/92 አንቀፅ 68፣69

     

    ዹሰ/መ/ቁ. 103721

    ዚካቲት 03 ቀን 2008 ዓ.ም

     

     

    ዳኞቜ፡- ተሻገር ገ/ስላሎ

    ሙስጠፋ አህመድ ተፈሪ ገብሩ

    ሞምሱ ሲርጋጋ አብርሃ መሰለ

     

    አመልካቜ፡-  ወ/ሮ ሰሚራ ጀማል ኹጠበቃ ሰለሞን ታደሰ ቀሚቡ ተጠሪ፡- 1ኛ. አቶ ጀማል እንዲሪስ ኹጠበቃ መሰሚት ስዩም ጋር ቀሚቡ

    2ኛ. ወ/ሮ ሉላ አሹፈ አልቀሚቡም

    3ኛ.አቶ ሀጎስ አብዱራህማን በመዝገብ ቀት በኩል እንዲሰሙ ተናግሯል፡፡

    መዝገቡ ተመርምሮ ተገቢውን ዳኝነት ለመስጠት ለዚካቲት 01 ቀን 2008 ዓ/ም ቀጠሮ ዚያዘ ሲሆን በዚህም መሰሚት መዝገቡን መርምሹን በአዳሪ በዚሁ እለት ዹሚኹተለውን  ፍርድ ሰጥተናል፡፡

     ፍ ር ድ

    ይህ ዹሰበር ጉዳይ በአሁን አመልካቜና 1ኛ ተጠሪ መካኚል ዹነበሹው ጋብቻ በፍ/ቀት ዚፍቺ ውሳኔ መሰሚት መፍሚሱን ተኚትሉ በአሁን አመልካቜ ዚጋራ ንብሚት ድርሻ ጥያቄ መነሻ ዚስር ፍ/ቀቶቜ ዚጋብቻ ውጀት በሆነው ዚንብሚት ክርክር ላይ ዚሰጡትን ዳኝነት በዚህ ሰበር ሰሚ ቜሎት ክርክር ካስነሳው ዚውሳኔ ክፍል አንፃር ተመልክቶ ዚውሳኔውን አግባብነት ኚግራ ቀኙና ክርክሩ ዹሚመለኹተው ሆኖ ዹተገኘው 3ኛ ተጠሪም ካቀሚቡት ክርክር ጋር በማገናዘብ አስፈላጊውን ዳኝነት ለመስጠት በሚል ዹቀሹበ ነው፡፡

     

    ዚጉዳዩም አመጣጥ ባጭሩ እንደሚኚተለው ነው በአሁን አመልካቜ እና 1ኛ ተጠሪ መካኚል ሚያዚያ 21  ቀን 1987 ዓ/ም ተደርጎ ዹነበሹው ጋብቻ ግንቊት 24 ቀን 2003 ዓ/ም  በፍ/ቀት ዚፍቺ ውሳኔ መፍሚሱን ተክትሎ ዹአሁን ተጠሪ ሀምሌ 27 ቀን 2003 ዓ/ም ተሻሜሎ ባቀሚቡ ማመልኚቻ ዚጋራ ንብሚት ናቾው ያሏ቞ውን ናቾው ዚሚንቀሳቀስና ዚማይንቀሳቀስ ንብሚቶቜ በመዘርዘር ድርሻ቞ው ተለይቶ ይወሰንላቾው ዘንድ ተገቢ ዚነበሩትን ዹአሁን 1ኛ ተጠሪን እና ዹ1ኛ ተጠሪ ሌላ ሚስት ዚሆነቜን ዹአሁን 2ኛ ተጠሪን በተኚሳሜነት ላይ ደመወዝ በዚሁ ዚጋብቻ ውጀት በሆነው ዚንብሚት ድርሻ ጥያቄ ላይ፣ እንደዚህም 1ኛ ተጠሪ ዚጋራ ንብሚትን ሲያስተዳድር ዚደሚሰው፣  ጉዳት ሲታወቅ በኃላ ተገቢውን ዚካሳ ለአመልካቜ እንዳይኚፍል ይወሰንልኝ   በማለት


    ዳኝነት ጠይቀዋል፡፡ እንደክርክራ቞ው ያስሚዳልናል ያሏ቞ውን ዹሰውና ዚሰነድ ማስሚጃም አያይዘው አቀርበናል፡፡

     

    ዹአሁን 1ኛ እና 2ኛ ተጠሪዎቜ ዚጋራ ንብሚት ናቾው በሚል በአሁን አመልካቜ ዚክስ ማመልኚቻ ላይ ኚተዘሚዘሩት ንብሚቶቜ ዚጋራ ንብሚት ዚሆኑትን በማመን፣ በጋራ ሀብትነት ዚማይታወቁትንፀ ዚሚያገኙትን ደግሞ በመካድ በአመልካቜ ክስ በተዘሹዘሹው ዚንብሚት ዝርዝር አንፃር መልስ ዚሰጡ ሲሆንፀ በንብሚት አስተዳደር ሚገድ ያደሚስኩት ጉዳት ዹሌላ በመሆኑ ዹሰጠው  ጥያቄ አይመለኹተኝም በማለት ክርክራ቞ውን አቅርቧዋል፡፡ ለክርክሩም ድጋፍ ያላ቞ውን ማስሚጃዎቜ አያይዘው አቅርበዋል፡፡

     

    ዹአሁን 3ኛ ተጠሪም ዚጋራ ንብሚት ነው በሚል በአሁን አመልካቜ ኚተጠቀሱት ንብሚቶቜና መካኚል በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍል ኹተማ ወሚዳ 3 ክልል በቀት  ቁጥር 2545  ዚሚታወቀውን ቀት በውል አዋዋዩ ክፍል ዘንድ ጂ. ኀስ. ኀ.ጄኔራል ትሬድንግ ኃ/ዹተ/ዹግል ማህበር ኚተባለው ድርጅት ዚገዙት ስለሆነ ዚአመልካቜን ጥያቄ ውድቅ ለማድሚግ ይወሰንልኝ በማለት በጉዳዩ ላይ ጣልቃ ገብተውም ተኚራክሚዋል፡፡ ለዚህም ክርክራ቞ው ለማስሚጃነት ሰነዶቜን እንዳቀሚበም ዚመዝገቡ መልሰን ያስሚዳል፡፡

     

    እኚሁ ጣልቃ ገብ ያቀሚቡትን ክርክር አስመልክቶ ዹአሁን አመልካቜ ጣልቃገብ ፍ/ቀቱ በንብሚቱ ላይ ዚእግድ ትእዛዝ በሰጠበት ንብሚት ላይ ግዥ ዹፈጾሙ ስለሆነ ዚሜያጭ ውሉ ኚጅምሩ ፈራሜ ስለሆነ ጥያቄው ተቀባይነት ዹለውም በማለት ተኚራክሚዋል፡፡

     

    ዹአሁን 1ኛ እና 2ኛ ተጠሪዎቜ ይህንኑ በቁጥር 2545 ተመዝግቩ ዚሚታወቀውን ቀት አስመልክቶ ንብሚቱ በማናቾውም ስም ተመዝግቩ ዚሚታወቅ ዚጋራ ንብሚት ባለመሆኑ እንጂ ዚጋራ ንብሚት ተቆጥሮ መቅሚቡ ተገቢ አይደለም በማለት አመልካቜ ባቀሚቡት ክስ ቀጥተኛ መልስ ዚሰጡ ኹመሆኑም በላይ በጣልቃ ገብ በኩል ዹቀሹበው ክርክር አስመልክቶ ደግሞ ተቃውሞ ዚሌለባ቞ው መሆኑን ገልጞናል፡፡

     

    ሁሉም ወገኖቜ ኹላይ ባጭሩ ለይዞታ ደሹጃ ዹተገለጾውን ዚጹሁፍ ክርክር ካደሚጉ በኋላ ለጉዳዩም ላይ ዹቃል ክርክር እንዳደሚጉ መዝገቡ ያስሚዳል፡፡

     

    ዚስር ፍ/ቀትም ኚግራ ቀኙ ክርክር በመነሳት በአኚራካሪነታ቞ው በጭብጥነት ተይዘው ኚማስሚጃ አንፃር ለማዚት ዳኝነት ያስፈልጋ቞ዋል፡፡ በማለት ኚሙግት ደሹጃ ደርሶ ለማስሚጃ ሰምቶ ዳኝነት ካሳሚፈባ቞ው ንብሚቶቜ መካኚል በአኚራካሪያ቞ው ኹዚህ ሰበር ደሹጃ ዘልቀው ኚደሚሱት መካኚል አንዱ በቀት ቁጥር 2545 ዹተመዘገበውን ቀት አስመልክቶ


    ዹአሁን አመልካቜ በጋብቻ ዘንድ ዚተፈራውን ይህንኑ ንብሚት ኚእኔ ለማሞሜ ሲል ያለ እኔ ፈቃድ ጀ. ኀስ.ኀ አጄኔራል ትሬድንግ ኃ/ዹተ/ዹግል ማህበር ወደ ተባለው ድርጅት በመዋጚነት አስገምቶ አሜሜቶ ዹሰጠ በመሆኑፀ እንዲሁም ይህን ንብሚት ዹአሁን 3ኛ ተጠሪ ፍ/ቀቱ በንብሚቱ ላይ ዚእግድ ትእዛዝ ኚተሰጠበት በኋላ እንዲገዙት ዹተደሹገ ስለሆነ ንብሚቱ ዚጋራ ሀብት መሆኑ ታውቆ በድርሻዬ ልኹፍል ይገባል በማለት ዚተኚራኚሩ ቢሆንም በኢፊድሪ ዚፍትህ ሚንስተር ዚሰነዶቜ ማሚጋገጫና ኚዘገባ ጜ/ቀት በቀን 10/3/2002 ዓ/ም በተፈሹመ ዹጂ ኀስ ኀ ጄነራል ትሬድንግ ኃ/ዹተ/ዹግል ማህበር ዚመመስሚቻ ጜሁፍ ይዘው በቀት ቁጥር 2545 ተመዝግቩ ዚሚታወቀው  በ1ኛ ተጠሪ  አማካኝነት በመጭነት  ዹተመዘገበ መሆኑ ተሚጋግጧል፡፡

     

    ሚያዚያ 16 ቀን 2002 ዓ/ም በተካሄደ ዹጂ ኀስ ኀ.ኀጀኔራል ትሬድንግ ኃ/ዹተ/ዹግል ማህበር ለሂሳብ 1ኛ ተጠሪ በማህበሩ ዚዚራሳ቞ውን አክስዮን በብር 240,000.00 /ሁለት መቶ አርባ ሺህ ብር/ ሜጠው ዚተሰራበት መሆኑ በኢፈደሪ ዚፍትህ ሚኒስ቎ር ማስሚጃ ማሚጋገጫ ምዝገባ ጜ/ቀት ማህተም በተሹጋጠ ሰነድ ተሹጋግጧል ጂ. ኀስ ጄኔራል ትሬድንግ ኃ/ዹተ/ ዹግል ማህበር ግንቊት 17 ቀን 2003 ዓ/ም በተፃፈና በሰነዶቜ ማሚጋገጫና መዝገብ ጜ/ቀት በተመዘገበ ዚሜያጭ ውል ይህንኑ ዚቀት ቁጥር 2545 ዹሆነው በብር 240,000.00 /ሁለት መቶ አርባ ሺህ ብር/ ለጣልቃ ገብ ለአሁን 3ኛ ተጠሪ አብዱራህማን አህመድ ዹተሾጠ ስለመሆኑም በጣልቃ ገብ አማካኝነት በቀሹበው ዚጜሁፍ ማስሚጃ ተሹጋግጧ በመሆኑም ይኾው ቀት ኹ1ኛ ተጠሪ እጅ ሙሉ በሙሉ ወጥቶ በጂ ኀስ. ኀ.ተራ ደንብ ኃ/ዹተ/ዹግል ማህበር ተጠቃሎ ተላልፏል ዚተስፋፋውም ዚአመልካቜና 1ኛ ተጠሪ ጋብቻ እንዳይፈርስ ዚፍቺ ጥያቄ ለመቅሚቡ በፊት እና ለፍ/ቀት ዚእግድ ትእዛዝ በፊት ስለመሆኑ በማስሚጃ ተሚጋግጧል፡፡

     

    ዚጋራ ዹሆነውን ንብሚት ያለ ሁለተኛው ተጋቢ ፈቃድ በአንደኛው ተጋቢ አማካኝነት ተላልፎ ዹተገኘ እንደሆነ በአዋጅ ቁጥር 213/92 አንቀፅ 68/ሀ/ እና 69 እንደተደነገገው ፈቅደን ባልሰጠው ተጋቢ ጥያቄ መሰሚት ንብሚቱ ዚተላለፈበት ግዎታ እንዲፈርስ ካልተደሚገ በቀር በተፈጾፀመው ዚንብሚት ማስተላለፍ ስምምነት ውስጥ ተጋቢዎቜ እንደታሰበው ግምት እንደሚሰጡ ተደንግጓል፡፡ በዚህ መሰሚት አመልካቜ በዚህ በመ/ቁ 2545 ዹተደሹገውን ዚሜያጭ ስምምነት  በመቃወም በፍ/ቀት ጥያቄ አቅርበው ያስወሰኑት ዚለም፡፡ ስለሆነም ንብሚቱን ኚእኔ ለማሞሜ ሲል ለኢኀስኀ ትሬድንግ ኃ/ዹተወሰነ ዹግል ማህበር በመውጫ ሰጥቷል ዹፍ/ቀቱን ዕግድ በመጣስ  ሞጊታል በማለት ያቀሚቡት ክርክር ራሱ ቜሎ መቅሚብ ዚነበሚበት ክርክር እንጅ በዚህ አሁን በቀሹበው ክርክር ሊታይ ዚማይቜል ኹመሆኑም በላይ ንብሚቱ ወደ ማህበሩ ዹተዛወሹው በአመልካቜ በኩል ዚፍቺ ጥያቄ ለመቅሚብና ዚዕግድ ትዕዛዝ ኹመተላለፉ በፊት ስለሆነ ዹመ/ቁጥር  2545 ዚሚታወቀው ቀት ዚአመልካቜና ዚተጠሪዎቜ ዚጋራ ሀብት ሳይሆን ጣልቃ ገብ በግዥ ያገኙት ንብሚት ነው በማለት ወስኗል፡፡ እንዲሁም በዘምዘም ባንክ አ/ማህበር በተጠሪዎቜ ስም  ዚአኚሲዮን


    ድርሻ ዚለም፣ በባንክ ስማቜን ዹተቀመጠ ገንዘብ ዹለም በማለት ተጠሪዎቜ ቢኚራኚሩም ፍ/ቀቱ ስላቀሚበው ማስሚጃ ጭምር ዹተሹጋገጠ ሆኖ ተገኝቷል በማለት ተሹጋግጧል ባለው ዚገንዘብ መጠን መሰሚት ዹአሁን አመልካቜ ድርሻ እንዳላ቞ው ገልፆ ዳኝነት ሰጥቶበታል በሌላ በኩል ጋብቻው ፀንቶ በነበሚበት ወቅት ንብሚት በማስተዳደር በኩል ዚፈፀሙት ጉድለት ያለመሆኑ ያለ መሆኑ ተጣርቶ ኹተሹጋገጠ በኋላ ለማ እንዲኚፈላ቞ው ጠይቀዋል፡፡ ይሁን እንጅ ተጋቢዎቜ በጋብቻ቞ው ዘመን ዚጋራ ንብሚታ቞ውን በጋራ እንዲያስተዳድሩ በሕጉ ግምት ዚሚወስድ ሲሆን ይህን ግምት ማፍሚስ ዚሚቻለው አንደኛው ተጋቢ ዹሌለውን መብት ዚሚጎዳ ተግባር ፈፅሞ ስለመገኘቱ ዚማሚጋገጥ ማስሚጃ ዹቀሹበ እንደሆነ በሕጉ አንቀፅ 87 ተደንግጓል 1ኛ ተጠሪ  ንብሚት ሲያስተዳድሩ ፈፀሙ በሚል በማስሚጃ ዹተሹጋገጠና ተለይቶ ዚታወቀ ጉድለት ያልተገኘ በመሆኑ ፍ/ቀቱ ጥያቄውን አልተቀበለውም ዹሚለውን ውሳኔ ሰጥቶበታል፡፡ፍ/ቀቱ ለሰጠው ዳኝነት በምክንያትነት ያሰፈሚውን ሐተታ እና ዹሰጠውን ዚዳኝነት ዓይነት ኹዚህ በላይ ባሰፈሚው አኳኋን በሰጠው ዚፍርድ ክፍል ላይ ኹገለፀው በኋላ በፍርድ መሰሚት ዹተሹጋገጠውንና ሊሚጋገጥ ያልቻለውን ምስክር አስመልክቶ ዚፍርድ ተኚታይ በሆነው ዚውሳኔ ክፍል ላይ

     

    በቂርቆስ ክ/ኹተማ በቀሌ 02/03 ክልል በቀት ቁጥር 297 ተመዝግቩ ዹሚገኘውን ቀት በትግራይ ክልል መቀሌ ኹተማ ዹሚገኘውን ቀት አመልካቜና ተጠሪዎቜ በጋራ ያፈሩት ንብሚቶቜ ስለሆነ ዹክፍፍሉንም መንገድና ስልት ኚመጥቀስ ጋር ሶስቱም እኩል እንዲኚፈሉ በን/ስ/ላፍ/ክፍለ ኹተማ በመ/ቁጥር 2545 ዹግልግል ሀብት ነውፀ

     

    1ኛ ተጠሪ በቮክኖሎጅ ሲስተም ኃ/ዹተ/ዹግ/ማህበር ያላ቞ውን ሞር፣ በፒስ ደልለን ኃ/ዹተ/ዹማህበር ውስጥ ያለው ሞር 2ኛ ተጠሪ በዘምዘም ባንክ አ/ማህበር ያላ቞ው በሁለተኛ ተጠሪ ስም በዳሜን ባንክ ስለ አካባቢ ቅርንጫፍ በ1ኛ ተጠሪ ስም በወጋገን ባንክ ተ/ኃይማኖት ቅርንጫፍ በ1ኛ ተጠሪ ስም በዳሜን ባንክ ስለ አካባቢ ያስቀመጠውን ገንዘብ ኚእነ መጠኑ በመግለፅ ሶስቱም እኩል እንዲካፈሉ በማለት በኮ/መ/ቁ 61875 በቀን 13/10/2004 ዓ.ም ወስኖ ግራ ቀኙን አሰናብቷል፡፡

     

    በዚህ ውሳኔ ዹአሁን አመልካቜ ቅር ተሰኝተው ባቀሚቡት ዚይግባኝ ቅሬታ መነሻ ይግባኝ ሰሚው ኹፍተኛ ፍ/ቀት በኮ/መ/ቁ 125893 ሁሉንም ወገኖቜ ኹክርክር በኋላ

     

    ዚቀት ቁጥር 2545 አስመልክቶ ዹቀሹበውን ጉዳይ በሚመለኚት በዚሁ ቀት ላይ ዚስር ፍ/ቀት ዚካቲት 16/2003 ዓ.ም ዚዕግድ ትዕዛዝ ኚመስጠቱ በፊት ቀቱ በ1ኛ አማካኝነት በመውጫነት ወደ ጅ.ኀስ.ኀ ጀኔራል ትሬድግግ ኃ/ዹተ/ዹግል ማህበር ገብቶ ዹነበሹ እና 1ኛ ተጠሪ በማህበሩ ውስጥ ዚነበራ቞ውን 4127/4/ለ/2002 በቀን 12/9/2002 መተላለፉን ዚሰነዶቜ ማሚጋገጫ ፅ/ቀት ለስር ፍ/ቀት በቀን 20/4/2004 ዓ.ም ኹላኹው ማስሚጃ አሚጋግጧል፡፡ እንዲሁም ዹዚሁ ቀት ስመ-


    ሀብትነት ወደ ጅኀስኀ ጀኔራል ትሬድንግ ኃ/ዹተ/ዹግ/ማህበር በቀን 04/8/2002 በቁጥር ን/ስ/ቀ/05/83/3805/02 ዹተላለፈ ስለመሆኑ ዹን/ስ/ላ/ክ/ኹተማ መሬት አስተደደርና ግንባታ ፅ/ቀት ዚካቲት 14 ቀን 2003 ዓ.ም በተፃፈና ለስር ፍ/ቀት ኹላኹው ሰነድ ተሚጋግጧል፡፡

     

    ቀቱ ወደ ሶስተኛ ወገን በተላለፈበት ጊዜ ግንቊት 1/2002 ዓ.ም ግራ ቀኙ በጋብቻ ውስጥ ዚነበሩ ስለመሆኑ ዚስር ፍ/ቀት ግንቊት 24 ቀን 2002 ዓ.ም ዹሰጠው ዚፍቺ ውሳኔ ያሚጋግጣል፡፡ በመሆኑም ይኜው ንብሚት በጋብቻ ጊዜ ወደ ሶስተኛ ወገን ሲተላለፍ መተላለፉን አላወቀም ነበር ዹሚሉ ሲሆን አሁን ለዚህ ቜሎት ውሉ እንዲፈርስ ስልጣን ባለው ፍ/ቀት ጥያቄ አቅርበው እዚተኚራኚሩ እንደሚገኙ በገለፁት መልኩ ይኜው ውል በማስፈሚስ መብታ቞ውን ኚሚያስኚብሩ በቀር በጠዚቁት ዳኝነት አኳኋን ሊስተናገድ ዚሚቜል አይደለም በማለት ዚስር ፍ/ቀትን ውሳኔ ሲያፀናው በ1ኛ ተጠሪ እና በ2ኛ ተጠሪ ስም ዹሚገኘውን ዚሌር ሀብት መጠንን በሚመለኚት ማህበሮቹ ለስራ ተሰማርተው ያገኙትን ትርፍ ሁሉ አጠቃሎ መወሰን ሲገባው ማህበሮቜ በተቋቋሙበት ጊዜ በተደሹገው መነሻ ይካተታል መጠን ላይ መወሰኑ አግባብ አለመሆኑን እንዲሁም በልዩ ልዩ በባንኮቜ በእነዚሁ ተጠሪዎቜ ስም አንፃር ይገኛል ዚተባለውን ሀብት መጠን አስመልክቶ ፍ/ቀቱ ገንዘብ ስለመኖሩ በጠዚቀበት ጊዜ በባንኮቜ ተቀምጩ ተገኝቷል ዚተባለውን ዚገንዘብ መጠን ሳይሆን በትዳር በነበሩበት ጊዜ አንደኛዉ ወገን ብቻ በማውጣት ለግል ጥቅም ተጠቅሞበታል ኚሚያሰኝ በቀር ለጋራ ጥቅም እንደዋለ አያስቀጥርም በማለት መነሻ ሊሆን ኚሚቜለው ጊዜ ጋር በማስተያዚት በባንኮቜ ካላ቞ው ሂሳብ እንቅስቃሎ  በመነሳት መሠሚት ዚሚገባዉ መሆኑን ጠቅሰን በዚሁ መሠሚት እራሱ ይግባኝ በኚካሜ ፍርድ ቀት ጉዳዮን ተመልክተ ዚገንዘቡን መጠን በፍርዱ ዚውሣኔ ክፍፍል በተገለፀው አኳኋን ኹፍ አድርጎ በሚሻሻል መወሰን ፀ

     

    በሾር ድርሻ ላይ ዹተወሰነውን ዚድርሻ መጠንን ኹላይ በተመለኹተው መሠሚት ኚውሳነ በኃላ ዹክፍፍል ማስሚጃን በሚመለኚት 1ኛ መልሰ ሰጭ በሀብቱም ማህበሮቜ ዹተወሰነላቾውን ዚአክስዮን ድርሻ ለተቻለ እና ተጠሪዎቜ ዚሚስማሙ ኹሆነ በአባልነት እንዲቀጥሉ ይህ ካልተቻለ ተሜጊ ዚሜያጩን ድርሻ ይኹፈላቾው ዚአኚስዮኖቜ አሻሻጭም በንግድ ህግ አንቀጜ 523 እና ተኚታዮቜ ድንጋጌዎቜ እንደዚሁም ዹሰበር ሰሚ ቜሎት በመ/ቁ.57288 በሰጠው ዹህግ ትርጉም መሠሚት ሆኖ ድርሻ቞ው እንዲሰጣ቞ውና እንዲሁም በቀት ቁጥር 2545 ውስጥ/ ዹተሰጠውን ዕቃ በሚመለኚት ቀርቧል በተባለው ዹወንጀል ክስ ምርመራ ውጠት መሠሚት ዹአሁኑ አመልካቜ ጥያቄ ዚማቅርብ መብታ቞ው ዹተጠበቀ መሆኑን ኹዚህ በላይ ኚተገለፁት በቀር ሥማ቞ው በሥር ፍ/ቀቶቜ ዹተሰጠው ውሳኔ ዹፀና መሆኑን ለመግለፅ በሥር ፍ/ቀት ዹተሰጠውን ውሣኔ በማሻሻል ዹወሰነ መሆኑን ኚፍርዱ ግልባጭ ተሚድተናል ፡፡


    ዹአሁን አመልካቜ በዚህ ዹሰበር ሰሚ ቜሎት ሊታሚም ይገባል በማለት ለቅሬታ቞ው መሠሚት ያደሚጉት ዚቀት ቁጥር 2545 ዹሆነው ቀት ዚባልና ሚስት ዚጋራ ሀብት ነው ወይስ ዹአሁን 3ኛ ተጠሪ ዹሚለውን ለይቶ በመወሰን ሚገድፀእንዲሁም በሥር ይግባኝ ሰሚው ፍ/ቀት ውሣኔ ዚተሚጋገጠባ቞ውን ዚአክስዮን ድርሻዎ ዹክፍፍሉን መንገድ በሚመለኚት ዚአክስዮን ድርሻዎቜ በሚገኙበት ማህበር በአባልነት እንድቀጥል በማድሚግ መወሰን ስገባው ማህበሩ ለተስማማ በሚል ተገልፆ ዹህግ መሠሚት ዹለውም ለሚሉት መወሰኑ ነጥቊቜ ላይ ፡፡

     

    ተጠሪዎቜም በበኩላ቞ው ክርክር በሚመለኚታ቞ው ክርኹር አንፃር በሥር ፍ/ቀቶቜ ዹተሰጠው ዳኝነት መሠሚታዊ ዹህግ ስህተት ዚተፈፀመበት አይደለም ዚሚሉበትን ምክንያት በመጥቀስ ተኚራክሚዋል፡፡

     

    እንግዲህ ዚጉዳዮ አነሳስፀዚክርክሩ ይዘትና ዚሥር ፍ/ቀቶቜ በዹደሹጃው ዚሰጡት ዳኝነት ፀዚዚህን ዳኝነት አግባብነት በሚመለኚት ወገኖቜ በዚህ ሰበር ቜሎት ያቀሚቡት ክርክር በይዘት ደሹጃ ኹላይ ኹፍ ሲል ባጭር ባጭሩ ዹተመለኹተው ሲሆን ፀእኛም ጉዳዮን እንደሚኚተለው መርምሹናል ፡፡ ተመልክተናል ፡፡

     

    ጉዳዮን እንደመሚመርነውም በቀት ቁጥር 2545 ዹተመለኹተውን ቀት አስመልኚቶ ዹአሁን አመልካቜ ኚሥር ፍ/ቀት ጀምሮ ለክርክራ቞ው መሠሚት ያደሚጉት ንብሚቱ በሜያጭ ወደ አሁን 3ኛ ተጠሪ ዹተላለፈው ፍ/ቀቱ በዚሁ ንብሚት ላይ ዕግድ ኚሰጡበት በኃላ ዹፍ/ቀቱ ዕግድ ተጥሶ ስለሆነ ዚሜያጭ ተግባሩ ዋጋ አልባ ስለሆነ ሊፈርስ ይገባል ዹሚለውን አንደኛው ዹክርክር ነጥብ ሲሆን ዹዚህኑ ክርክር አግባብነት ለዚሁ ጉዳዮ በሥር ፍ/ቀቶቜ በነበሹው ዹክርክር ሂደት በማስሚጃ ኹተሹጋገጠው ዚፍሬ ነገር ጉዳይ በመነሳት ተመልክተናል ፡፡

     

    ዹአሁን አመልካቜ ለዚህ ዹሰበር ጉዳይ መነሻ ዹሆነውን ክስ ኚቀሚቡ በኃላ ዚክርክሩ ውጀት እስክታወቅ በሚል ይኜው ቀት በማናቾውም መንገድ ቢሆን ወደ ሶስተኛ ወገን እንዳይተላለፍ ዚዕግድ ትእዛዝ ዚሰጡት ዚካቲት 16 ቀን 2003 ዓ.ም መሆኑና ይኜው ቀት በአሁን 1ኛ ተጠሪ አማካኝነት በዓይነት በመወጫነት ወደ ጂ.ኀስ.ኀ ጀኔራል ትሬድንግ ኃ/ዹተ/ዹግ/ማህበር ዚገባውና ስመ ሀብትነቱም ወደ ዚሁ ማህበር ስም ዹተላለፈው ይኜው ዚወሰነበት ዚዕግድ ትእዛዝ ኚመስጠቱ በፊት ስለመሆኑ በሥር ፍ/ቀት ዹተሹጋገጠ ጉዳይ ነው፡፡ ዚአንድ ንብሚት ባለሀብት ማን ነው ዹሚለው ዹሚወሰነው ደግሞ ንብሚት ኚአንዱ ወደ ሌላው ለማስተላለፍ ዚሚያስቜለው እንደ ሜያጭ ስጊታ ወዘተ ዚመሳሰሉት ህጋዊ ተግባሮቜ በህግ ፊት በሚፀና አኳኋን ተፈፅመው እንደሆነ እና በዚሁ አኳኋን በተፈፀመው ህጋዊ ተግባር ዚተነሣ በንብሚቱ ላይ ዚባለቀትነት መብት ያገኘ ሰው ንብሚቱን ካስተላለፈዉ ተፈጥሯዊም ሆነ ዹህግ ሰው ባሻገር ማናቾውንም 3ኛ ወገን ለመመለስ ዚሚያስቜለውን ዚስመ ሀብት ዝውውር ሥርዓት ሁሉ ታኚናውኖ እንደሆነ በፍ/ብ/ህግ ቁጥር


    1678 ፣1731፣1184፣1195 ተደንግጓል፡፡ አሁን ዚተያዘውን ጉዳይ ኚእነዚህ ድንጋጌዎቜ አንፃር ስነዚው ክርክር ያስነሰው ንብሚት በ1ኛ ተጠሪ እና ጀ አስ ኀ ጀኔራል ትሬዲንግ መካኚል በተደሹገ ስምምነት መሠሚት ይኜው ንብሚት በዓይነት በመወሰኑ ወደ ኚማህበሩ ገብቶፀ ማህበሩ በዚሁ ንብነት ላይ መብትና ግዎታ ያቋቋመ ሲሆን ኹዚሁ ንብሚት ወደ ማህበሩ መግበት ዹተነሰ ለአስተላለፈውም ግዎታ ፈጥሮለታል ይህ በህግ ዹተፈቀደ ንብሚት ሊተላለፍ ዚሚቜለበት አንዱ ህጋዊ ተግበር ሲሆን ማህበሩ በዚሁ ንብሚት ላይ ዚእኔ በይ በመጣ ለመመለስ ዋስትና ዹሆነውን ዚስመ ሀብት ዝውውር ሥርዓት ሁሉ ፈፅሟ፡፡ በዚህም መሠሚት ዹዚሁ ንብሚት ዚበላቀትነት መብት ያለው ይኜው ማህበር እንጂ ሌላ ማናቾውም ወገን ሊሆን አይቜልም ይህን በንብሚት ላይ ያለን ዚበለሀብትነት መብት ማህበሩ ያቋቋመው ፍ/ቀቱ በንብሚቱ ላይ ዚዕግድ ትዕዛዝ ኚመስጠቱ በፊት ነው ኹዚህ በንብሚቱ ላይ ዚበለቀትነት መብት ኹቋቋመ በኃላ በዚህ በህግ ኹቋቋመው ላይ ዚበለቀትናት መብቱ ተጠብቆም በንብሚቱ ላይ ዹማዘዝ ወደ ሌላ 3ኛ ወገን ዚመስተልለፍ መብት ያለው ሲሆን ሌላ ማዹናቾውም 3ኛ ወገን ይህንኑ ንብሚት ለሚመለኚት ኚመህበሩ ጋር በሚያደሚገው ህጋዊ ተግበር ወደ እራሱ ያዛወሚው ኹሆነ ንብሚቱን ለማዘወር መብትና ስልጣን ኹለው ወገን ያገኘ ነው ወይስ አይደለም ዹሚለውን ለመለዚት ማህበር ንብሚቱን በሞጠበት ጊዜ በንብሚቱ ላይ ዹተመለኹተውን ስመ ሀብትነት ምዝገባ ዹሚኹተል እንጂ 3ኛ ወገን ኚማህበሩ ጋር ግብይት ዚፈፀመበት ጊዜ ሊሆን አይቜልም ኹዚህ በላይ ንብሚት ኹንደኛው ወገን ወደ ሌላው ሊተላለፍ ዚሚቜልበትን መንገድ በሚመለኚት በተጠቀሱት ድንጋጌዎቜ ዚተቀመጡት ሁለት ቋሚ መሟያዎቜ ማናቾውም በንብሚት ላይ ሊኖር ዚሚቜለው ግብዓት በህግ ዋስትና ተሰጥቶት በህ/ሰብ ደሹጃ ያለስጋት ዹሠለጠ ኢኮኒሚያዊ ግንኙት ለመፍጠር እንዲያስቜል ነው፡፡ ኹዚህ አንፃር ዹአሁን አመልካቜ ዹፍ/ቀቱ ዚዕግድ ትዕዛዝ ኹተለለፈ በኃላ 3ኛው ተጠሪ ኚማህበሩ ጋር ዚሜያጭ ውል ያደሚገበትን ጊዜ ተንተርሰው ዚሚያቀሚቡት ክርክር ዹህግ መሠሚት ያለው ሆኖ አላገኘነውም ፡፡

     

    ኹዚህም በቀር ዚማይንቀሳቀስ ንብሚት በዓይነት ለመውጫ ወደ አክሲሆን ማህበር ወይም ወደ ኩባንያ ስለመዘወሩ በመመስሚቻ ፅሑፍ ሰፍሮና በዚህ መስሚጃ መዝገብ ጜ/ቀት ተመዝግቩ በማንቀሰቀስ ንብሚት በመዝገብ ውስጥ መመዝገቡ ኹተሹጋገጠ ዹ3ኛ ወገኖቜን ላይ ለመመለስ ዚሚያስቜለው ሥርዓት መሟለቱን እንደሚያመለክት ይህ ለሰበር ሰሚ ቜሎት ኹዚህ ቀርቩ ተመሰሰይ በሆነው በሰበር መ/ቁ.. 27869 ትርጉም ዚሰጠበት ጉዳይ በመሆኑም ጭምር ኚዕግድ ትዕዛዝ ጋር በተያዚዘ ዹአሁን አመልካቜ ዚሚያቀርብበት ክርክር በስር ፍ/ቀቶቜ ዹተሰጠው ዳኝነት መሠሹተዊ ዹህግ ስህተት ዚተፈፀመበት መሆኑን ዚሚያመለክት ህጋዊ መሰሚት ዹለው ክርክር አይደለም ሌላውና ይህንኑ በቀት ቁጥር 2545 ዹተመለኹተውን ቀት  አስመልክቶ ዹአሁን አመልካቜ ያቀሚቡት ክርክር በዋጅ ቁጥር 2/3/92 ስለጋራ ዹበልና ሚስት ሀብት አስተዳደርና ጥበቃ በህጉ ዹተቀመጠውን  ዚተጋቢዎቜ ዚጋራ ስምምነትን አስፈላጊነት በመጥቀስ ነው፡፡


    ዚጋራ ሃብት ዹሆነን ንብሚት አንደኛው ተጋቢ ያለ ሌላኛው ተጋቢ ስምምነት ለሌላ ሶስተኛ ወገን በሜያጭ ማስተላለፍ እንደማይቜል በዚሁ ዚቀተሰብ ሕግ አንቀጜ 68 ዹተደነገገ ሲሆንፀ ይህ ድንጋጌ በይዘቱ ዚጋራ በሆነ ንብሚት ላይ ተጋቢዎቜ እኩል መብት ያላ቞ው መሆኑን በህገ- መንግስቱ አንቀጜ 34(1) ዹተመለኹተውን ህገ-መግስታዊ ድንጋጌ ተኚትሎ ዹተደነገገ ሲሆንፀ በሌላ በኩል በአገር በማህበሚሰብ ውስጥ ንብሚትን አስመልክቶ ዹሚደሹገው ግብይት ያለማነቆ በሰለጠ አኳኋን እንዲፈጞም ካልተደሚገ በአገር ዚኢኮኖሚ እንቅስቃሎ ላይ ሊያደርስ ዚሚቜለውን እንቅፋት በማዚት ይህ ኹላይ ዹተመኹተው ዚጋራ ስምምነት አስፈላጊነት በሁኔታ ላይ እንዲመሚኮዝ በማስፈለጉ ተኚታይ በሆነው አንቀጜ 69 እንደተመለኚተው አንደኛው ተጋቢ ያለፈቃዱ ንብሚቱ በአንደኛው ተጋቢ ብቻ መሞጡን በተሚዳ ጊዜ ይህ ዚሜያጭ ተግባር በህጉ ዹተሰጠውን መብት ዚጣሰ መሆኑን መነሻ አድርጎ በክስ አማካኝነት ማስፈሚስ እንደሚቻልፀ ይህንኑ ዚማስፈሚስ ተግባሩን ካልተጠቀመፀ ወይም በህጉ በተቀመጠው ዹጊዜ ገደብ ዚማስፈሚስ ጥያቄው ስልጣን ባለው ፍ/ቀት ካልቀሚበ ግን አንደኛው ተጋቢ ብቻውን ዹፈጾመው ህጋዊ ተግባር እንደጞና እንደሚቀር እንጂ ዚጋራ ስምምነት ባለመኖሩ ምክንያት ብቻ ንብሚቱ ዚተላለፈበትን ግብይት ወይም ዚሜያጭ ውል በዘፈቀደ በማናቾውም ጊዜ መቃወም እንደማይቻል ተደንግጓል፡፡ ስለሆነም ዚስር ፍ/ቀቶቜ በዚህ ሚገድ ዚሰጡት ዳኝነት ዹህጉን ትክክለኛ አፈጻጞም ዹተኹተለ እንጂ መሰሚታዊ ዹሕግ ስህተት ዹተፈጾመ አይደለም፡፡

     

    ዹአሁን አመልካቜም ይህንኑ ተገንዝበው ክርክራ቞ው በይግባኝ ደሹጃ ለደሚሰበት ጊዜ በዚሁ ስርዓት መሰሚት በንብሚት ላይ ያላ቞ውን መብታ቞ውን ለማስኚበር ስልጣን ባለው ፍ/ቀት ክስ አቅርበው በክርክር ላይ ዹሚገኙ መሆኑን ዚገለጹ በመሆኑና ይህ ቜሎም ለትክክለኛ ፍርድ አሰጣጥ ይህንኑ ዚተባለውን በመጀመሪያ ደሹጃ ፍ/ቀት ዹቀሹበውን ዚኮ/መ/ቁ. 194776 ዹሆነውን መዝገብም አስቀርበን እንደተመኚትነው ጥያቄውን በዚያው አግባብ ማቅሚባ቞ውን ተገንዝበናል፡፡ ይኾው ፍ/ቀትም ጉዳዩን ለጊዜው ዹዘጋው ዚፌዎራል ይግባኝ ሰሚው ፍ/ቀት በኮ/መ/ቁ. 125895 ዚቀሚበለትን ዚይግባኝ ጉዳይ መርምሮ ዚመጚሚሻ ዳኝነት እስኪሰጥበት ጊዜ  ድሚስ በማገዱ ምክንያት በመሆኑና ይግባኝ ሰሚው ፍ/ቀት በጉዳዩ ላይ ዚመጚሚሻ ዳኝነት ዚሰጠበት ጉዳይ ስለሆነ ዚስር ፍ/ቀቶቜ በፍርዳ቞ው ላይ እንደገለጹት መብታ቞ውን ኚሚያስኚብሩ በቀር በዚህ ዚጋራ ንብሚት መሆኑ ተሹጋግጩ ዚጋራ ሃብትን ለማኹፋፈል እንዲቻል በቀሹበው መዝገብ ላይ ወደ ሶስተኛ ወገን በሜያጭ አማካኝነት ተላልፎ ዚባልና ሚስት ዚጋራ ሃብት መሆኑ ያልተሚጋገጠውን ዚቀት ቁጥር 2545 እንደጋራ ሃብት ሊቆጠር ይገባል በማለት ዚሚያቀ ርቡት ክርክር ተቀባይነት ያለውም አይደለም፡፡

     

    ሌላውና ለዚህ ዹሰበር ጉዳይ ዹክርክር ምክንያት ዹሆነው ለአሁን አመልካቜ ይግባኝ ሰሚ ኹፍተኛው  ፍ/ቀት  አሻሜሎ  በወሰነላቾው  ዚአክሲዮን  ሌር  ድርሻ  ላይ  ያላ቞ውን     ሀብት


    ዚሚያገኙበትን ተጠቃሚ ዚሚሆንቚትን መንገድ ይግባኝ ሰሚው ፍ/ቀት ዚሚስማማ ኹሆነ በአባልነት እንዲቀጥሉ ይህ ካልሆነም ተሜጊ ዚሞያጭ ድርሻ እንዲያገኙ በማለት በንግድ ህግ ቁጥር 523 እና ተኚታዮቹ ዹተመለኹተውን መሠሚት በማድሚግና በሰበር ሰሚው ቜሎት በሰበር መ/ቁ.57288 ዹተሰጠውን ትዕዛዝ በመኹተል ዹሰጠውን ዳኝነት አግባብነቱን አስመልክቶ ግራ ቀኙ ክርክር ያደሚጉበት ጉዳይ ነው፡፡

     

    ይህንንም ጉዳይ እንደተመለኚትነው በማናቾውም ምክንያት በፍ/ቀት በሚሰጥ  ፍርድ ዹሚሹጋገጠው መብት ኚተብ ወይም ኹውል ዹመነጹውን መብት መኖርና አለመኖር አስመልክቶ እንዲህጉ አነጋገር ለማስሚዳት ዹቀሹበውን ክርክርና ክርክሩን አነጋገር ለማስሚዳት ዹቀሹበውን ክርክርና ክርክርን ለማስሚዳት ዹቀሹበውን መብት ወደ ተግባር ይህንኑ ኹህግ እንዲያስቜል ለመብት ምንጭ ዹሆነውን ህግ መሠሚት በማድሚግ ነው፡፡

     

    ኹዚህም አንፃር ጉዳዩን አግባብነት ካለው ህግ ጋር ተገናዝቩ ሊታይ ዚሚገባው ነው፡፡

     

    አግባብነት ካላ቞ው ህጎቜ አንዱ ይኾው ዚአክቢዮን ድርሻ ግራ ቀኙ በጋብቻ ዘን በነበሩበት ጊዜ ዚተፈራ ዚጋራ ሀብት እንደመሆኑ መጠን በሀብቱ ዚባለእኩልነት ድርሻ቞ውን ዹሚቃሹጋግጠው አዋጅ ቁጥር 213/92 አንቀጜ 62 አንዱ ሲሆን እንዲሁም ኹዚሁ ዚጋራ ሀብት ነው፡፡ ኚተባለው ዚሀብት ዓይነት አንፃር ሲታይ ደግሞ ዹዚህ ዚጋራ ሀብት ዹክፍፍል ሁኔታ ዚሀብቱን ጉዳይ ምክንያት በማድሚግ በሚደነግገው በንግድ ህጉ አንቀጜ 523 ዹተመለኹተው ድንጋጌ ደግሞ ሌላው ነው፡፡ ስለሆነም ዹዚህኑ ክፍፍል ሥርዓት ዚሚደሚግበትን መንገድ በሚመለኚት ዚሥር ይግባኝ ሰሚው ፍ/ቀት በንግድ ህጉ አንቀጜ 523 ሥር ዹተመለኹተውን ድንጋጌ መሠሚት ማድሚግ ዚሚያነቀፍ አይደለም፡፡ ሆኖም ይህንኑ ድንጋጌ እንደሙሉ ይዘቱ አይነት ተፈፃሚ በማድሚግ ስለሆነም ዹአሁኑ አመልካቜ በፍርድ በተሹጋገጠላቾው ዚአክሲዮን ድርሻ ቫት መብት ላይ ኚንግድ ህጉ አንቀጜ 523 አንፃር አዚቶ መብቱን ለማሚጋገጥ መነሻ ለሆኑ ኚሚገባ቞ው ዹህጉ ክልሎቜ መካኚል በንግድ ህጉ አንቀጜ 523/2/ እንደተመለኚተው ዚአክሲዮን ማህበር መመሥሚቻ ፅሑፍ ዚይዙቱ ዹአሁን አመልካቜ በማህበሩ አባልነት ተካተው በአባልነት ይህንኑ ለፍርድ በተሚጋገጡባ቞ው ዚአክሲዮን ድርሻ ሀብት መገልገል ዚሚቻሉ መሆኑንና አለመሆኑን አስመልክቶ ምን እንደሚል ኚመመስሚቻ ፅሑፍ ጋር አገናዝቩ ኚታዚ በኋላ ሊታይ ዚሚገባው እንጂ ሆና እያለ ይግባኝ ሰሚው ፍ/ቀት ዹሰጠው ዳኝነት በዚህ ሚገድ ዚተባለ ሆኖ አላገኘነውም ስለሆነም በዚሁ ዚነግድ ህግ ቁጥር 523/2/ ድንጋጌ ተትክኚለኛ አፈፃፀሙን ተኚትሎ ፍርድ በመስጠት  ሚገድ ዚታዚው ጉድለት ሊታሚም ዚሚገባው ሆኖ አግኝተነዋል፡፡

     

    በዚህ ሁሉ ምክንያት ዹሚኹተለውን ውሣኔ ሰጥተናል፡


     ው ሣ ኔ

     

    1. ዚፌዎራል ዚመጀመሪያ ደሹጃ ፍርድ ቀት በኮ/መ/ቁ.61875በቀን 13/10/2004 ዓ5ም ዹሰጠውን ፍርድ እንዲሁም ይግባኝ ሰሚው ኹፍተኛ ፍ/ቀት በኮ/መ/ቁ12559 ሰኔ 30 ቀን 2006 ዓ.ም ዹሰጠውን ፍርድ በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕ/ቁ. 325/1/ መሠሚት አሻሜለን ወስነናል፡፡

    2. በን/ስ/ላ/ኹተማ ወሚዳ 03 ክልል ውስጥ በመ/ቁጥር 2545 ተመዝገቩ ዚሚታወቀው  ቀት ላይ ዚባለቀትነት መብት ያለው ዹአሁን 3ኛ ተጠሪ አቶ ሐገስ አብዱራህማን ናቾው መባሉ በአግባቡ ነው ብለናል፡፡

    3. ለአሁን አመልካቜ በፍርድ በተሚጋገጡላ቞ው ዚአክሲዮን ድርሻና መጠን ላይ ባላዠው ዚሀብት መብት ላይ መገልገል ዚሚቻልበት ማበህበሩ አባልነት ተካተው በአባልነት ነው ወይስ በአባልነት መገልገሉ ዚሚቻሉበት ህጋዊ ምክንያት ታይቶ በሐራጁ ተሜጊ ይህንኑ ሀብት እንደያገኙት ነው?ዚሚባለው ጭብጥ ኚማህበሩ መመስሚቻ ፅሑፍ ይዘት እና ኚንግድ ህጉ አንቀጜ 523/2/ አንፃር ታይቶ ይወሰልን ዘንድ ብቻ መዝገቡን በፍ/ብ/ሥ/ሥ/ቁ.343/1/ መሠሚት ወደ ሥር ፈ/ቀት መልሰናል፡፡

    4. ዹዚህ ክርኹር ውጀት እሰኪታወቅ ድሚስ በሚል በዚህ ዚስር መዝገብ ቁጥር 103721 ተሰጥቶ ዹነበሹው ዚዕግድ ትዕዛዝ ተነስቷል ይፃፍ፡፡

    5. ዹዚህ ዹሰበር ክርክር ጉዳይ ስላስኚተው ወጪና ኪሣራ ግራ ቀኙ ዚዚራሳ቞ው ይቻሉ፡፡ ብለናል፡፡

    መዝገቡ ተዘግቷል ወደ መዝገብ ቀት መልሰናል፡፡

    ዚማይነበብ ዚአምስት ዳኞቜ ፊርማ አለበት፡፡

     

     

    መ/ተ

  • አንድ ጋብቻ ሲፈርስ ንብሚት ክፍፍልን በሚመለኚት በእርቅ ውል ስምምነት በሜማግሌ ዹተደሹገው እርቅ በፍ/ቀት ተመዝግቩ ኹተዘጋ በኋላ እንደገና እንደ ባልና ሚስት አብሚን እዚኖርን ስለነበር በድጋሚ ዚንብሚት ክፍፍል ይደሹግ ዹሚል ጥያቄ አግባብነት ያለው ስላለመሆኑ፣

     

    ዹሰ/መ/ቁ. 105054

    ታህሳስ 22 ቀን 2008ዓ/ም

    ዳኞቜ፡- ተሻገር ገ/ስላሎ

     

    ሙስጠፋ  አህመድ ተፈሪ ገብሩ

    ሞምሱ ሲርጋጋ አብርሃ መሰለ

    አመልካቜ፡- ወ/ሮ ጌጀ እጅጉ -ቀርበዋል ተጠሪ፡-አቶ ብርሃኑ ተሰማ   -ቀርቧል

    መዝገቡን መርምሹን ዹሚኹተለውን ፍርድ ሰጥተናል፡፡

     

     ፍ ር ድ

     

    ጉዳዩ ዚባልና ሚስት አፈፃፀም ዚሚመለኚት ነው፡፡ ክርክሩ ዹተጀመሹው በሌሙና ቢልቢሎ ወሚዳ ፍርድ ቀት ተጠሪ ባቀሚቡት ዹአፈፃፀም ክስ ነው፡፡ ዚአቀቱታውን ይዘትም ባጭሩ በመ/ቁ.343/96 በቀን 21/8/1996 ዓ/ም ዹነበሹው ጋብቻ ሲፈርስ ንብሚት ክፍፍል በሚመለኚት በእርቅ ውል ስምምነት በሜማግሌ ዹተደሹገው እርቅ በፍርድ ቀት ተመዝግቩ ተዘግተዋል፡፡ በዚሁ መሰሚትም አንድ ወፍጮ ቀትፀ አንድ ዚዘይት መጭመቂያ ቀት እና አንድ ፒፒሻ ሜጉጥ ዚተጠሪው እንደሆነ ፍርድ ቀት በውሳኔው አሚጋግጠዋል፡፡ ኚውሳኔ በኃላ ታርቀን በባልና ሚስት ሆነን ስንኖር ዚዲገሉና ጢጆ ወሚዳ ፍርድ ቀት መ/ቁ.19963 በቀን 9/8/ 2005ዓ/ም እና ዚአርሲ ዞን ኹፍተኛ ፍርድ ቀት በመ/ቁ.6054 በቀን 19/10/05ዓ/ም በመ/ቁ. 343/96 በሆነው መዝገብ ላይ ዹተሰጠ ዚንብሚት ክፍፍል እንዳይነካ ሲል ተወስነዋል፡፡ ስለዚህ ዚወፍጮ ቀት ዹነበሹው አሁን ዚእንጚት መሰንጠቂያ ዹሆነው እና ዚዘይት መጭመቂያ ቀት ስም ይዛወርልኝ ፒፒሻ ሜጉጥ ታስሚክበኝ ወይም ግምቱ 26,000 ብር እንዲኚፈለኝ ሲሉ አፈፃፀም መጠዹቃቾውን ዚሚያሳይ ነው፡፡ ዹአሁኑ አመልካቜም በሰጡት መልስ በ1996 ዓ/ም ባልና ሚስት መሆናቜን ዚማይካድ እውነት ነው፡፡ ትዳር ሲፈርስ ለኔ ዹተሰጠኝ ዚያዝኩት እንጂ ዚተጠሪ አይደለም፡፡ ያልተወሰነበት ዚሚፈፅምበት ነገር ዚለም፡፡ በእጄ ዹሌለውን ነገር ለመፈፀም አልገደድም፡፡ ጋብቻ ኹፈሹሰ ዚሰራሁት በስሜ ካርታ አውጥቌ ዚሚሰራበት ነው በማለት መልሳ቞ውን አቅርበዋል፡፡


    ዚስር ፍርድ ቀትም ዚግራቀኙን ማስሚጃ በመመዘን በውላቾው መሰሚት መፈፀም አለበት በማለት ዚዘይት መጚመቂያና ዚወፍጮ ቀት ዹነበሹ ወደ እንጚት መሰንጠቂያ ዹተቀዹሹው ወደ ተጠሪ ስም እንዲዛወር እና ሜጉጥ እንዲያስሚክቡ ትእዛዝ ሰጥተዋል፡፡

     

    በዚሁ ትእዛዝ ላይ ኹአሁኑ አመልካቜ ይግባኝ ዚቀሚበለት ዚአርሲ ዞን ኹፍተኛ ፍርድ ቀትም በሜጉጥ ዹተሰጠው ትእዛዝ በማሻሻል በሌሎቹ ንብሚቶቜ ላይ ዚስር ፍርድ ቀት በማፅናት ትእዛዝ ሰጥተዋል፡፡ በመቀጠል ለኊሮሚያ ጠ/ፍ/ቀት ይግባኝ ሰሚ ቜሎት ቅሬታ በአመልካቜ በመቅሚቡ ዚግራ ቀኙ ክርክር ኹሰማ በኃላ ዚዘይት መጭመቂያ በተመለኹተ ዹተሰጠው ትእዛዝ በማፅናትፀ ወፍጮ ቀት ዹነበሹው ወደ እንጚት መሰንጠቂያ ቀቱ ዚተጠሪ ነው፡፡ ነገር ግን ወደ እንጚት ድርጅት ሲቀዚር ማሜኖቹና መሳሪያዎቹ ዚተገዙት እንደ ባልና ሚስት በአንድ ቀት  በሚኖርበት ጊዜ ስለሆነ ማሜኖቹና ዕቃዎቹ በባለሙያ ተገምቶ ግምቱ ወይም በጚሚታ በመሞጥ እኩል እንዲካፈሉ በማለት በመሻሻል ውሳኔ ሰጥተዋል፡፡ ዹሰበር አቀቱታ ዚቀሚበለት ዹክልሉ ሰበር ሰሚ ቜሎት ዹተፈፀመ መሰሚታዊ ዹሕግ ስሕተት ዚለበትም ሲል አቀቱታው ሳይቀበለው በትእዛዝ ዘግቶታል፡፡

     

    ዹሰበር አቀቱታ ዹቀሹበውም ዚስር ፍርድ ቀቶቜ በጉዳዩ ላይ ዚሰጡት ዳኝነት መሰሚታዊ ዹሕግ ስሕተት ዚተፈጞመበት ስለሆነ ሊታሚም ይገባል በማለት ነው፡፡ አቀቱታው  በሰበር ቜሎት እንዲታይ ዚተያዘው ጭብጥ ዚእንጚት ድርጅት ዹተቋቋመው ወፍጮ ቀት ዹነበሹው በ1996ዓ/ም በስምምነት ኚተካፈሉ በኃላ እንደገና እንደባልና ሚስት አብሚው ሲኖሩ መሆኑ ባልተካደበት በተደሹገው ዚንብሚት ኹፍፍል ስምምነት መሰሚት ቀቱ ዚተጠሪ ነው ተብሏል በሚል መነሻ አመልካቜ በአፈፃፀም መዝገብ ላይ ለተጠሪ እንድትለቅ ዹተሰጠው ትእዛዝ ህጋዊ ዹክርክር አካሄድና አመራርን ዹተኹተለ መሆን አለመሆኑን ለመመርመር ነው፡፡ አቀቱታው ተመርምሮ ለሰበር ቜሎቱ ሊታይ ዚሚገባ ነው ተብሎ በመታዘዙ ለተጠሪ ጥሪ ተደርጎላቾው መልሳ቞ውን ሰጥተዋል፡፡ አመልካቜም ዚመልስ መልስ አቅርበዋል፡፡

     

    ዚጉዳዩ አመጣጥ ባጭሩ ኹላይ እንደተገለፀው ሲሆን በዚህ መሰሚትም በጭብጥነት በተያዘው ነጥብ ኚግራ ቀኝ ወገኖቜ ክርክርፀ አቀቱታ ኚቀሚበበት ውሳኔ እና ኹሕጉ ጋር አገናዝበን መርምሚናል፡፡ ጉዳዩ ዹአፈፃፀም ኚስ ስለሆነ በዋናው ጉዳይ ዹተሰጠው ውሳኔ መሰሚት እንዲፈፀም መደሹግ አለበት፡፡ በግራ ቀኙ ዚተማመኑበት ጉዳይ በመሐኹላቾው ዹነበሹው ጋብቻ በፍቺ ሲፈርስ ዚንብሚት ክፍፍል በስምምነት በማድሚግ በፍርድ ቀት ተቀባይነት አግኝቶ ዹፀደቀ ነው፡፡ ኚፍቺ በኃላም እንደባልና ሚስት አብሚው እዚኖሩ እንደነበር በስር ፍርድ ቀቶቜ ያሚጋገጡት ፍሬ ነገር ነው፡፡ በ2005ዓ/ም ዹአሁኑ ተጠሪ ዚፍቺ ክስ ለፍርድ ቀት አቅርበው ነገር ግን ጋብቻ ዹለም ግንኙታ቞ው


    እንደ ባልና ሚስት አብሚው እንደሚኖሩ ሰዎቜ ዚሚባል ነው፡፡ በዚህ ጊዜ አብሚው ያፈሩት ንብሚት ዚጋራ እንዲሆንና በ1996 ዓ/ም ዹተደሹገው ክፍፍል ዹተጠበቀ መሆኑን ውሳኔ ተሰጥተዋል፡፡

     

    ውሳኔው ይህ ኹሆነ አፈፃፀሙን ዚዘይት መጭመቂያና ዚወፍጮ ቀት ለተጠሪ ዹደሹሰው መሆኑን አመልካቜም ዚራስዋ ድርሻ እንደያዘቜ ኚስር መዝገብ መገንዘብ ይቻላል፡፡ ኚፍቺ በኃላ አብሚው መኖር ኚጀመሩ ያፈሩት ንብሚት መኖር አለመኖሩን ለማጣራትና ማስሚጃ ዹመመዘን ስልጣን ባለ቞ው ዚስር ፍርድ ቀቶቜ ያሚጋገጡት ወፍጮ ቀት ዹነበሹው ወደ ዚእንጚት ድርጅት ሲቀዚር ዚተለያዩ ማሜኖቜና ዕቃዎቜ አብሚው ያፈሯ቞ው እንደሆነ ነው፡፡ በዚህ መሰሚትም አብሚው ያፈሩት ማሜኖቜና እቃዎቜ እኩል አንዲካፈሉፀ ቀቱ ደግሞ ለተጠሪ እንዲሆን በማለት ዹተሰጠው ውሳኔ መሰሚታዊ ዹሕግ ስሕተት ያለበት ሆኖ አልተገኘም፡፡ በዚሁ መሰሚትም ዹሚኹተለውን ውሳኔ ሰጥተናል፡፡

     

     ው ሳ ኔ

     

    1. ዚኊሮሚያ ጠ/ ፍ/ ቀት ይግባኝ ሰሚ ቜሎት በመ/ቁ.181913 በቀን 12/10/2006 ዓ/ም ዚስር

     

    ፍርድ ቀቶቜ ውሳኔ በማሻሻል ሰጠው ውሳኔ እና ዚኊሮሚያ ጠ/ፍ/ቀት ሰበር ሰሚ ቜሎት በመ/ቁ.185727 በቀን 22/11/2006ዓ/ም ዹሰጠው ትእዛዝ በፍ/ብ/ስ/ስ/ሕ/ቁ.348/1/ መሰሚት አጜንተናል፡፡

     

    2. በዚህ ቜሎት ተሰጥቶ ዹነበሹው ዚእግድ ትእዛዝ ተነሰተዋል ለሚመለኹተው አካል ይተላለፍ፡፡

     

    3. በዚህ ቜሎት ለተደሹገው ወጭና ኪሳራ ዚግራ ቀኙ ወገኖቜ ዚዚራሳ቞ውን ይቻሉ፡፡ መዝገብ ተዘግተዋልፀ ወደ መዝገብ ቀት ይመለስ፡፡

     

     

    ዚማይነበብ ዚአምስት ዳኞቜ ፊርማ አለበት፡፡

     

     

    መ/ይ

  • ዚጋብቻ ዚምስክር ወሚቀት ተገቢውን ስርዓት ተኚትሎ ዹተሰጠ አይደለም ተብሎ መሰሹዝ ጋብቻ አልነበሹም ለማለት ዚሚያስቜል ስላለመሆኑ፣

    Download Cassation Decision

  • ባል ወይም ሚስት ዚጡሚታ አበል ተጠቃሚ ሆነው ባሉበት ፍቺ ቢኚሰት ዚጡሚታ መብት ተጠቃሚ ዹሆነው ባል ወይም ሚስት ዚጡሚታ አበል ለባል ወይም ለሚስት ሊያካፍል ዚሚገባ ስላለመሆኑ ፣ ዚመንግስት ሠራተኞቜ ጡሚታ አዋጅ ቁጥር 345/95 አንቀጜ 35

    Download Cassation Decision

  • ዹገጠር መሬት እንደሌላው ንብሚት በመቁጠር ኚቀተሰብ ህጉ አንጻር ዚሚታይ ስላለመሆኑ ፣ በአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ዚመሬት ይዞታ ማሚጋገጫ ደብተር በአንድ ተጋቢ ስም ተዘጋጅቶ ኹተሰጠ በኋላ ጋብቻ ቢፈፀምና ተጋቢዎቹ መሬቱን ዚጋራ ለማድሚግ ሊስማሙ ዚሚቜሉ ስለመሆኑ፣ ዚአማራ ክልል ዹገጠር መሬት አጠቃቀም አዋጅ ቁ. 133/1999 አንቀጜ 24/3/ ደንብ ቁ. 151/1999 አንቀጜ 20/6/

    Download Cassation Decision

  • በአባት በኩል ያለን መወለድ መቃወም ዚሚቻለው ዹልጁ አባት ነው ተብሎ በህግ ግምት ዹሚሰጠው ሰው እሱ ዹሞተ ወይም ቜሎታ ያጣ እንደሆነ ኚተወላጆቹ አንዱ ዚመካድ ክስ በማቅሚብ መቃወም ዚሚቜል ስለመሆኑ፣ ዚተሻሻለው ዚቀተሰብ ህግ አዋጅ ቁ. 213/1992/አንቀጜ 167፣174 እና 179

    Download Cassation Decision

  • እድሜው ያልደሚሰ ልጅ ዚማይንቀሳቀስ ንብሚት ለመሞጥ ዚሚያስቜል ዚሞግዚት ስልጣን ይሰጠኝ ጥያቄ ፍ/ቀቶቜ ዹህፃንን መብትና ድህንነት ቅድሚያ እንዲሰጠው በማደሹግ ሲወሰኑ ኹዚሁ ጋር ተያይዞ ዹቀሹበውን መሰሚታዊ ጥያቄ እና አማራጭ መፍትሔ መኖሩን አለመኖሩን በማጣራት መወሰን ያለበት ሰለመሆኑ ዚኢ.ፌ.ዮ.ሪ መንግሰት 36 (2) ፣ ፍ/ብ/ሕ/ቁ 280 እና 289(1) ዚቀተሰብ ህግ አዋጅ 213/1992 አንቀፅ 43

    Download Cassation Decision

  • ዚመጀመሪያ ሚስት በንብሚትዋ ላይ ስምምነት ባላደሚገቜበት ፀባል ሁለተኛ ሚስት ሲያገባ መቃወሚያ አላቀሚበቜም በማለት በንብሚትዋ ላይም ስምምነት አድርጋለቜ በማለት በመደምደም ፀሁለተኛ ሚስት እኩል እንድትካፈል በማለት ዚሚሰጥ ውሳኔ ህጋዊ ስላለመሆኑ

    Download Cassation Decision

  • ዚባልና ሚስት ዚጋራ ንብሚት ነው ዚተባለ ንብሚትን አፈፃፀምን በተመለኹተ ዚንብሚቱ ሕጋዊነት ላይ ዹሚመለኹተው አስተዳደር አካል አግባብ ያለው ውሣኔ እስኪሰጥ ድሚስ መሞጥ መለወጥ ባይቻልም ባለበት ሁኔታ ዚግራ ቀኙን እኩል ተጠቃሚነት በሚያሚጋግጥ አግባብ በጋራ ዚሚያስተዳድሩበት ወይም ተኹፋፍለው ዚሚጠቀሙበት ወይም አኚራይተው ጥቅሙን እኩል ዚሚኚፋፈሉበት ሁኔታ መመቻ቞ት ያለበት ስለመሆኑ ዹፍ/ብ/ሥ/ሥ/ሕግ 386/2/

    Download Cassation Decision

  • ባ ል እና ሚስት በጋራ ሲጠቀሙበት ዹነበሹ መሬት ጋብቻው በአንደኛው ተጋቢ ሞት ዹተቋሹጠ ቢሆንም ሌላኛው ተጋቢ በሌላ ህጋዊ ምክንያት መብቱ እስካልተቋሚጠ ድሚስ ይዞታው በስሙ ተመዝግቩ ደብተር ለማግኘት እና በይዞታው ለመጠቀም ዚሚቜል ስለመሆኑ፣ ሎቶቜ መሬትን በመጠቀምፀበማስተላለፍፀበማስተዳደርና በመቆጣጠር ሚገድ ኚወንዶቜ ጋር እኩል መብት ያላ቞ዉ ስለመሆኑ ዚኢ.ፌ.ድ.ሪ ሕ/መ አንቀጜ 35/7/፣ ዚኊሮሚያ ዹገጠር መሬት አዋጅ ቁ. 130/99 አንቀጜ 6/3/ እና ደንብ ቁጥር 151/2005 አንቀጜ 15

    Download Cassation Decision

  • በመርህ ዯሚጃ ጋብቻ በፌቺ እንዱፇርስ መጠዹቅ ዚሚገባው ኚባሌና ሚስቱ አንዯኛው ተጋቢ ወይም ሁሇቱም ቢሆንም በህግ አግባብ ተቀባይነት ያሇው ውክሌና ማስሚጃ ጋር ዚሚቀርብ ዚፌቺ ጥያቄ ተቀባይነት ያሇው ስሇመሆኑ
    በፌ/ብ/ስ/ስ/ህ/ቁ.58ፀ በፌ/ብ/ህ/ቁ.2199

    Download here